ሞዴል ምህረት ክፍሌ ትውልዷ በኢትዮጵያ ቢሆንም ቤልጄማዊ ዜግነት ያላት ናት፡፡ ምህረት ከ2 ዓመት በፊት በ63 ዓመት ከሚበልጧት የቢራ ነጋዴው ቡርኖ ኤች ሱበርት ጋር የፈፀመችው ጋብቻ በጀርመን ታብሎይድ ጋዜጦች አበይት መነጋገርያ ሆኖ ነበር፡፡ የመጀመርያ ሚስታቸው ከሞተች ከ5 ወራት በኋላ የተፈፀመ ጋብቻ በመሆኑ የቢራ ነጋዴውን ቤተሰብ ክፉኛ አሳዝኖ እንደነበር የዴይሊ ቴሌግራፍ ዘገባ አውስቷል፡፡
የ64 ዓመቱ ሃንስ ፒተር ባቀረበው ክስ ..አባቴ ታሞ በነበረ ጊዜ የሚወስዳቸውን ፈሳሽ ነገሮች በመደበቅ በድርቀት እንዲጐዳ አድርጋ ለሞት ያበቃችው ምህረት ክፍሌ ናት፡፡ ወንጀሉን የሰራችው፣ ምናልባትም ሃብት ለመውረስ ካላት ፍላጐት የመነጨ ሳይሆን አይቀርም.. ብሏል፡፡ የፍራንክፈርት ፖሊስ በቀረበው ክስ፤ ምርመራ መጀመሩን የገለፀው የዴይሊ ሜል ዘገባ፤ የቢራ ነጋዴው ከሞቱ ከ5 ቀናት በኋላ ባለቤታቸው ሞዴል ምህረት ክፍሌ ፓርቲ ስትጨፍር ታይታለች፤ የሚለውን መረጃ ለዘገባው መነሻ ማድረጉን ገልጿል፡፡ የጀርመን ቢራ ንጉስ ሲባሉ የኖሩት የ90 ዓመቱ ብሩኖ ኤች ሱበርት ..ለሞዴል ምህረት ክፍሌ ሙሉ ሃብታቸውን እንዳወረሷትና ልዩና የማፈቅራት ሰው ነች፡፡ ማርጀቴ እንዴት ቆጨኝ.. ብለው በኑዛዜያቸው መናገራቸውን ዴይሊ ሜል ጨምሮ አውስቷል፡፡