ኢማና መርጋ በውድድር ዘመኑ ከታዩ ምርጥ የረጅም ርቀት አትሌቶች አንዱ መሆኑን የሚገልፁ መገናኛ ብዙሃን በለንደን ኦሎምፒክ ትኩረት ከሚደረግባቸው አትሌቶች ተርታ መድበውታል፡፡ አትሌት ኢማና መርጋ ዘንድሮ በዓለም አትሌቲክስ በ10ሺ ሜትር በ1355 ነጥብ ሁለተኛ፤ በ5ሺ ሜትር በ1353 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ የያዘ ሲሆን በሁሉም የአትሌቲክስ ውድድሮች በ1384 ነጥብ 18ኛ ላይ እንዲሁም በጎዳና ላይ ሩጫ ውድድሮች በ1139 ነጥብ 41ኛ ደረጃ ላይ ተመዝግቧል፡፡
በሌላ ዜና በ800 የዓለም ሪኮርድን የያዘውና በ34 ውድድሮች ሳይሸነፍ የቆየው ኬንያዊው አትሌት ዴቪድ ሩዱሻ በ17 ዓመቱ ኢትዮጵያዊ አትሌት መሃመድ አማን መቀደሙ አነጋጋሪ ሆነ፡፡ አትሌት መሃመድ አማን ሩዲሻን ያሸነፈው በጣሊያኗ ሚላን ከተማ ከሳምንት በፊት በተካሄደው የግራንድ ፕሪ ውድድር ሲሆን ርቀቱን በ1 ደቂቃ ከ43.50 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ሲያጠናቅቅ ሩዲሻን በ0.07 ሰኮንዶች ቀድሞት ገብቷል፡፡ ያስመዘገበው ሰአትም በርቀቱ የውድድር ታሪክ የምንገዜም ሁለተኛው ፈጣን ሰአት ሆኗል፡፡ አትሌት መሃመድ አማን በ800 ሜትር በ2009ና 2011 እኤአ ላይ በአፍሪካ ወጣቶች ሻምፒዮና ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች ያስመዘገበ ሲሆን ዘንድሮ በዓለም ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና በፈረንሳይ ሊል የብር ሜዳልያ ተጎናፏል፡፡ እንደ ኬንያው ዴይሊ ኔሽን ዘገባ አትሌት መሀመድ አማን በለንደን ኦሎምፒክ ብቻ ሳይሆን በ800 ሜትር በዴቪድ ሩዲሻ ለተመዘገበው የዓለም ሪኮርድ ለመስበር ዋና ተቀናቃኝ ነው፡፡