Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 12 January 2013 09:28

ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ከጌታ መንገድና ከኢህአዴግ መንገድ አንዱን መምረጥ ይኖርባቸዋል! Featured

Written by 
Rate this item
(5 votes)

የኢትዮጵያ ሕዝብ ጨረቃን ከሰማይ አውርዱልን እያለ አይደለም። የኢትዮጵያ ሕዝብ እያለ ያለው ግልጽነትን፣ ቀጥተኝነትን፣ ቅንነትንና ሀቀኝነትን አውርዱልን ነው። ዴሞክራሲን አውርዱልን ነው። ቁሳዊ ልማት ብቻውን አይበቃም፣ ሰብአዊና መንፈሳዊ ልማትንም አውርዱልን ነው።
ዶ/ር ኃይሉ አርአያ
የጌታ ኢየሱስ መንገድ ስል የክርስትና ሃይማኖት ዕምነት ቀኖናውን (ዶግማውን) ሳይሆን ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ ሲያስተምር ያሳየውን የቀናነት፣ የሃቀኝነት፣ የግልጽነት፣ የፍትሓዊነት፣ የእኩልነት፣ የአንድነት፣ የነፃነት፣ የዴሞክራሲያዊነት፣ የመተሳሰብ፣ የመፈቃቀር፣የመከባበር፣ የመተማመን... መንገድ ማለቴ ነው። ይህ መንገድ የክርስትና ሃይማኖት ብቻ ሳይሆን የእስልምና እንዲሁም የሌሎች የዓለም ታላላቅ ሃይማኖቶች መንገድ ነው።

በዚህ መንገድ በሚመራ ህብረተሰብ ውስጥ በዕውቀት (በችሎታ) ማነስ ወይም በተራ ስህተት ወይም በስንፍና ካልሆነ በስተቀር ሆን ተብሎ፣ ታስቦና ታቅዶ በተንኮል በሚፈጸም ቂም በቀል፣ ግፍና በደል አገርና ሕዝብ አይጎዱም። የኢትዮጵያ ሕዝብ በዚህ መንገድ ቢመራ ከድህነትና ከኋላ ቀርነት የመላቀቅ፣ በዴሞክራሲያዊና ፍትሐዊ ሥርዓት የመመራትና በነፃነት፣ በሠላምና በአንድነት የክብር ኑሮ የመኖር ተስፋው እየራቀ ሳይሆን እየቀረበና እየለመለመ ይመጣል። የሚያሳዝነው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመራው በዚህ መንገድ ሳይሆን በኢህአዴግ መንገድ ነው። የኢህአዴግ መንገድ ደግሞ በአብዛኛው ከላይ ከተገለጸው መንገድ የተለየ ነው። በእኔ እምነት የኢህአዴግ መንገድ ቀናነት፣ ግልጽነትና ሀቀኝነት የሚጎድለው መንገድ ነው።
ከታሪካቸው እንደተረዳሁት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከልብ አማኝ ክርስቲያን ናቸው፣ ወደ ፊት ካልተለወጡ በስተቀር። በመሆናቸውም የጌታ ኢየሱስ አስተምህሮን የህይወታቸው መመሪያ አድርገው ይወስዳሉ ብዬ አምናለሁ። በከፍተኛ ትምህርት ተቋም መምህርና ዲን በነበሩበት ጊዜ የዕለት ተዕለት ሥራቸው ከዕውቀት፣ ከጥናትና ከምርምር እንዲሁም ከትምህርት አስተዳደር ጋር የተያያዘ ስለነበር የሥራ ህይወታቸውን ከሃይማኖታዊ መርሆቻቸውና እሴቶቻቸው ጋር አጣጥመው ለማስኬድ ብዙም አያስቸግራቸውም ነበር ብዬ እገምታለሁ። ከጊዜ በኋላ፣ በፖለቲካው ዓለም ውስጥ ሲገቡና በመሥመሩ በደረጃ እያደጉ ሲመጡ ግን ችግር ሳይገጥማቸው አልቀረም ብዬ አስባለሁ።
ፖለቲካ በመሰረቱ ሳይንስም ኪነጥበብም ነው። በመሆኑም በትምህርት ዓለም እንደተፈላጊ የዕውቀት መስክ ተወስዶ ሰዎች በከፍተኛ ደረጃ እየሠለጠኑበት ነው። ሆኖም በጊዜ ሂደት ቅንነቱና ሀቀኝነቱ የጎደላቸው ፖለቲከኞች ፖለቲካን በሥራ ላይ ሲያውሉት አጠቃቀሙን ስላበላሹት ሕዝብ ስለፖለቲካ ያለው አመለካከት ቀና አይደለም። ከዚያም ባሻገር ፖለቲካ ማለት የመቅጠፍ፣ የማስመሰል፣ የመዋሸትና ቅንነት የጎደለው አካሄድ ነው እስከማለት ተደርሷል።
ፖለቲካን እንደ ሳይንስነቱና እንደ ኪነጥበብነቱ በሥራ ላይ ለማዋል ከፍተኛ ቅንነትና ሀቀኝነት (ፈረንጆች በጠቅላላው honesty and integrity የሚሉትን) ይጠይቃል። ቅንነቱና ሀቀኝነቱ ያላቸው ሰዎች በብዛት ወደ ፖለቲካ ሙያ ባለመምጣታቸው ግን በአገራችን ፖለቲካ እንደሚባለው ሊሆን አልቻለም።
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከተናገሯቸው ውስጥ ሁለት ኣጫጭር ምሳሌዎችን በመውሰድ በኢህአዴግ መንገድና የጌታ ኢየሱስ መንገድ ባልኩት መካከል ያለውን ልዩነት እንደምሳሌ በትንሹ እንመልከት። የምንመለከታቸው ምሳሌዎች ትንንሽ ይሁኑ እንጂ የትልልቅ ችግሮች ምልክቶች ናቸው። አንደኛው ትንሽ ነገር ግን የትልቅ ነገር ምሳሌ ነው የምለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፓርላማ የመጀመሪያ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን ሲያቀርቡ ከተናገሩት የተወሰደ ነው። አንድነት ፓርቲንና ልሣኑን ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣን ይመለከታል። እርሳቸው ወደ አሉት በቀጥታ ከመሄዳችን በፊት ግን ትንሽ ማብራሪያ ላስቀድም።
አንድነት ፓርቲ እንደማንኛውም ዜጋ ሆነ ድርጅት በሕገ መንግሥቱና በፓርቲዎች ምሥረታ ዓዋጅ የተሰጠው ሀሳብን በነፃነት የመግለጽ መብትን ለመጠቀም ፍኖተ ነፃነት የተባለ ጋዜጣ ጀመረ። ጋዜጣው የሚታተመው በብርሃንና ሠላም ማተሚያ ድርጅት ነበር። ጋዜጣው በሕዝብ ዘንድ ተወዳጅነቱ እያደገና የህትመት ቅጂውም እየጨመረ ሲመጣ ችግሮች መታየት ጀመሩ። ለምሳሌ መጀመሪያ ብርሃንና ሠላም ማተሚያ ደርጅት በአታሚና በአሳታሚ መፈረም አለበት ያለውንና በሕገመንግሥቱ የተከለከለውን ቅድመ ሳንሱር በጓሮ በኩል የሚያስገባ አዲስ የሥራ ውል ሠነድ ድንገት ይዞ ብቅ አለ። አንድነት የሠነዱን ይዘት በሕግ ባለሙያ አስጠና። ጥናቱም የተወሰኑ የሰነዱ ቁልፍ አንቀጾች ሕጋዊ መሠረት የሌላቸው መሆናቸውን አመለከተ። ስለዚህ አንድነት ሠነዱን እንደማይፈርም አስታወቀ። በዚህ ጊዜ አታሚው ድርጅት በቀጥታ የውል ሠነዱ ካልተፈረመ ጋዜጣውን አላትምም ማለትን ትቶ ሌሎች ምክንያቶችን ማፈላለግ ጀመረ። ከጋዜጣው አዘጋጆች እንደተረዳሁት፣ አንዱ የተሰጠው ምክንያት “በርካታ ሰዎች በጋዜጣችሁ በምታወጧቸው ነገሮች ላይ ቅሬታ ያላቸው መሆኑን ስለገለጹልን” የሚል ነው። አታሚው ድርጅት ይህንኑን ምክንያት በጽሑፍ እንዲሰጥ በጽሑፍ ተጠይቆ ለመስጠት ፈቃደኛ እንዳልሆነ ነው የተረዳሁት።
የብርሃንና ሠላም ምክንያት ምን ያህል አሳማኝ ነው? በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት (አለ እንበልና) ጋዜጣውን ያነበቡ ሰዎች ቅር ተሰኙ ተብሎ አላትምም ይባላል? ቅር የተሰኙ ሰዎችስ እነማን እነማን ናቸው? እዚህ ላይ ቅንነት፣ ግልጽነት፣ ሀቀኝነት፣ ነፃነትና ሌሎች ባህሪያት የሀገራችን ዜጎች፣ ድርጅቶችና ኃላፊዎቻቸው እንዲሁም ህብረተሰባችን በአጠቃላይ ዛሬም ቢሆን የሚመሩባቸው የተከበሩ እሴቶች ናቸው ከሚል እምነት በመነሳት አንዳንድ ጥያቄዎችን እናንሳ። ለምንድን ነው ብርሃንና ሠላም አሳታሚ ድርጅት በድንገት፣ የዜጎችና የድርጅቶች ሀሳብን በነፃነት የመግለጽ ሕገመንግሥታዊ መብትን የሚጥሱ አንቀጾችን የያዘ የሥራ ውል እንዲህ ደፍሮ ያመጣው? ሠነዱ የያዘው ሀሳብ ምን ያህል የራሱ ነው? የበላይ ስውር እጅ አለበት? ድርጅቱ ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣን ለማተም ለምን ይህን ያህል ተቸገረ? ጋዜጣውን አላትምም ያለበትንስ ምክንያት በጽሑፍ ለመስጠት ያልፈለገው ለምንድን ነው? በእኔ እምነት ከዚህ ሁሉ በስተኋላ የአንድነት ጋዜጣ እንዳይታተም የሚያደርግ የኢህአዴግ እጅ አለበት። ይህ የተለመደ የኢህኣዴግ ፖለቲካዊ አካሄዱ ነው።
ከብርሃንና ሠላም ማተሚያ ቤት የሕግ ክፍል ኃላፊ ጋር በግንባር ተገናኝተን ሲናገሩ እንደሰማሁት፤ ማተሚያ ቤቱ አዲስ ውል እንዲያወጣ የተገደደው ራሱን ከሕግ ተጠያቂነት ለማዳን ነው የሚል ነው። እዚህ ላይ አንድ የሕግ ነጥብ ግልጽ መሆን አለበት። በቅድሚያ ሕጋዊነት በሰፈነበት ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት፣ አንድ አሳታሚ አካል በሕግ መጠየቅ አለበት ከተባለ የሚጠየቀው አሳትሞ ባወጣው ነገር ነው። የቅድመ ሳንሱር መቅረት ትርጉም የሚኖረው እዚህ ላይ ነው። በሌላ በኩል ሕጉ እንደሚለው፤ አታሚው አትሞ ባወጣው ነገር ላይ በሕግ መጠየቅ ካለበት የሚጠየቀው አሳታሚው ሳይገኝ ሲቀር ብቻ ነው። እዚህ ላይ አሳታሚው አካል በብሔራዊ ደረጃ የተደራጀ፣ አምኖ ለሚያደርገው ነገር ሁሉ ኃላፊነትን ለመውሰድ ዝግጁ የሆነ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ ነው። በአገር የማይገኝበት አንድም ምክንያት የለም። ስለዚህ ብርሃንና ሠላም አዲስ የውል ሠነድ ያመጣሁት ራሴን ከተጠያቂነት ለማዳን ነው የሚለው ምክንያቱ ውሀ አይቋጥርም። የሕግ መሠረት የለውም። ነገር ግን የብርሃንና ሠላም ኃላፊዎች የሕዝብ ሀብት የሆነውን ድርጅት በእጃቸው ስለያዙ ብቻ አጼ በጉልበቱ ሆነውና ሃይ የሚላቸው ኃይል ጠፍቶ አሊያም አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ ሆኖ ሕዝብ ሀሳቡን በነፃነት የመግለጽና መረጃ በነፃነት የማግኘት መብቱ ተረግጦ ይነጋል፣ ይመሻል። ብርሃንና ሠላም ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣን አላትምም ሲል አንድነት ሌሎች አታሚዎች ፍለጋ ሄደ። አንዳንድ ማተሚያ ቤቶች ፍኖተ ነፃነት የተቃዋሚ ፓርቲ ጋዜጣ መሆኑን ሲያውቁ በራቸውን ይዘጋሉ። ምን አስፈራቸው? ሌሎች አንዳንድ አታሚዎች እሺ እናትማለን ብለው ገንዘብ ከተቀበሉ በኋላ ባልታወቀ ምክንያት ስልክ ደውለው ጋዜጣችሁን አናትምም፣ ኑና ገንዘባችሁን ውሰዱ ይላሉ። ማን ወዮላችሁ አላቸው? አሁንም ሌሎች ማተሚያ ቤቶች ጋዜጣውን አንድ ጊዜ ያትሙና ከሳምንት በኋላ ቀጣዩን ጋዜጣ ለማሳተም ሲኬድ በሆነ አስፈራሪ ኃይል አሁንም ወዮላችሁ የተባሉ ይመስል አናትምም ይላሉ። ለምን ሲባሉ ምክንያቱን በግልጽ ለመናገር ፈቃደኞች አይደሉም ወይም የሆነ የማያሳምን ሰንካላ ምክንያት ይሰጣሉ። ለምሳሌ ሥራ በዝቶብናል፣ ወረቀት የለንም ይላሉ፣ ሥራ እንዳልበዛባቸው ወይም የወረቀት እጥረት እንደሌለባቸው በግልጽ የሚያሳዩ ማስረጃዎች ቢኖሩም። አንዳንዶቹ ሊገልጹት የማይፈልጉት የጭንቀት መንፈስ በውስጣቸው ይታያል። ሌሎቹ ደግሞ “እባካችሁ ተዉን ልጆቻችንን እናሳድግበት”፣ “እኛ ችግር ውስጥ መግባት አንፈልግም፣ በሠላም ሰርተን ለመኖር ነው የምንፈልገው”፣ “ከአቅም በላይ የሆነ ችግር አለብን”፣ “መመሪያ ተሰጥቶናል” ይላሉ ሾላ በድፍኑ። መመሪያ የሰጣችሁ ማን ነው? መመሪያው የተሰጣችሁ በጽሑፍ ነው ወይስ በቃል፥ በሥልክ ነው ወይስ በአካል ተብለው ሲጠየቁ ለመናገር ፈቃደኞች አይደሉም። በዚህ ጊዜ ነው አንድነት “የፍትሕ ያለህ!” ለማለት ለጠቅላይ ምኒስትሩ የአቤቱታ ደብዳቤ የጻፈውና የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉም ጉዳዩን በፓርላማ የጥያቄ ጊዜ ያቀረቡት። በዚህ ጊዜ ነው ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩም በተለመደው ኢህአዴጋዊ መንገድ በመሄድና የቀዳሚያቸው የአቶ መለስ ዜናዊን የአነጋገር ስልት በተከተለ መንፈስ በአንድነት አቤቱታ ላይ የተሳለቁት።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ የስላቅ ንግግር መንፈሱ ምን ይላል? እኛ ለአንድነት ጋዜጣውን የሚያትምለት ማተሚያ ቤት አንፈልግለትም። በአዲስ ኣበባ ውስጥ 34 ማተሚያ ቤቶች አሉ። ከእነዚህ ማተሚያ ቤቶች ጋር በመነጋገር ጋዜጣቸውን ሊያሳትሙ ይችላሉ ነው የሚለው። በጤናማ የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ ብንሆን ኖሮ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያሉት ትክክል ነው ማለት ይቻል ነበር። ችግሩ የሚመነጨው ጤናማ የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ ባለመሆናችን ነው።
በጤናማ የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ ብንሆን ኖሮና ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩም የኢህአዴግን ሳይሆን ቀና፣ ግልጽና ሀቀኛ የሆነውን የጌታ ኢየሱስ መንገድ ቢከተሉ ኖሮ ምን ማድረግ ወይም ምን ማለት ይችሉ ነበር? ሁለት አማራጮች ነበሯቸው። የጽሕፈት ቤታቸው ዋና ሥራ፣ ሕግ አውጪው አካል ያወጣቸውንና ሕግ ተርጓሚው አካል በሕገመንግሥቱ መሠረት የወጡ ናቸው ያላቸውን ሕጎች ማስፈጸም ነው። ለዚህም ነው ጽ/ቤታቸው “አስፈጻሚ አካል” የተባለው። ስለዚህ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአፈጻጸም ችግር እንዳለ የሚያመለክት አቤቱታ ሲቀርብላቸው አንደኛው አማራጫቸው፣ ባለው የአሠራር ተዋረድ ጉዳዩ እንዲጣራ አመራር መስጠትና በተገኘው መረጃና ሕጉ በሚያዘው መሠረት የአፈጻጸም መመሪያ መስጠት ነው። ጉዳዩ እዚያ ላይ ያልቃል።
ችግሩ መፍትሔ ሳያገኝ ቀርቶ አቤቱታው በጥያቄ መልክ ፓርላማ ከቀረበ ዘንዳ ሁለተኛው አማራጭ በቀና መንፈስ፣ በጌታ ኢየሱስ መንገድ፣ የፖሊሲ ማብራሪያ መስጠት ነው። ማብራሪያውም የሚከተሉት መሠረታዊ ሀሳቦችን ሊያካትት ይችላል።
እንደ መግቢያና እንደ በጎ አስተሳሰብ ማሳያ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአንድነትን ችግር የተገነዘቡ መሆናቸውን፣
ሕገመንግሥታችን ሃሳብን በጽሑፍም ሆነ በቃል የመግለጽ መብትን የሚያረጋግጥ መሆኑን፣
ማተሚያ ቤቶች እንደማንኛውም አገልግሎት ሰጪ ድርጅት ለሕግና ለገበያ ሥርዓት ተገዥ መሆን ያለባቸው መሆኑን፣
ሕዝብን ለማገልገል ቃል ገብተው የንግድ ፈቃድ ያወጡ ማተሚያ ቤቶች፣ አሳታሚዎች በሕጋዊ መንገድ እስከቀረቡና በግልጽ የተቀመጡና አግባብነት ያላቸው ቅድመ ሁኔታዎችን በተገቢው ሁኔታ እስካሟሉ ድረስ ሊያስተናግዷቸው የሚገባ መሆኑን፣ ይህን ካላደረጉ በሕግ ሊጠየቁ እንደሚችሉ፣ ከዚህ ባለፈ ማተሚያ ቤቶችን የሚያስፈራሩ ወገኖች ካሉ ድርጊታቸው ህገወጥ ስለሆነ ከዚህ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ፣
ስለዚህም ከዚህ አጠቃላይ መግለጫ በኋላ አንድነት ጋዜጣውን ለማሳተም ችግር እንደማይገጥመው ተስፋ ያላቸው መሆኑን፤
ይህ መንገድ መካሪ፣ አስታራቂ፣ አስጠንቃቂ፣ ሠላም ፈጣሪ፣ የበሰለ፣ የሰከነና የቀና ፖለቲከኛ መንገድ ነው። ይህ መንገድ ከማሾፍ፣ ከስላቅና ከአራዳነት መንገድ ምን ያህል እንደሚለይ ማየት ይቻላል። ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የፓርላማ ንግግር በኋላ አንድነት ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣውን ለማሳተም ማተሚያ ቤት ፍለጋ ብዙ ጥሯል። ሆኖም የገጠመው ቀደም ሲል የተገለጸው ሁኔታ ነው። የጋዜጣው ሕትመት እንደታፈነ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብም ነፃ ሃሳቡን በነፃነት የመግለጽና መረጃ የማግኘት መብቱ እንደተነፈገ ነው። እዚህ ላይ ሊጤን የሚገባው ማተሚያ ቤቶች የመንግሥት ግብር እየከፈሉ ሠርቶ የማትረፍና ንብረት የማፍራት ሕገመንግሥታዊ መብታቸው ሲረገጥ በደሉን የመቋቋም ወኔ አጥተውና በፍርሀት ተሸማቅቀው ሁኔታውን አንገታቸውን ደፍተው እየተቀበሉ ማለፋቸው የሚያሳዝንና የሚያሳፍር መሆኑ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩት ካሉት የሚወሰደው ሁለተኛው የኢህአዴጋዊ አካሄድ ምሳሌ በቅርቡ ከአልጀዚራ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ጋር ባደረጉት ቃለምልልሰ እስረኞችን በተመለከተ የተናገሩት ነው። በዚህ ቃለምልልስ በኢትዮጵያ ውስጥ አንድም የፖለቲካ እስረኛ እንደሌለ ነው የተናገሩት። የእርሳቸውና የፓርቲያቸው የኢህአዴግ አስተሳሰብ አያሳምንምና አያስከብርም እንጂ በጣም ግልጽ ነው። እንደሳቸውና እንደ ፓርቲያቸው አስተሳሰብ እንደ እነ አንዱዓለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ እስክንድር ነጋ፣ ዘሪሁን ታዬ፣ በቀለ ገርባ፣ ኦልባና ለሊሳ፣ ርዕዮት ዓለሙ የመሳሰሉ እስረኞች የፖለቲካ እስረኞች አደሉም። በእርሳቸውና በፓርቲያቸው በኢህአዴግ አስተሳሰብና አካሄድ መሠረት እነዚህ ሰዎች በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው፣ ተከስሰው፣ በማስረጃ “ተረጋግጦባቸው”፣ ፍርድ ቤት የፈረደባቸው “ወንጀለኞች” ናቸው። ይህ የተለመደ የኢህአዴግ ደረቅ መንገድ ነው። የቀረበባቸው ክስ የፈጠራ ክስ ነው። የቀረበባቸው ማስረጃ አሳማኝ አይደለም። የፈረደባቸው ፍርድ ቤት ነፃና ገለልተኛ ሊባል አይችልም። የክሱ ዓላማ ለነፃነት፣ ለፍትሕና ለዲሞክራሲ የሚታገሉ የፖለቲካ ጀግኖችን በሕግ ሽፋን ለማጥቃትና ሕዝብን ለማሸማቀቅ እንጂ ሕግን ለማስከበርና የሃገር ደህንነትን ለመጠበቅ አይደለም። በዚህ ሁኔታ የታሰሩ ዜጎች የፖለቲካና የህሊና እስረኞች እንጂ ወንጀለኞች አይደሉም። የፖለቲካና የህሊና እስረኛ ሆነውማ የሠለጠነውና ለፍትሕ፣ ለሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች አክብሮት ያለው ዓለም እየመሰከረላቸው ነው። ብዙዎቹንም እየሸለማቸው ነው።
ቀናና ሀቀኛ በሆነው በጌታ ኢየሱስ መንገድ በሚመራ ሥርዓት ውስጥ ዜጎች በፈጠራ ክስ አይከሰሱም። ጉዳያቸው በነፃ ፍርድ ቤት ከመታየቱና ከመወሰኑ በፊት በአደባባይ (በፓርላማ ፊት) ወንጀለኞች ናቸው አይባሉም። የሚቀርቡ ማስረጃዎች በማንኛውም ሚዛናዊ በሆነ ዓይን ሲታዩ ተአማኒነትና ተቀባይነት ያላቸው ናቸው። ፍርድ ቤቶች ነፃና ገለልተኞች ናቸው። በዚህ ዓይነት መንገድ የሚመራ ጤናማ የፖለቲካ ሥርዓት በሰፈነበት ሀገር የዓቃቤ ሕግ ዋና ዓላማ በማንኛውም ወገን ሕግ እንዲከበርና የዜጎች መብት እንዳይጣስ መከላከል እንጂ ሥልጣንና የሕግን ረቂቅና ውስብስብ ባህሪን በፖለቲካ ማጥቂያ መሣሪያነት በመጠቀም የአንድ የፖለቲካ ወገን ጥቅም ጠባቂ መሆን አይደለም።
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በኢህአዴግ መንገድ እና ቀና፣ ሀቀኛና የጌታ መንገድ በተባለው መካከል ልዩነት ወይም ቅራኔ የለም ብለው ሊያምኑና እስከመጨረሻው ሊከራከሩ ይችላሉ። የእሳቸው እምነትና ክርክር አንድ ነገር ነው። ከጌታም ሆነ ከሕዝብ እይታ የማይደበቀውና በመሬት ላይ ያለው ሀቅ ደግሞ ሌላ ነገር ነው። በእኔ እምነት በኢህአዴግ መንገድና በጌታ መንገድ መካከል ብዙ ልዩነት አለ።
አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ የሃይማኖት ሰው መሆናቸውን ስሰማ ትልቅ ተስፋ ነው በውስጤ ያደረብኝ። ያ ተስፋ አሁንም አለ። ከዚህ በፊት የነበሩና አሁንም ያሉ ዋና ዋና የኢህአዴግ መሪዎች አብዛኛዎቹ የማሌሊት (ማርክሲስት ሌኒንስት ትግራይ) ቅኝቶች እንደነበሩና እንደ ማርክሲስትነታቸው በእግዚአብሔር አያምኑም ስለሚባሉ፣ ይህም በመሆኑ ፈሪሀ እግዚአብሔር አለባቸው ተብሎ ስለማይወሰድ፣ አሊያም ደግሞ በሰብአዊነት ፍልስፍና በዳበረ ባህሪ ይገዛሉ ብሎ ማመን ስለሚያዳግት በማን አምላክ ሊባሉ እንደሚችሉ ለማወቅ ግራ የሚያጋባ ነበር ማለት ይቻላል። በአሁኑ ጊዜ ግን በሃይማኖታዊ እምነታቸው ጠንካራ የሆኑና ፈሪሀ እግዚአብሔር ያላቸው ሰው በዋና የመሪነት ቦታ ላይ ይገኛሉ። ስለዚህ ነው በአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ አመራር ሀገራችን በብልጣብልጥነትና በመሰሪ ፖለቲካ ሳይሆን ብልህነት በሰፈነበት፣ ቀና፣ ግልጽና ሀቀኛ በሆነ የዲሞክራሲ መንገድ የምትመራበት ጊዜ ተቃርቦ ሊሆን ይችላል የሚል ተስፋ ያደረብኝ።
አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ታሪካዊ መስቀለኛ መንገድ ላይ ናቸው። ሁለት አማራጮች አሏቸው። አንደኛው አማራጭ የኢህአዴግ መንገድ ትክክል ነው በሚል (የተሳሳተ) እምነት “የመለስን ራዕይ እውን ማድረግ” በሚል መፈክር የአንድ አምባገነን አውራ ፓርቲ ሥርዓትን በተለመደው የአፈናና የጭቆና መንገድ እንዲቀጥል ማድረግ ነው። ይህን ማድረግ ደግሞ እውነተኛ የመድበለ ፓርቲ ዴሞክራሲ ለኢትዮጵያውያን ህልም ሆኖ እንዲቀር ማድረግ፥ በቁሳዊ ልማትና በሕዝቡ የዕለት ተዕለት ኑሮ የማይታይ የዕድገት ፕሮፓጋንዳ የሕዝብን አዕምሮ አደንዝዞ መግዛት፣ ሙስና እየተስፋፋ ሄዶ በሌሎች አንዳንድ አገሮች እንደሚታየው መቆጣጠር እማይቻልበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ መፍቀድ፣ በተዛባ የሀብት ክፍፍል ሥርዓት ጥቂት ሀብታሞች ከሥርዓቱ ጋር ለጋራ ጥቅም በመሻረክ ይበልጥ ሀብታሞች እየሆኑ እንዲሄዱ፣ ብዙሃኑ ድሆች ደግሞ በሥራ አጥነትና በኑሮ ውድነት እየተደቆሱና የባሰ ድሃ እየሆኑ እንዲሄዱ የሚያደርግ ሁኔታ መፍጠር፣ ወጣቱ ትውልድ ጥራት ያለው ትምህርት ለማግኘት ካለመቻሉም በላይ ሠርቶ የማደር ተስፋው እየመነመነ በመሄዱ በሀገሩ ተስፋ ቆርጦ የሚሰደድበትና ለበረሃና ለባህር ላይ ሞት፣ ከዚህ አደጋ ከተረፈም ለውርደትና ለስቃይ ህይወት የሚዳረግበትን ሁኔታ ማስቀጠል ማለት ነው። በአጭሩ፣ ቀደም ሲል እንደተገለጸው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከድህነትና ከኋላ ቀርነት የመላቀቅ፣ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የመመራትና በነፃነት፣ በሠላምና በአንድነት የክብር ኑሮ የመኖር ተስፋው እየራቀ ይሄዳል ማለት ነው። ሁለተኛው አማራጭና አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝም በሚገባ ይረዱታል፣ ያምኑበታል ብዬ የማምነው ቀደም ሲል የተገለጹት ባህሪያት ያሉት የጌታ ኢየሱስ መንገድ ነው። ይህም ኢህአዴግን ወደዚያ መንገድ፣ ማለትም ወደ ግልጽነት፣ ቀናነትና ሀቀኝነት መንገድ ማምጣት ማለት ነው።የተከበሩ ጠቅላይ ሚኒስትር በህይወታቸው በሚመሩበት ቅዱስ መጽሐፍ የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 6 ቁጥር 24 እንዲሁም የሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 16 ቁጥር 13 “ለሁለት ጌታ መገዛት የሚቻለው ማንም ሰው የለም” ይላል። በሕጉ ዓለምም “የፊዱሺያሪ መርሕ” (The Fiduciary Principle) እንደሚለው “አንድ ሰው ለሁለት ጌታ መታዘዝ አይችልም (No man can serve two masters) እዚህ ላይ፣ ማለትም አሁን በያዝነው ጉዳይ “ሁለት አለቃ” ማለት ግልጽ፣ ቀናና ቀጥተኛ የሆነው የጌታ መንገድ አንደኛው ሲሆን ሌላው ደግሞ ቀናነት፣ ሃቀኝነትና ፍትሐዊነት የጎደለው የኢህአዴግ መንገድ ነው። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሁለቱ መንገዶች ተገዥ ሊሆኑ አይችሉም። ያላቸው አማራጭ በተሰጣቸው ታሪካዊ የአመራር ዕድል ተጠቅመው ኢህአዴግን ወደ ቀናው መንገድ ማምጣትና በታሪክና በኢትዮጵያ ሕዝብ ዘንድ የሚያኮራና የሚያስከብር ሥራ መሥራት፣ አሊያም በተለመደው የኢህአዴግ መንገድ በመቀጠል በታሪክ የሚያስወቅስ ሥራ መሥራት፣ በዚህም ከጌታ እየራቁ መሄድ ነው። የእኔ ምኞትና ጸሎት የመጀመሪያውን እንዲመርጡ ነው።
ዘግይቶ የደረሰ
ከላይ የቀረበውን ጽሑፍ ጨርሼ ለሕዝብ ንባብ ላቅርብ አላቅርብ በማለት ነገ ዛሬ ስል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሪፖርት የሚያቀርቡበትና ጥያቄና መልስ የሚካሄድበት ሌላ የፓርላማ ስብሰባ መጣ። በዚህ ጊዜ የተከበሩ አቶ ግርማ ሠይፉ ከዚህ በፊት እንዳደረጉት የጋዜጣ ማሳተም ችግርን በተመለከተ ቀደም ሲል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉዳዩን አስመልክተው ተናግረውት ከነበረው በመነሳት ጥያቄ አቀረቡ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲመልሱ ከዚህ በፊት ከተናገሩት በተሻለ ሁኔታ ጥሩ እየተናገሩ ከመጡ በኋላ፣ አንድ ቦታ ላይ ሲደርሱ ወደ ኢህአዴግ መንገድ ገቡና ነገር ተበላሸ። ለእኔም አንድ ጥሩ የኢህአዴጋዊ መንገድ ምሳሌ ሰጡኝ። ጥሩ ነገር ሲናገሩ ቆይተው አንድ ቦታ ላይ አንድ ጥያቄ ጠየቁ፣ አንድ ማሳሰቢያ አቀረቡ። ጥያቄውም “ለምንድን ነው ማተሚያ ቤቶች ተቃዋሚዎችን እንደጦር የሚፈርዋቸው?” የሚል ሲሆን ማሳሰቢያቸውም “ተቃዋሚዎች ለምንድን ነው ማተሚያ ቤቶች እንደጦር የሚፈሩን ብለው ራሳቸውን መጠየቅ አለባቸው” የሚል ነበር።
እግዚአብሔር ያሳያችሁ፣ አምላክ ያመልክታችሁ፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አስተሳሰብ ማተሚያ ቤቶች እንደጦር የሚፈሩት የሆነ የሚያስፈራራ የመንግሥት ኃይልን ሳይሆን ተቃዋሚዎችን ነው። እስቲ ልብ በሉ፣ ተቃዋሚዎች ምናቸው ያስፈራል? ደረትና ግንባር የሚመታ አነጣጥሮ ተኳሽ የላቸው፣ ሰው አይገድሉ፣ ወህኒ ቤት የላቸው አያስሩ፣ በፈጠራ ክስ በንግድ ድርጅት ላይ ወገብ የሚሰብር ግብር አይጭኑ ወይም እንዲታሸግና እንዲዘጋ አያደርጉ ወይም ፈቃድ አናድስም አይሉ፣ አያጉላሉ። አባቶቻችን “የማይመስል ነገር ለሚስትህ አትንገር” ይላሉ። ተቃዋሚዎች ቢያስፈሩ፣ የሚያስፈሩት ኢህአዴግን ነበር። ለዚያውም ግን “ኢጎኣቸው” በያሉበት ቸክሎ ይዟቸው ከታሪክ መማርና መተባበር አቅቷቸው ኢህአዴግ አውራ ፓርቲ ነኝ ብሎ ብቻውን እንዲያቅራራ ሜዳውን ትተውለታል።
እስቲ አንድ ሁለት ጥያቄዎችን እናንሳ? ማተሚያ ቤቶች ተቃዋሚዎችን ቢፈሩ ኖሮ ለምንድን ነው ለማተም ፈቃደኛ ሆነው የማሳተሚያ ክፍያ በደረሰኝ በቅድሚያ ከተቀበሉ በኋላ በማግሥቱና ከዚያም በኋላ “ጋዜጣችሁን ልናትምላችሁ አንችልም፣ ኑና ገንዘባችሁን ውሰዱ” የሚሉት? አሊያም አንድን ጋዜጣ አንድ ጊዜ ካተሙ በኋላ ቀጣዩን እንዲያትሙልን ስንወስድላቸው ከተቃዋሚው በኩል የተጓደለ ነገር ሳይኖርና ግልጽና በቂ ምክንያት ሳይሰጡ ለምንድን ነው አናትምም የሚሉት?
ማተሚያ ቤቶች ማንን እንደሚፈሩ በሰማዩ ጌታ ፊት ቀርቶ በማተሚያ ቤቶች፣ በሕዝብ ፊትና በኢህአዴግ በራሱም ፊት ግልጽ ነው። ምን ይሆናል ታዲያ፣ የሰማዩ ጌታ አልተናገረም፣ ማተሚያ ቤቶችም ትንፍሽ አላሉም፣ ሕዝብም እየሰማ ዝም አለ፣ ኢህአዴግም እያወቀ እንደልቡ ያለውን አለ። በመሀል ግልጽነት፣ ቀጥተኝነት፣ ቅንነትና ሀቀኝነት መስዋዕት ሆኑ። የኢትዮጵያ ሕዝብ ጨረቃን ከሰማይ አውርዱልን እያለ አይደለም። የኢትዮጵያ ሕዝብ እያለ ያለው ግልጽነትን፣ ቀጥተኝነትን፣ ቅንነትንና ሀቀኝነትን አውርዱልን ነው። ዴሞክራሲን አውርዱልን ነው። ቁሳዊ ልማት ብቻውን አይበቃም፣ ሰብአዊና መንፈሳዊ ልማትንም አውርዱልን ነው። አሸዋና ስሚንቶ ከኮረት ጋር ቀላቅለን፣ ማጠናከሪያ ብረት አክለን ግድብ ገደብንልህ፣ ፎቅ ሠራንልህ፣ መንገድ ዘረጋንልህ፣ ትምህርት ቤቶች፣ ክሊኒኮች፣ ኮንዶሚኒየም፣ ወዘተ ሠራንልህ፣... ከዚህ የበለጠ ምን ትፈልጋለህ በሚል የ24 ሰዓትና የ7 ቀን ፕሮፓጋንዳ አታሰልቹን ነው። እነዚህ ነገሮች ጥሩ ነገሮች ቢሆኑም ምንም ያህል ይሁኑ ብቻቸውን በቂ አይደሉም ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚለው ከቁሳዊ ልማቱ ጎን ለጎን፣ ነገ ሳይሆን ዛሬ ነፃነትን፣ የኢትዮጵያዊነት ክብርን፣ የመድበለ ፓርቲ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን፣ ፍትሐዊነትን፣ የሕግ የበላይነትን፣ ነፃና ፍትሐዊ ምርጫን፣ የሰብአዊ መብቶች መከበርን... እንፈልጋለን ነው። እነዚህ ሰብአዊ ፍጡራንና የኢትዮጵያ ዜጎች በመሆናችን ብቻ የምጎናጸፋቸው በረከቶች የሚገኙት የጌታ መንገድ በሆነው የግልጽነት፣ የቀጥተኝነት፣ የቅንነትና የሀቀኝነት መሥመር ሲኬድ ብቻ ነው።

Read 12392 times