ከትላንት በስቲያ በመላው ዓለም የተከበረውን የቫለንታይን (የፍቅረኞች ቀን) አስመልክቶ ነገ ከጧቱ ሦስት ሰዓት እስከ ቀኑ 10 ሰዓት በጃንሜዳ ፍቅረኛን በጀርባ አዝሎ ውድድር እንደሚያካሂድ “ኪዩፒድ” የማስታወቂያ ሥራ አስታወቀ፡፡ ውድድሩ ከ18 አመት በላይ የሆኑ ጥንዶች ብቻ እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡ ኪዩፒድ ከአዲስ አበባ አስተዳደር ስፖርት ኮሚሽን ጋር በመተባበር ባዘጋጀው ውድድር ላይ አስር ሺህ ጥንዶች ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ድርጅቱ ገልጿል፡፡ “ልዩነታችን መወሰናችን” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው ውድድር ላይ ነፃ የኤችአይቪ ምርመራና የምክር አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ፕሮግራሙ ሩጫ፣ እግር ኳስ፣ ጠረጴዛ ቴኒስና የኢትዮጵያ ባህላዊ ጨዋታዎች እንዲሁም የዘፈን ግብዣ እንደሚያካትት አዘጋጆቹ ጠቁመዋል፡፡