Saturday, 16 March 2013 11:36

ኢትዮጵያዊቷ በሶርያ ያሳለፈችውን ስቃይ ትናገራለች...

Written by 
Rate this item
(18 votes)

*የወንድ ልጅ ብልት ቆርጠው “ተጫወችበት” ይላሉ--- *ቦንብ ታጥቀሽ ራስሽን አፈንጂ ተብዬ ነበር ---- *አፍሪካውያንን በኤሌክትሪክ ማቃጠል የተሰጠኝ የሥራ ኃላፊነት ነበር--- *ውሃ ስንጠይቅ ሽንታቸውን ነበር የሚሰጡን …እላያችን ላይ ይሸናሉ … ከአማርኛ ይልቅ አረብኛ መናገር ይቀናታል፡፡ የምትናገረው በቁጭት፣ በእልህና በፍርሃት ስሜት ነው፡፡ ከአራት ዓመት በፊት ለሥራ ወደ ሶሪያ የተጓዘችው ሃረግ (ሜሪ)፤ በሶርያ ከጦርነቱ መጀመር ጋር ተያይዞ ያሳለፈችውን መከራና ስቃይ በአንደበቷ ትናገራለች - አንዳንዴ በሰመመን፣ ሌላ ጊዜ በመንገሽገሽ፡፡ ከሶሪያ በሱዳን በኩል አድርጋ ወደ ኢትዮጵያ በገባች በአምስተኛ ቀኗ ከጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ጋር ያደረገችውን ቃለምልልስ ከዚህ በታች አቅርበነዋል፡፡ በሶርያ በምን ሥራ ላይ ነበር የተሰማራሽው? በ2009 ዓ.ም ወደ ሶርያ የሄድኩት በአውሮፕላን ነበር፡፡ እንደሌሎች ሴት እህቶቼ የቤት ውስጥ ሥራ ሳይሆን እርሻ ላይ ነበር ሥራ ያገኘሁት፡፡ ሥራዬ የወይራ ፍሬ መልቀም እንዲሁም ሙዝ፣ ትፋህ፣ አትክልትና ፍራፍሬ መኮትኮት፣ ማጨድ፣ ወዘተ ነበር፡፡ አንድ አመት ሙሉ ብቻዬን ነው የሠራሁት፡፡ ሴት ነሽ--- እንዴት የእርሻ ሥራን ልትመርጪ ቻልሽ? በመጀመሪያም ወደ ሶሪያ ስሄድ ሰው ቤት እንደምቀጠር አልነበረም የተነገረኝ፡፡ እዚያ ስደርስም ወደ ገጠር ነው የተላኩት፡፡ በእርግጥ ግብርናውን ወድጄው ነበር፡፡ ግን የምኖርበት ሰውዬ በጣም አስቸገረኝ፡፡ የተቀጠርኩበት ቤት እናትና ልጅ ነበሩ፡፡ ልጁ ትልቅ ሰው ቢሆንም የአእምሮ ዘገምተኛ ነበር፡፡ እናቱ አሮጊት ናት፡፡ ልጅዬው በተደጋጋሚ ይዝትብኝ ነበር፡፡ አብረሽኝ ካልተኛሽ እያለ ያስጨንቀኛል፡፡ ምን ልበልሽ… በጣም ያሳቅቀኝ ነበር፡፡ እና ስራዬን ሰርቼ ወደ ቤት መመለስ እንደ ጦር ነበር የምፈራው፡፡ ይመታኛል፣ ይጎትተኛል፣ ይጎነትለኛል … አንድ ዓመት ሙሉ በእነዚህ ሰዎች ቤት በስቃይ ቆየሁ ፡፡ ምን ያህል ነበር የሚከፈልሽ? ከዚህ ስሄድ 125 ዶላር እንደሚከፈለኝ ነበር የተነገረኝ፡፡ እዛ ስደርስ ግን መቶ ዶላር ሆነ፡፡ እንዲያም ሆኖ አንድ ዓመት ሙሉ የሰራሁበትን ገንዘብ ከሰዎቹ አልተቀበልኩም፡፡ በቃ ጠፍቼ ነው … የሄድኩት፡፡ በየወሩ አልነበረም ደሞዝ፡፡ አንድ ዓመት ከስድስት ወር ከሰራሽ በኋላ ነው የሚከፍሉሽ፡፡ እንዴት ጠፋሽ? በእርሻው ቦታ ላይ ስሰራ ጎረቤታችን የሆነ አንድ መልካም ሰው ሁልጊዜ ሁኔታዬን ያይ ነበር፡፡ አንድ ቀን አናገረኝ፡፡ እኔም የሚደርስብኝን በደል ሁሉ አጫወትኩት፡፡ እዚህ ሰውዬ ቤት ስቀጠር ህፃን ልጅ አለው ተብዬ ነበር … ይመስለኛል ለሰውዬው ማረጋጊያና ስሜት መወጫ ነው የወሰዱኝ፡፡ እኔ ከሄድኩ በኋላ እናቱን ሌላ አገር ልኳቸው እኔ ብቻ ከእርሱ ጋር ቀረሁ፤ ለሦስት ወር ሁለታችን ብቻ ነበር፡፡ በየጊዜው ይደበድበኝ ነበር፡፡ በተደጋጋሚ በስለት አስፈራርቶ ደፍሮኛል፤ እ..ከዛ በጣም ታመምኩኝ፣ አርግዤ ነበር፡፡ ‹‹ፔሬዴ ቀርቷል፤ ሃኪም ቤት ውሰደኝ አሊያም ወደ አገሬ ላከኝ›› አልኩት፡፡ ‹‹እገልሻለሁ›› አለኝ፡፡ ስንት ቀን እየፈራሁ ዛፍ ላይ ወጥቼ ‹‹አልወርድም›› እለው ነበር፡፡ … ይሄን ሁሉ ይመለከት ነበር - ያ ጎረቤታችን ሰውዬ፡፡ በኋላ ‹‹ከተማ ወስጄሽ የውጪ ዜጎች ቤት ትቀጠሪያለሽ›› አለኝ፡፡ ጎረቤትሽ ማርገዝሽን ያውቅ ነበር? አውቋል፡፡ ወደ ከተማ ሊወስደኝ የተነሳሳው እኮ ይህንንም ሚስጢር አጫውቼው ነው፡፡ ከዚያም ‹‹ማርሊዬስ›› የሚባል ክርስቲያን አረቦች የሚሄዱበት ቤተክርስትያን ወስዶ ጣለኝ፡፡ እዚያ ችግሬን ነገርኳቸው - ለቤ/ክርስቲያኑ ቄስ፡፡ ሀሙስ፣ አርብና ቅዳሜ ለሦስት ቀን ቤተክርስትያን ውስጥ አሳደሩኝ፡፡ “እሁድ ነው ኢትዮጵያውያኖች የሚመጡት፤ ከእነርሱ ጋር ትገናኛለሽ” አሉኝ፡፡ እሁድ ዕለት ኢትዮጵያውያኖች መጡ - ብዙ ናቸው፡፡ የደረሰብኝን በሙሉ አጫወትኳቸው፡፡ ቅዳሴ እንኳን ሳያልቅ ነው ይዘውኝ ወደ ቤታቸው የሄዱት፡፡ አንድ እንደ ትልቅ እህቴ የማያት ሴት ነበረች … ለእሷ ምስጢሬን ሁሉ አጫወትኳት፡፡፡ ‹‹ምንም ችግር የለም›› አለችና ሃኪም ቤት ሄድን፡፡ አስመረመረችኝ -----የሁለት ወር ተኩል እርጉዝ ነሽ ተባልኩ፡፡ እዛ አገር ማስወረድ ክልክል ነው፡፡ እርጉዝ ከሆንሽ ወደ አገርሽ አይልኩሽም፡፡ ከተወለደ በኋላ ልጁን ነጥቀው ነው አንቺን ወደ አገርሽ የሚሰዱሽ፡፡ በጣም አስቸጋሪ ህይወት ነው፡፡ ብወልደውም ልጄን አይሰጡኝም፤ ለማስወረድ ደግሞ ገንዘብ አልነበረኝም … እስከ አምስት መቶ ዶላር ያስፈልጋል ፡፡ ያቺ እንደ ትልቅ እህቴ የማያት ልጅ የምታውቀውን ሰው አነጋግራልኝ፣ እሱ ረዳኝና ፅንሱን አቋረጥኩ፡፡ ልጆች በእስር ቤት ወልደው የሚያሳድጉ ኢትዮጵያውያኖች አሉ ይባላል … በርካታ ኢትዮጵያውያኖች፣ ኤርትራውያኖችም … አሉ፡፡ እኔ ፅንሱን ካቋረጥኩ በኋላ … ሁለት ሳምንት … እቤቷ አረፍኩ፡፡ ምናልባት ሰውዬውም የሚያፈላልገኝ ከሆነ በሚል … ሁለት ሳምንት ሙሉ ከቤት አልወጣሁም፡፡ ከሌሎች ኢትዮጵያውያኖች ጋር ተገናኘሽ … ደማስቆ ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያውያኖች በሙሉ እርስ በርስ ይተዋወቃሉ፡፡ በሳምንት አንድ ቀን እሁድ እሁድ አንድ ላይ እንውላለን፣ ቡና ይፈላል፣ ተሰብስቦ እረፍት መውሰድ፣ መዝናናት የተለመደ ነው፡፡ ሴቶቹ ሰው ቤት ነው የሚሠሩት፡፡ ወንዶቹ ግን አይቀመጡም--- እዛ አገር የሚሄዱበት ምክንያት በቱርክ አድርገው ወደ ሌላ አገር ለመሻገር ነው፡፡ አንቺ ከዛ በኋላ ሌላ ሥራ አገኘሽ ወይስ----- ራሴ አማርጬ ሰው ቤት ተቀጠርኩ፡፡ ቋንቋ ስለማውቅ ችግር አልገጠመኝም፡፡ አሮጊትና ሽማግሌ ባልና ሚስቶች ቤት ተቀጥሬ መሥራት ጀመርኩ ፡፡ ይኸኛውስ ቤት ተስማማሽ? ምን ያህል ይከፈልሽ ነበር? መጀመሪያ ስገባ መቶ ሃምሳ ዶላር ነበር፡፡ በኋላ ሁለት መቶ ሃያ አምስት ዶላር ሆነልኝ፡፡ አሮጊቷ ከተኛችበት አትነሳም፡፡ 85 ዓመቷ ነበር -- እሷን አንስቼ አጥባለሁ፡፡ ፓምፐርስ (የሽንትና የሰገራ መቀበያ) እቀይርላታለሁ፡፡ … መርፌ አወጋግ ልጃቸው አሰልጥናኝ -- መርፌ እወጋቸው ነበር፡፡ እንደ ልጃቸው ነበር የሚያዩኝ፡፡ ልጆቻቸው ዩኤን ነው የሚሠሩት፡፡ የመጀመርያው ቤት ፓስፖርቴን ትቼው ስለወጣሁ እዛ ተመዝግቤ በዚያ ወረቀት ነበር የምጠቀመው፡፡ አሮጊቷ የዛሬ ዓመት ሞተች፡፡ ከዛ ሽማግሌው ልክ እንደ ሚስቱ ሆነ፡፡ እሱን ሳነሳ ስጥል … (95 ዓመቱ ነበር፡፡) ግን በጣም ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ የቤቱ ሃላፊ እኔ ነበርኩ፡፡ በጣም ሀብታሞች ናቸው፡፡ መኪና አስመጪና ላኪ ነበሩ፡፡ ሴቷ ልጅ ነበረች የቤተሰቦቿን ሀብት የምታስተዳድረው፡፡ ምን ያህል ጊዜ ሰራሽ? አራት ዓመት ከ6 ወር አብሬአቸው ነበርኩ፡፡ ጦርነቱ ሲጀመር ሃብታሞች ስለሆኑ ሁሉን ነገር ትተውት ወጡ፡፡ በመሃል እኔ ቀረሁ፡፡ ልጅቷ ፓስፖርት ልታወጣልኝ በጣም ደክማልኛለች፤ ግን አልተሳካም፡፡ እና ቤቱን ለእኔ ጥለው ወደ ቤሩት ተሳፈሩ፡፡ አካባቢው በጣም አስቀያሚ ነበር፡፡ አሸባሪዎች እንደፈለጉ የሚገቡበት የሚወጡበት ቦታ ነበር፡፡ እዚያ መኖር እንደማልችል አውቄዋለሁ፡፡ የነበርኩባቸዉ ሰዎች ደግሞ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ አሸባሪዎች ይፈልጓቸዉ ነበር፡፡ ያንን ትልቅ ቤት ጥለውልኝ ብቻዬን ተሸክሜው ስለቀረሁ ተጨነቅሁ … መወሰን ነበረብኝ፡፡ በርካታ ቤተክርስያኖች ተቃጥለዋል፡፡ ፈርሰዋል፡፡ የሚሸሸው ክርስቲያኑ ነው፡፡ ፓስፖርት ያለው ይሸሻል፡፡ ፓስፖርት ኖሮት ብር የሌለው ኢትዮጵያዊ አለ---ሁሉም መሸሽ ነው፡፡ እስር ቤት መግባትም አለ፡፡ እኔም እጣ ፋንታዬ ይሄው ሆነ፡፡ በእስር ቤት ውስጥ .. የነበረውን ሁኔታ ንገሪኝ? እስር ቤት አንድ ወር ተቀመጥኩ፡፡ እስር ቤት እኮ የገባሁት ልመጣ አካባቢ ነው ከዛ በፊት በአሸባሪዎች እጅ ወድቄ ስንት ነገር ደርሶብኛል..በአሁኑ ሰዓት በጣም በረዶ ነው፡፡ እስር ቤት አትበይው … ‹‹የምድር ጀሃነም›› ነው፡፡ እዚህ ካዛንቺስ ሆነሽ ፍንዳታ ከተሰማ ተነስተሽ መገናኛ ድረስ ነው የምትሮጪው፡፡ ትራንስፖርት የለም፣ ከተያዙ መያዝ ነው፤ የሚሞተውም ይሞታል፡፡ አሁን እኔ በወጣሁበት ሰዓት ከተማው ላይ ብዙም ጦርነት አልነበረም፡፡ ዳር ዳሩ ላይ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ እንደ አቃቂ ባለ ከከተማው ዳር ነበር የምኖረው፡፡ ከደማስቆ ራቅ ይላል፡፡ በጣም ብዙ ኢትዮጵያውያን ሴቶች በሴተኛ አዳሪነት ይሠራሉ የሚባለው እውነት ነው? ወደው አይደለም ሴተኛ አዳሪ የሚሆኑት፡፡ ፓስፖርት የላቸውም፤ ሊቀጠሩ ሲሄዱ ፓስፖርት ይጠየቃሉ፡፡ ቀጣሪዋ ‹‹አልፈግሽም›› ብላ ልታባርራት ትችላለች ፡፡ መኖር፣ መብላት ስላለባቸው የግድ ለእንደዚህ ዓይነት ህይወት ይዳረጋሉ፤ እዚያ ደግሞ የኢትዮጵያ ቆንስላ የለም፤ ኤርትራውያን እንኳ ቆንስላ አላቸው፡፡ ኤርትራዊ ላይ አንድ ችግር ቢደርስበት ቆንስላው ወደተከራየው ቤቱ ይወስዳቸዋል፡፡ ኢትዮጵያውያን በጣም የሚያሳዝን ነው ኑሯቸው ፡፡ አሁን እንኳን ወደ አገራቸው መምጣት አቅቷቸው በየሜዳው ወድቀዋል፡፡ በጦርነቱ ቤቱ ሁሉ እየፈረሰ ነው፡፡ ተከራይተው የሚኖሩት ንብረታቸውን ማውጣት አልቻሉም፡፡ የሴቶች ህይወት … በቃ ይሄው ነው፡፡ ወደው አይደለም የገቡበት ---- ኢትዮጵያውያኖች ያ ባህል ኖሯቸው አይደለም፤ በችግር ነው፤ አማራጭ በማጣት፡፡ እስር ቤት ከመጣልሽ በፊት..በአሸባሪዎች እጅ ወደቅሽ? በጣም አሰቃቂ ነው … በአሸባሪዎች እጅ ላይ ወደቅሁኝ፡፡ /ሰውነቷ ይንቀጠቀጣል፣ ለደቂቃዎች በዝምታ ቆየች፤ አይኖቿ እንባ አቀረሩ …) አየሽ ሰውነቴን … (ትከሻዋ አካባቢ እያሳየችኝ … የተቃጠለ ገላ …) ምንድን ነው? ሲጋራ ተርኩሰውብኝ ነው … … አሸባሪዎቹ ናቸው እንዲህ ያደረጉኝ--- የት ነው የወሰዱሽ? ቢሄዱት የማያልቅ ምድር ቤት (Underground) አላቸው፡፡ ውስጥ ለውስጥ ተቆፍሮ … የቀለጠ ከተማ ነው፡፡ በአንድ አቅጣጫ ብቻ እንዳይመስልሽ … ወደ አምስትና ከዛም በላይ አቅጣጫ መግቢያ መውጭያ ያለው ነው … የታሰሩ ሰዎች የሚሰቃዩበት፣ የጦር መሳሪያ በየዓይነቱ በብዛት ያለበት … ኑሯቸውም እዛው ነው? አዎ፡፡ ሴቶችም ወንዶችም አሉ፡፡ ብዙ ጊዜ አሸባሪዎቹ አይወልዱም፡፡ ከወለዱ ግን የልጆቻቸው አስተዳደግ አሰቃቂ ነው፡፡ በፊት ለፊታቸው አንገት በቢላዋ እየተቀላ፤ እጅና ጣት እየተቆረጠ … ያንን እያዩ ነው የሚያድጉት፡፡ ወንዶችን በፊንጢጣቸው … ኤሌክትሪክ ይልኩባቸዋል፡፡ ሴቶችን ህፃናቱ ፊት ይደፍራሉ፡፡ … የ3 እና የ5 ዓመት ህፃናት እንዲያዩ እንዲለማመዱ ይገፋፏቸዋል፡፡ የአሸባሪዎቹ ሚስቶች እዚያው አሉ፡፡ እነርሱም ሰውን ያሰቃያሉ፡፡ ሴትን ሴት፤ ወንድን ወንድ ነው የሚያሰቃየው፡፡ ሚስቱ ካሰቃየችኝ በኋላ ‹‹አምጫት›› ብሎ ይደፍረኛል፡፡ ሱዳኖች፣ ናይጄሪያዎች፣ ሴኔጋሎች … ብዙ የአፍሪካ ዜጐች ነበሩ - የሚሰቃዩ፡፡ የተለያየ አደንዛዥ ዕፅ ይሰጡናል፤ በመርፌ የሚወጋ፣ የሚጨስ፣ የሚሸተት … በግዴታ ነበር፡፡ ከዚያ መጋረፍ ነው … ወንዶቹ ብልት ላይና ምላሳቸው ጫፍ ላይ ኤሌክትሪክ ያደርጉባቸዋል፡፡ እኔን … ቦንብ ታጥቀሽ ራስሽን ታጠፊያለሽ ብለውኝ ነበር፡፡ ‹‹ላ … ላ›› አልኳቸው፡፡ ከዛ … የደረሰብኝን ስቃይ … (ረጅም ትንፋሽ) እስቲ የደረሰብሽን ንገሪኝ … … በቃ ተይው ይቅር … (ለመሄድ ተነስታ ተመልሳ በማቅማማት ተቀመጠች) አይዞሽ ንገሪኝ … ስታወሪው ይሻልሻል … ለመናገር ይከብዳል፡፡ የወንድ ልጅን ብልት ቆርጠው አምጥተው “ተጫወችበት” ይላሉ--- በጣም … አስቀያሚ ነው … ተይኝ ባክሽ … በተደጋጋሚ ስትደፈሪ እርግዝና አልተፈጠረም? ሃሃ … (ሳቅ) የሚሰጡኝ መድሃኒትስ … አምፒሲሊን ይሁን … ምን ይሁን አላውቅም ግን ይሰጡኝ ነበር … ስለዚህ እርግዝና የለም፡፡ ስቃይ ሲበዛብሽ … ምንም አትይም … ቁጣ ወይ ደግሞ … “በቃ ራሴን አፈነዳለሁ” አልኳቸው:: ውይ ሳልነግርሽ … ምግብ የለም፣ ውሃ በምንጠይቅ ሰዓት ሽንታቸውን ነበር የሚሰጡን … ሲያሰኛቸው በገላችን ላይ ይሸናሉ፡፡ ትንሽ ውሃ በተለያዩ ማደንዘዣ ዕፆች ቀላቅለው ጠጡ ይሉናል ፡፡ ያን ከሰጡኝ በኋላ የሚያደርሱብኝ ስቃይ አይታወቀኝም … እና “አፈነዳለሁ” ብዬ ተስማማሁ … ወጥቼ ልሙት … አንድ ኢትዮጵያዊ ይህንን እንዳዳረገች ሁሉም ይወቅ ብዬ ወሰንኩ፡፡ ከእንግዲህ ምን ቀረኝ … ብሬን ንብረቴን ወስደውታል፡፡ አማርኛ የማወራው--- ችግሬን የማስረዳው ሰው እንኳን የለም፡፡ እንዲህ እናድርግ ምናምን ብላችሁ ከሌሎቹ ጋር አትማከሩም ነበር? እኔ ከሴቶች ጋር ሳይሆን ከወንዶች ጋር ነበር ይበልጥ የምቀራረበው፡፡ ናይጀሪያኖች፣ ሱዳኖች … ሱዳኖች በእኔ ስቃይ በጣም ተጐድተዋል … ስጮህ ይሳቀቁ ነበር፡፡ በእነሱ ፊት ይገናኙኝ ነበር፡፡ አፍሪካውያኖችን በኤሌክትሪክ አቃጥይ ይሉኝ ነበር፡፡ “ሂጅና አቃጥያቸው”፤ “ሽንትሽን ሽኝባቸው…” እባላለሁ፡፡ እነሱ ጋ ስደርስ በጣም አለቅስ ነበር፡፡ ጣታቸውን … እግራቸውን ይቆርጡባቸዋል፡፡ … ህክምና የለ፤ ደማቸው እየፈሰሰ ነው የሚውሉት … አቃተኝ (ረጅም ትንፋሽ) ምን ያህል ነበሩ? አስራ ሶስት፡፡ ከሞቱት ሌላ ማለቴ ነው---- (ደረትዋን ደጋግማ በእጅዋ ትይዛለች) አቤት ...ሽታው በልብሴ ...በሠራ አካላቴ ጠረኑ ሁሉ..ይመጣብኛል፡፡ ናይጀራዊው ጋ ሄጄ የታዘዝኩትን ስነግረው ..በአረብኛ ‹‹..አድርጊው..ካላደረግሽው አትወጪም፤ እኛንም አታድኝንም..አድርጊው..ለኩሽኝ..›› አለኝ፡፡ አልቻልኩም፤ የመጀመሪያ የጨካኝነት ልምምድ ነበር፡፡ አለቀስኩኝ፡፡ በብዛት ኮኬን እወስድ ነበር፡፡ ስትለኩሺያቸው ቆመው ያዩሽ ነበር? አዎ.. ደስ ይላቸዋል፡፡ .ናይጀሪያዊውን እየለኮስኩት ሳለ “ጭኔ ላይ የምታያት የበር ቁልፍ ናት፡፡ እቺን ይዘሽ መውጣት ትችያለሽ” አለኝ፡፡ እሱን እየለኮስኩ ቁልፉን ወሰድኩት፡፡ አረቡ እያየን አልነበረም፡፡ ናይጄሪያዊው ቁልፉን ከየት አገኘው? ከየት እንዳገኘው መጠየቅም አልፈለኩም፤ ጊዜውም አልነበረኝም፡፡ ማውራት አንችልም ነበር፤ ከናይጀሪያዊው ጋር ልንግባባ የምንችለው በአረብኛ ቋንቋ ብቻ ነው፡፡ በንግግርሽ ውስጥ እንግሊዝኛ ከሰሙ ...ጉድሽ ነው፡፡ የተለየ ቋንቋ እንድትናገሪ አይፈቀድልሽም፡፡ (ንግግርዋን አቋርጣ) ይቅር በለኝ--- አሰቃየኋቸው፡፡ በኤሌክትሪክ ከለኮስኳቸው በኋላ ስላለቀስኩ ..‹‹ለምን ታለቅሻለሽ›› ብለው አሰቃዩኝ፡፡ ‹‹የገነት ፓስፓርት›› የሚሉት አለ፡፡ የገነት ፓስፖርት ... ሰው ገድለው ገነት የሚገቡበት ፓስፖርት፡፡ የራሳቸው የቡድን ፓስፖርት ነው፡፡ ‹‹ነፍስ አጠፋለሁ›› ብዬ ስነሳ ፓስፖርት ተሰራልኝ፡፡ ፓስፖርቱ ምን አለው? ምንም፡፡ የእኔ ስምና የቤተሰቤ ስም ዝርዝር አለው፡፡ አረንጓዴ ነው፡፡ ፎቶ የለውም፡፡ ስትገልጪው ይሄ ብቻ ነው የያዘው መረጃ፡፡ “የገነት ፓስፖርት” ይላል ፅሁፉ፡፡ ፓስፖርቴ ተሰራልኝ፡፡ እላዬ ላይ ቦንብ ካጠመዱልኝ በኋላ የገነት መግቢያ ፓስፓርቴም፣ አብሮ ይታተምልኛል፡፡ ፓስፖርቴ ተሰራ፤ አብሬያቸው እሰግድ ነበር፤ ቁራን እንዴት እንደሚቀራ አስተማሩኝ፡፡ “የዛሬ 15 ቀን ወደ ገነት መሄጃሽ ነው ማረፍ አለብሽ” ብለው ነገሩኝ... እረፍቱ የት ነው …? ‹‹የምድር እረፍት›› ነው የሚሉት፡፡ 15 ቀኑን የሟች ሬሳ በተጠራቀመበት … (ፀጥ አለች) … ሰውነታቸው የተቆራረጠ ሰዎች በብዛት ተገድለው በተጣሉበት … ከነበርንበት ወደ አንድ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ … ሬሳ ውስጥ … ከሙታን ጋር፡፡ ጨካኝ … እንድትሆኝ ነው … እዚያ የጉድጓድ መውጫ በር አለ … ያ … ናይጄሪያዊ የሰጠኝ ቁልፍ መውጫ ነው … እሱ እኮ ከታሰረ ሁለት ዓመቱ ነው … ጦርነቱ ሲጀምር የተያዘ ነው፡፡ እረፍት እንደሚወስዱኝ ሁሉ ያውቃል፡፡ … በዚያ አሰቃቂና ዘግናኝ ቦታ በአጋጣሚ ህይወቱ ያላለፈ ትኩስ ቁስለኛ … (የገደሉት መስሏቸው ትተውት የሄዱት) አገኘሁ፡፡ ለመሞት ጥቂት ደቂቃዎች ነበር የቀረው፡፡ የእረፍቱ ቦታ..... ሱሪ እና አሮጌ ነገር አለበሱኝ፤ ሬሳው ውስጥ ተቀመጥኩ፡፡ … እፀልይ ነበር … ቁልፉን እንዴት ይዘሽው ገባሽ? በማህፀኔ ውስጥ ደብቄ … በምኔም ልደብቅ አልችልም ነበር፡፡ ስፀልይ ሰውየውም ቀና አለ … እጅግ ያሳዝናል … ሰውነቱ ሁሉ የተጠባበሰ ነው … ተበለሻሽቷል፡፡ ይህ ሰው እንደተጋደመ “ሬሳዎቹን … ገለል ገለል አድርገሽ ውጪ” ብሎ አሳየኝ … የደረጃ መወጣጫ … አለው … እሱ ሲወጣ አስፓልት ይገኛል፡፡ እየመጡ አያዩሽም ነበር? በፍፁም አያዩኝም … 15 ቀን ካረፍኩ በኋላ መጥተው ይወስዱኛል … ብቅ ብለው ግን አያዩኝም፡፡ ከዛ ሰው ጋር ተግባባሁ፤ ውሃ … ሲለኝ ሽንቴን ሸንቼ ሰጠሁት፡፡ ህይወቱን ለትንሽ አተረፍኩት፡፡ … በሌሊት በሩን ከፈትን … ተሸክሜ … አወጣሁና ጣልኩት፡፡ እነሱ ለሊት ለሊት ስራ አይሰሩም፡፡ ስራቸው ቀን ነው፡፡ በግርግር ጫጫታ ባለበት ሰዓት እንጂ … ጨለማ ተገን አድርገው እንኳን ሰውን አይደበድቡም፡፡ ቢያስተጋባ ቢሰማብን ብለው ስለሚያስቡ ይፈራሉ፡፡ ሌሊት መጠጣት ነው ሥራቸው፡፡ የቆሻሻ ቱቦ … ስር ለስር … የትና የት የሚደርስ--- ውስጥ ለውስጥ የሚያስኬድ መንገድ መሰለሽ … እንደ ምንም ደረጃውን ተሸክሜው … እየጎተትኩት … ወጥተን ያ ናይጄሪያዊ በሰጠኝ የበለዘ ቁልፍ … ከፈትኩት … ስወጣ አስፓልት ላይ ነው የወጣሁት፡፡ ቅርብ ነው ለከተማው፡፡ ምሽት ላይ ነበር፤ ማንም ዝር አይልም፡፡ ‹‹ስምርዬ›› የሚባል ቦታ አለ፡፡ እንደ አውቶብስ ተራ ዓይነት ነው፡፡ አስፓልቱ ላይ ከወጣን በኋላ … ተሸክሜ ያወጣሁት ሰው … የተወሰነ ቦታ ድረስ እየጎተትኩት ከተማ አካባቢ ስንደርስ አደባባይ ላይ ጥዬው ሄድኩ፡፡ ከወጣሁ በኋላ ደክሞኛል … አሞኛል፡፡ ኢትዮጵያኖችን መጠጋት አልቻልኩም፡፡ ለምን? በጣም አስቀያሚ ሁኔታ ላይ ነበርኩ፡፡ ሀሺሽ ጠጥቻለሁ፣ ጠረኔ በጣም መጥፎ ነው፤ ፀባዬ ከፍቷል፡፡ በዛ ሰዓት የሄድኩት ቤተክርስቲያን ነው፡፡ ፀለይኩ … አለቀስኩ … የት እንደምሄድ አላውቅም፡፡ … ሁሉ ነገር ብርቅ ሆኖብኛል፡፡ መንገድ ላይ ስዘዋወር አንድ ኢትዮጵያዊ አገኘሁ፡፡ ሳናግረው “ሰምተናል ሰምተናል” አለኝ፡፡ ምኑን? አንዲት ኢትዮጵያዊ ተይዛለች መባሉን፡፡ ማን እንደሆነች ግን አላወቅንም ነበር፡፡ በአሸባሪዎች እጅ ወደቀች ሲባል ሰምተናል - አለኝ፡፡ በአገሪቱ ላይ ስልክ የሚባል የለም … አጋጣሚ ሆኖ በነጋታው ወደ ካናዳ የሚሳፈር ልጅ ነበር፤ በጣም አዘነ፡፡ ከዛ ጉድጓድ ከወጣሁ በኋላ ግን በጣም ፈራሁ … የሚያየኝ ሰው ሁሉ የሚያውቀኝ የሚከተለኝ… የሚገለኝ ይመስለኝ ነበር፡፡ ቀን ቀን ስታያቸው ኖሮማል ሰው ስለሚመስሉ፤ ለብሰው ዘንጠው ስለሆነ የሚወጡት … አንድ ሰው አስተውሎ ካየኝ ከእነርሱ መካከል አንዱ ይመስለኝ ነበር፡፡ በአጋጣሚ በዛን ወቅት ደግሞ በዊግ ቁጥርጥር ተሰርቻለሁ … በፀጉሬ ይለዩኛል ብዬ እሰጋም ነበር፡፡ “እባክህ ከአንድ ሱናዳዊና ናይጄሪያዊ የተሰጠኝ መልዕክት አለ … ስማቸው እገሌ ይባላል … ሂጂና ያሉበትን ቦታ ተናገሪ ስላሉኝ እዛ ውሰደኝ” አልኩት፡፡ ናይጄሪያዎች በጣም ጎበዞች ናቸው … እንዴት እንደሚወጣ … ያውቃሉ ----ጥበበኞች ናቸው እና ይሄን ልንገር አልኩት፡፡ የተባለው ቦታ ወሰደኝ፡፡ ... ነገርኳቸው፡፡ ተላቀስን -- ቁልፍ ሰጥቶ ያስወጣኝ የናይጄርያው ወንድም “ኢሾ” ይባላል፡፡ ምን ማድረግ እንዳለብን አወራን፡፡ ቦታው እንደዚህ ዓይነት ቦታ ነው፤ ቁልፉም ይሄው … ‹‹ስጪያቸው እነርሱ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ያውቃሉ ነው ያለኝ” አልኩት፡፡ ቁልፉ ላይ … ሌላ መልዕክት አለው? እንዴ … እንዴት አወቅሽ? --- ቁልፉ ሰፋ ያለ ነው.. በላዩ ላይ በራሳቸው ቋንቋ ፅፈውበታል … ሰጠኋቸውና አወጣጤን ነገርኩት፡፡ አለቀሱ፤ በህይወት የለም ብለው ደምድመው ነበር፡፡ (እንባዋን እየጠረገች) አንድ ኢትዮጵያዊ ከአንድ ሱዳናዊ ጋር አገናኘኝ፡፡ በጣም ባለውለታዬ ነው-- እንደ ነገ ወደ ካናዳ በረራ ነበረው--- ለእኔ ሲል ቀኑን አራዘመ … በሃሺሽና በተለያዩ ሱሶች የተበከለው ደሜ … ባህሪዬን አስከፍቶት ስለነበረ መርዙ ከደሜ እስኪወጣ ድረስ ተቸገርኩ፡፡ ስለዚህ … አስመረመረኝ … ከሰው ጋር ትንሽ ትራቅና ትቀመጥ ተባለ … መድሃኒት ተሰጠኝ፡፡ ያ ያስተዋወቀኝ ያልኩሽ ሰው በሱዳን አድርጌ ወደ ኢትዮጵያ እንድመጣ ነገሮችን ያመቻችልኝ ጀመር፡፡ ሌላ ዳዊት ባህሩ የሚባል ኢትዮጵያዊ (እዛ የሚኖር የአሜሪካ ዜግነት ያለው) … የቻልኩትን ሁሉ እረዳታለሁ … ፓስፖርቷንም በማውቀው ሰው አወጣላታለሁ አለ፡፡ የምንኖረው አንድ አፓርታማ ላይ ነው፡፡ እኔን ይዞ ሲወጣ ሲገባ ያየ ሰው በትኩረት ያየኝ ነበር፡፡ ስወጣ ከእግር ጥፍሬ እስከ ራስ ፀጉሬ ተከናንቤ ነበር የምወጣው፡፡ እዛ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደግሞ አይከናነቡም፡፡ ‹‹አሸባሪ ናት፤ ጥቁር ናት ግን ተከናንባ ነው የምናያት ፈራናት›› ብለው አስጠቆሙኝና እስር ቤት ገባሁ፡፡ የዩኤን ወረቀት ነበረኝ፡፡ የደረሰብኝን ነገር ሁሉ አጫወትኳቸው፡፡ እስር ቤት ውስጥ ስገባ ለእኔ እረፍት ነበር፤ አልተጐዳሁም፡፡ ከእስር ቤት ውጪ ያሉ ኢትዮጵያውያን በየሜዳውና በየመናፈሻው ወዳድቀው ተወንጫፊና፣ ተፈንጣሪ መሳሪያ እየወደቀባቸው ይሞታሉ፡፡ እኔ በቅርብ የማውቃት ልጅ የሞተች አለች፡፡ እኔ እዚህ ስመጣ … አሁንም የሚያስለቅሰኝ እዛ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ሁኔታ ነው … ቢያንስ መቶ ኢትዮጵያውያንን ማምጣት ቢቻል ---

Read 10515 times