Print this page
Saturday, 30 March 2013 15:30

ኃይሌ በ40 ዓመቱ ይሮጣል

Written by 
Rate this item
(11 votes)

በሃዋሳ በስሙ የሚያዘጋጀው ማራቶን ትኩረት እያገኘ ነው በቅርቡ 40ኛ ዓመቱን የሚይዘው ኃይሌ ገብረስላሴ በ “ግሬት ማንችስተር ራን” እንደሚሳተፍ የውድድሩ አዘጋጆች አስታወቁ፡፡ ስለተሳትፎው የተጠየቀው ኃይሌ ‹‹ሩጫ ስለሚያስደስትኝ መሮጤን እቀጥላለሁ፤ መቼ እንደሚያበቃልኝ አላውቀውም፤ ወደ ማንችስተር ተመልሼ ለመወዳደር የምችልበትን እድል መተው አልችልም›› ብሏል፡፡ ኃይሌ በ “ግሬት ማንችስተር ራን” የ10 ኪሎሜትር ሩጫ ለ6 ጊዜያት ሲያንፍ፤ ላለፉት አምስት ተከታታይ ዓመታት የውድድሩ አሸናፊ ነበር፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ዘንድሮ “ኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን” በሃዋሳ ከተማ መካሄዱ ትኩረት እየሳበ ነው፡፡ የውድድሩ አምባሳደር አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ለተሳታፊዎች ባቀረበው በጥሪ ለ20 ዓመታት ካሳለፈው የሩጫ ዘመን በኋላ ዓለምን ወደ አገሩ ኢትዮጵያ ሲጋብዝ በታላቅ ጉጉት እንደሆነ ገልጿል፡፡

የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን በኢትዮጵያ በአውሮፓ እና በአሜሪካ ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የውድድር አዘጋጆች በተሰባሰቡበት ቡድን የሚመራ ሲሆን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀና ቀለሙ ኢትዮጵያዊ ማራቶን ነው ተብሏል፡፡ ከ1200 በላይ ተሳታፊዎች እንደሚኖሩት ከሚጠበቀው ኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ጋር በመያያዝ የግማሽ ማራቶን፤ የ5 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ እና የህፃናት ውድድሮችም ይደረጋሉ፡፡በውድድሩ ኦፊሴላዊ ድረገፅ በቀረበው መረጃ መሰረት በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ተሳታፊ ለሚሆኑ ራጮች የጉብኝት ፕሮግራም የተዘጋጀ ሲሆን የኢትዮጵያን ባህልና ታሪክ ለማስተዋወቅ ታስቧል፡፡ የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ጋር ተያይዞ በሚደረገው የገቢ ማሰባሰብ 200ሺ ዶላር ለእንጦጦ ፋውንዴሽን እንደሚበረከትም ታውቋል፡፡ በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን በሁለቱም ፆታዎች ለሚያሸንፉ አትሌቶች ለእያንዳንዳቸው 12 ወቄት ወርቅ ይሸለማል፡፡

ለውድድሩ መሮጫ የተመረጠችው የሃዋሳ ከተማ ከዓለም አቀፉ የአማተር አትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ጋር በሚደረግ ትብብር በቀጣይ ወራት የእውቅና ሰርተፍኬት ለውድድሩ አዘጋጅነት ይሰጣታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በተያያዘ ዜና ባለፈው ሳምንት በፖላንዷ ከተማ ባይድጎስዝ በተደረገው 40ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ኬንያ 5 ወርቅ በማግኘት ስኬታማ ስትሆን ኢትዮጵያ በግልና በቡድን 10 ሜዳልያዎች በመሰብሰብ ከፍተኛ ውጤት አስመዘገበች፡፡ በሻምፒዮናው አጠቃላይ የውጤት ሰንጠረዥ ኬንያ 5 ወርቅ፤ 3 ብርና 1 ነሐስ በመውሰድ አንደኛ ሆና ጨርሳለች፡፡ ኢትዮጵያ በ3 የወርቅ፤ 4 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች በማግኘት ሁለተኛ ሆና በሻምፒዮናው በአዋቂ ወንዶች 12 ኪሎ ሜትር፤ በአዋቂ ሴቶች ስምንት ኪሎ ሜትር እንዲሀም በወጣት ሴቶች የ4 ኪሎ ሜትር ውድድሮች ኬንያውያን የወርቅ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ውጤታማ ሆነዋል፡፡

የኢትዮጵያው አትሌት ሃጎስ ገብረ ህይወት በወጣት ወንዶች 6 ኪሎ ሜትር ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ ድል አስመዝግቧል፡፡ ከ32 አገራት የተወከሉ 102 አትሌቶች በተሳተፉበት የአዋቂ ወንዶች 12 ኪሎ ሜትር ውድድር በቡድን ውጤት ኢትዮጵያ 1ኛ ደረጃ ስትወስድ አሜሪካና ኢትዮጵያ ተከታታዩን ደረጃ ወስደዋል፡፡ ከ29 አገራት የተወከሉ 97 አትሌቶች በተሳተፉበት የአዋቂ ሴቶች 8 ኪሎ ሜትር ውድድር ደግሞ በቡድን ውጤት ኬንያ 1ኛ ደረጃ ስትወስድ ኢትዮጵያና ባህሬን ተከታታዩን ደረጃ ወስደዋል፡፡

Read 10556 times
Administrator

Latest from Administrator