Saturday, 12 November 2011 07:47

ድራማ የሚመስለው የባለስልጣኑ ጋዜጣዊ መግለጫ

Written by  ኤሊያስ
Rate this item
(0 votes)

እንደ እኔ ቢሆን ኖሮ በመንግስት መገናኛ ብዙሃን ውስጥ ሳይሆን በግል የቴሌቪዥን ጣቢያ ተቀጥሬ ብሰራ ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ግን ምርጫ አልነበረኝም፡፡ የቴሌቪዥንና የሬዲዮ ጣቢያዎች ገና ከመንግስት ንብረትነት አልተላቀቁም፡፡ ከሁሉም ያናደደኝ ደግሞ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው ብሮድካስቲንግ ኤጀንሲ በ2004 ዓ.ም የግል ቴሌቪዥን ጣቢያ ፈቃድ እንደማይሰጥ ገና ክረምቱ ላይ መናገሩ ነው፡፡ በዚህ ተስፋ ቆርጬ ነው መስከረም መባቻ ላይ ኢቴቪ ውስጥ የተቀጠርኩት፡፡ ምን ላድርግ? አውሮፓ በቲቪ ጋዜጠኝነት ለመማር ስወስን እኔ ትምህርቴን እስከማጠናቅቅ አንድ ሁለት የግል ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ይከፈታሉ በሚል ግምት ነበር፡፡ ግን ግምቴ የተሳሳተ መሆኑን የተገነዘብኩት አገሬ ስመለስ ነው፡፡ በንጉሱ ዘመን የተጀመረው አንድ ለእናቱ ብሄራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ራሱን ሦስት ቦታ አባዝቶ (በቻናል) የአየር ሰዓቱን ለብቻው ተቆጣጥሮታል፡፡ ሌላ ምርጫ እንደሌለኝ ገባኝ፡፡ ኢቴቪን ሳላመነታ Join አደረኩት፡፡ ሌላው ቢቀር የተማርኩትን ትምህርት እተገብርበታለሁ ብዬ ነበር የገባሁት፡፡ በእርግጥ ጓደኞቼ አከላክለውኝ ነበር፡፡ “ኢቴቪ የተማርከውን ያስረሳሃል … ይቅርብህ” በማለት ምርጫ ስላልነበረኝ የጓደኞቼን ምክር ሳልቀበል ቀረሁ፡፡ ይገርማል እኮ! ይሄን ሁሉ ሃተታ ለምንድነው የዘበዘብኩት? የዛሬ ወጌ የሚያጠነጥነው በኢቴቪ ዙሪያ ሳይሆን ሙስና ላይ ነው፡፡

ኢቴቪ ውስጥ አዲስ ጋዜጠኛ ስለሆንኩ ከSenior ጋዜጠኞች ጋር እላካለሁ እንጂ እስካሁን ለብቻዬ እንድዘግብ የተላኩበት ሥራ አልገጠመኝም፡፡ በዚህ ደስተኛ አልነበርኩም፡፡ ራሴን (ችሎታዬንና ብቃቴን) መፈተሽ ስለምፈልግ የመጀመሪያ ዘገባዬን መቼ ሰርቼ (አቅርቤ) እያልኩ ስጨናነቅ ነበር፡፡
አለቃዬ አንድ ከፍተኛ የመንግስት ባለሥልጣን ሙስና ነክ መግለጫ እንደሚሰጡ ነግሮኝ ነው ከካሜራማን ጋር የላከኝ፡፡ አንጋፋዎቹ ጋዜጠኞች ለተለያዩ ዘገባዎች ክልል ስለወጡ ነው እንጂ ይሄንን ዕድል ማንም እንደማይሰጠኝ አውቀዋለሁ፡፡ ግን ደግሞ አንድ ነገር አውቃለሁ፡፡ ከልጅነቴ ጀምሮ ዕድለኛ እንደነበርኩ፡፡ አለቃዬ ሥራውን ከሰጠኝ ቅጽበት ጀምሮ የመጀመሪያ ዘገባዬን እንዴት እንደማቀርብ በአዕምሮዬ እያሰላሰልኩ ነበር፡፡ የቲቪ ዘገባዎችን ማራኪና ቀልብ የሚገዙ የማድረግ ዕቅድ ነበረኝ - በግሌ፡፡ ለዚህ ደግሞ የአውሮፓ የጋዜጠኝነት ትምህርቴ ያግዘኛል፡፡ በእርግጥ ዕቅዴ ዕውን የሚሆነው አለቃዬ መልካም ፈቃዱ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ እሱ ከደበረው ግን ደበረው ነው፡ የፈለገ አገር የሚነቀንቅ ፕሮግራም ብሰራ እንኳ ካልተመቸው ይቀራል፡፡ እኔ ግን ይሄ ሁሉ ነገር አላሳሰበኝም፡፡ ዋናው ትኩረቴ ሥራው ላይ ነበር፡፡
በሙስና ዙሪያ መግለጫ ይሰጣሉ የተባሉት የመንግስት ባለስልጣን ዘናጭ ቢሮ ውስጥ ገባን - ከካሜራማኑ ጋር፡፡ ለካስ የግል ጋዜጠኞችም ተጠርተዋል፡፡ 4 የሚደርሱ ቢሮው ውስጥ ተቀምጠዋል፡፡ ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ሁለት የውጭ ጋዜጠኞች ገቡ፡፡ እነሱ ግን ወዲያው ተባረሩ፡፡ “ይሄ የእኛ ገበና ነው፤ እናንተን አይመለከታችሁም” በሚል ሰበብ፡፡ ምን ማለት እንደሆነ ግን አልገባኝም፡፡ ጋዜጠኞቹ ቅር እያላቸው ሳይወዱ በግድ ወጡ፡፡ አንዳንድ የግሉ ፕሬስ ጋዜጠኞች ግን ባለሥልጣኑ የእንግሊዝኛ አፍ ስለማይደፍሩ ነው ብለው ሲያሟቸው ሰምቻለሁ፡፡ ሃሜቱ ባለስልጣኑ ጆሮ እንዳልደረሰ ግን እርግጠኛ ነኝ፡፡ ለምን ቢባል - ቢደርስማ ኖሮ እኛንም ያባርሩን ነበር፡ ሰውዬው ስሜታዊ ይመስላሉ - ከአነጋገራቸው፡፡ እንዳልኳችሁ አጀንዳው ሙስና ነው፡፡ ባለስልጣኑ የቀድሞ አለቃቸውን የሙስና ሃጢያት አጣፍጠው እየነገሩን ነው - ልክ እንደ ወሬ ወይም እንደ ሃሜት፡ “የሚገርማችሁ የዚህን መ/ቤት የቀድሞ ሥራ አስኪያጅ የሙስና ወንጀል ለየት የሚያደርግው “ሞስኖ” ባገኘው ገንዘብ የታላቁ ህዳሴ ግድብን ቦንድ መግዛቱ ነው” እያሉ ከትከት ብለው ሳቁ፡፡ ጋዜጠኞችም በሳቃቸው አጀቧቸው፡፡ “ትንሽ ቦንድ እንዳይመስላችሁ … የ100ሺ ብር ነው .. ይሄ ብቻ አይደለም በ2002 ዓ.ም ምርጫ በሚወዳደርበት ወረዳ ሃይለኛ ተፎካካሪ ገጥሞት ስለነበር በሙስና ካገኘው ገንዘብ 85ሺ ብር አውጥቶ ለቅስቀሳ ዘመቻ አውሎታል … አይገርምም ቀደም ብንል ኖሮ ይሄን ሰው እናድነው ነበር” አሉ በተቆጨ ስሜት፡፡ ነገሩ ግራ አጋባኝ፡፡ ሰውየው የሚናገሩት ከምራቸው ነው? በዚያ ላይ ሥልጣናቸው ምን እንደሆነ የሚገልፅ ነገር አላየሁም- በደፈናው “የመንግስት ባለስልጣን” ይላል - በራቸው ላይ የተለጠፈው ጽሑፍ፡፡ ምን ማለት ነው? መግለጫቸውን ሲጨርሱ ሃላፊነታቸውን እጠይቃቸዋለሁ ብዬ አስገራሚና አስቂኝ ንግግራቸውን እከታተል ገባሁ፡፡ በመጨረሻ የሙስና ተጠርጣሪው በሞያሌ በኩል ከአገር አምልጠዋል አሉ፡፡ ያለ ነገር አላፌዙም አልኩኝ -በሆዴ፡፡
የመንግስት ባለስልጣኑ ተጠርጣሪው ወንጀለኛ ፀረ-ልማት መሆናቸውን አሰመሩበትና የፓርቲያቸውን ዕቅድ ነገሩን፡፡
ፓርቲያቸው ኢህአዴግ እስከ ቀጣዩ ምርጫ ሙስናን በሁለት ዲጂት ለመቀነስ ዕቅድ እንዲያዘ፤ ዕቅዱንም እውን ለማድረግ እንደሚረባረብ በወኔና በስሜት ተሞልተው ነገሩን፡፡ ሹመታቸው ያልታወቀው የመንግስት ባለሥልጣን በዚሁ መግለጫቸውን ቋጩ፡፡ አሁን ጋዜጠኞች ጥያቄ እንድንጠይቅ ዕድል ተሰጠን፡፡ አንደኛው የግል ፕሬስ ጋዜጠኛ ደፋር ጥያቄ ጠይቆ ባለስልጣኑንም አደፋፈራቸው፡፡
“ኢህአዴግ በተለመደው የአፈፃፀም ችግር እስከ ቀጣይ ምርጫ ሙስናን በሁለት ዲጂት መቀነስ ባይሆንለትስ?”
“ሥልጣኑን በገዛ ፈቃዱ ይለቃል!”
ሁሉም ቀና ቀና እያለ ባለስልጣኑ ላይ አፈጠጠ፡ ይኼኔ ነው የተናገሩትን ያሻሻሉት፡፡
“ፓርቲዬ ባይለቅ እንኳ እኔ በፈቃዴ ስልጣኔን እለቃለሁ!” አሉ በእርግጠኝነት!
ለነገሩ ይሄም ቀልድ አይደለም፡፡ እስከዛሬ ማን እንዲህ ደፍሮ ተናግሮ ያውቃል? ቀድሞ ነገር ከሥልጣን የመልቀቅ ጉዳይ መች ተነስቶ ያውቃል? (አንዴ ጠ/ሚኒስትሩ ብለው ነበር ግን ረሱት!)
ወደ ቴሌቪዥኑ ጣቢያው ስመለስ ሪፖርቱን እንዴት ጉደኛ አድርጌ እንደማቀናብረው እያሰብኩ ነበር፡፡ ዘገባውን ፀረ ሙስና ኮሚሽን ስፖንሰር ቢያደርገውስ አልኩና … ከሙስና ቢቆጠርብኝስ ብዬ ተውኩት፡፡ (ፀረሙስና ኮሚሽን ራሱ ጋማዬን ቢለኝስ? የማን አለህ ይባላል!) ቀጥሎ ደግሞ አጃቢ ሙዚቃ ላሰራለት አሰብኩ-ለሙስና ዘገባዬ፡፡ ክፋቱ ግን ጊዜ የለም፡፡ ከሁለት ሰዓት በኋላ አየር ላይ የሚውል ዘገባ እንደሆነ ከአለቃዬ ተነግሮኛል፡፡
የመንግስትና የህዝብ ሃብት በሙስና ዘርፈው በሞያሌ በኩል አገር ጥለው ጠፉ የተባሉትን ሥራ አስኪያጅ የተመለከተውን ዘገባ፤ ከምክትል ስራ አስኪያጁ ጋዜጣዊ መግለጫ ጋር እያቀናበርን ምስሎች ጨማምረን አሰናድተነዋል-ከኤዲተሩ ጋር፡፡
ይሄ አስገራሚ የሙስና ዘገባ ለኢትዮጵያ ህዝብ ሊሰራጭ ጥቂት ደቂቃዎች ብቻ ናቸው የቀሩት፡፡ የመጀመሪያ ዘገባዬ በቲቪ የሚተላለፍበትን ቅፅበት ለማየት ተጣድፌአለሁ፡፡ አስሬ ሰዓቴን አያለሁ፡፡ በዚህ መሃል ነው የአለቃዬ ፀሃፊ ስቱዲዮ ድረስ መጥታ የጠራችኝ፡፡ በሙስጤ እየተነጫነጭኩ አለቃዬ ቢሮ ሄድኩኝ፡፡ አለቃዬ ያለ ወትሮው እንክብካቤ አበዛብኝ፡፡ አስቸኳይ ሥራ ሊያዘኝ ስለመሰለኝ “ዘገባዬ ሲተላለፍ ሳላይ ንቅንቅ አልልም” የሚል መልስ አዘጋጅቼ ነበር፡፡ ነገሩ ግን ሌላ ነበር፡፡ በህልሜም በእውኔም ያላሰብኩት ዱብዕዳ!
“ዘገባው አሁን መተላለፍ አይችልም” አለ-አለቃዬ
“ለምን? ብዙ የለፋሁበት እኮ ነው” ሰበብ ደረደርኩ
“ምን መሰለህ መግለጫውን የሰጡት ባለስልጣን አምልጠዋል!”
“ምን …ወዴት … ለምን?”
“ከቀድሞው አለቃቸው ጋር በሙስና ተጠርጥረው ሊያዙ ሲሉ ሾለኩ ነው የተባለው”
“የት? ሞያሌ?”
“አዎ መያዛቸው ግን አይቀርም”
“ታዲያ ይሄንንም አብረን እንዘግበዋ!”
“ያምሃል … ገና ሳይጣራ … አይ የልጅ ነገር”
አለቃዬ አናደደኝና ቢሮውን ጥዬው ወጣሁ፡ ከዘገባው አለመተላለፍ የበለጠ ያበሸቀኝ “የልጅ ነገር” ያለው ነው፡፡ አሁን የልጅ ነገር የሚያስብል ምን ሰራሁ? የግል ቴሌቪዥን ጣቢያ በቅርቡ ባይጀመርም ሥራ መልቀቄ ግን አይቀርም፡፡

 

Read 4002 times Last modified on Saturday, 12 November 2011 08:00