Monday, 27 May 2013 14:39

“የቡድንና የቡድን አባቶች…”

Written by  ኤፍሬም እንዳለ
Rate this item
(2 votes)

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

የአፍሪካ አገሮች ጠበል ጠዲቅ ‘አብረው መቃመስ’ ከጀመሩ ‘ፊፍቲ’ ሞላቸው አይደል! እሰይ…ሌላ ‘ፊፍቲ’ ዓመት ያሰንብታቸው፡፡ ታዲያ ለብዙዎቹ ይቺ የሀበሻ ቅኔ ትተላለፍኝማ! መከራ ሲመጣ አይነግርም አዋጅ ሲገሠግስ አድሮ ቀን ይጥላል እንጂ… አዎ…ያነሳ ቀን መልሶ እንደሚያፈርጥ ማወቅ አሪፍ ነው፡፡ (የጋዳፊና የሙባረክ ችግር ይሄን ነገር ተርጉሞ የሚያቀርብላቸው ያለመኖሩ ነው፡፡ ልክ ነዋ! አይደለም ሰው…‘ጫፍ’ ላይ ያለ ድንጋይም ቀኑ ሲደርስ ተንከባሎ ለኮብልስቶን ጥሬ ዕቃ ይሆናል፡፡) እናማ…ጥያቄ አለን…‘የሚደርሰን’ ጠበል ጠዲቅ ካለ ይድረሰና! ዘላላም እኮ ‘እዛ ላይ’ አይከረምም፡፡ የእኛ ወዳጅነት የሚፈለግበት ጊዜ ይመጣላ! ሲወጡ የተጠየፉን ሲወርዱ “ማሬ…” “ወርቄ…” አይነት ነገር ጊዜው አልፎበታል፡፡

መከራ ሲመጣ አይነግርም አዋጅ ሲገሰግስ አድሮ ቀን ይጥላል እንጂ፣ የሚባል ነገር አለ፡፡ አዎ፣ እዚቹ ክፍለ አሀጉራችን ውስጥ በአብዛኛው የሚያነሳውም፣ የሚጥለውም ‘ቀን’ ነው፡፡ የተጠቀሱት ነገሮች እንደ ‘ጎልድን ጁብሊ’ አከባበር ግለሰባዊ አስተዋጽኦ ይታይልንማ! እኔ የምለው… ድሮ ‘ካዛብላንካ ቡድን’ ምናምን የሚባሉ ቡድኖች ነበሩ አይደል! ዘንድሮ ‘ምናምኖፎን…’ ነገር የሚባሉ “የቡድንና የቡድን አባቶች” ነገር አለ እንዴ! አሀ…ስለሚመለከተን መጠየቅ አለብና! እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ድሮ ለኳስ ቡድን ሲመሰረት አሪፍ ዘዴ ነበረው፡፡ ሁለት ልጆች ይያዛሉ፣ ስም ይከፋፈሉና የቡድን አባቶች ዘንድ ይሄዳሉ፡ “የቡድንና የቡድን አባቶች…” “ከምንና ከምን?” “ከሰማይ በራሪ ከምድር ተሽከርካሪ…” “የሰማይ በራሪ፡፡”

አለቀ፡፡ ቡድን ተመሰረተ፡፡ ጨዋታው ሲያልቅ ቡድን አይኖርም፡፡ ምነው እንዲህ አይነቱን ‘የመንደር ልጅነት’ና ‘የሰንበቴ ተጣጪነት’ የቡድን መመስረቻ ክራይቴሪያዎች የማይሆኑበት ዘመን በመጣልንማ! እናላችሁ…ለጨዋታው ብቻ የሚሆን መቧደን ያለበት ዘመን በመጣልን የምንልበት ዘመን ደርሰናል፡፡ በጎጥና በመንደር እየተቧደንን ሉሲ እንኳን “አሜሪካ ይቺን ታህል ዓመት ቆይቼ እስክመጣ እንዲሀ ሆነው ይጠበቁኝ!” ብላ ሳትታዘበን አትቀርም፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…የዚህ አገር ኳስ አደጋገፍ ግራ እየገባን ነው፡፡ አለ አይደል…ስታዲየም ግጥም ብሎ ስለሞላ እኮ ሁሉም የኳስ አፍቃሪ ነው ማለት አይደለም፡፡ ‘ኳስ አፍቃሪ’ መሆን ማለት እኮ…አለ አይደል…በየስድስት ወሩ ሌሊት አሥራ አንድ ሰዓት ለትኬት መጋፋት ሳይሆን መንገድ ላይ በጨርቅ ኳስ የሚደረጉ ግጥሚያዎችን እንኳን የሚያይ አይነት ማለት ነው፡፡ ዋናው ጉዳዩ ከ‘ቡድኖች’ ጋር ሳይሆን ከእግር ኳስ ስፖርት ነው፡፡ ስሙኝማ…ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…ዘንድሮ አብዛኞቻችን ኳስ አፍቃሪዎች ሳንሆን ‘የቡድን ደጋፊዎች’ ነን፡፡

የኳስ ዓለም በሁለትና በሦስት የእንግሊዝ ቡድኖች ላይ የተገደበ ሲሆን… የምር ያጠያይቃል፡፡ “የቀበሌያችን ልጆች…” “የከፍተኛችን ልጆች…” ምናምን እየተባለ እኮ ኳስ ለምን ክብ እንደሆነች ግራ የሚገባቸው ሁሉ ወጥተው ይደግፋሉ፡፡ እነዚህ ‘የቡድን ደጋፊዎች’ እንጂ ‘የኳስ አፍቃሪዎች’ አይደሉም፡፡ እናማ… በቡድን ስሜትና በኳስ ማፍቀር ስሜት የሚሰጡት ድጋፎች ይለዩልንማ! ዘንድሮማ…አንዳንዶች ‘ዘር መቆጣጠር’ን ኳስ ውስጥ ሊያመጡት ሲሞክሩ ማየት…አለ አይደል…የምር አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ በማለዳው ‘ሀይ’ ካልተባለ በኋላ መዘዝ ይመዛል፡፡ አደባባይ ቆሞ አበጀሁ ቢላችሁ ይህ ባለጊዜ ምን ትሉታላችሁ፣ የሚሏት ነገር አለች፡፡ የሰላም፣ የወንድማማችነት ተምሳሌት በሆነው የተቀደሰው የኳስ ሜዳ በቡድን ድጋፍ እየገቡ “አበጀሁ!” የሚሉ አሉ ይባላል፡፡

ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… ‘ቦተሊካው’ም እንዲሁ ነው፡፡ ‘የቡድኖች’ አበዛዝ! ልክ ነዋ…“በፖለቲካ ድርጅቴ የመጣ በዓይኔ የመጣ…” የሚለውን አብዛኛውን “ለመሆኑ የፖለቲካ ድርጅትህ ምን አይነት የትምህርት ፖሊሲ አለው?” ብላችሁ ጠይቁትማ! መጀመሪያ… “በቃ፣ ትምህርት ቤቶች መክፈትና አስተማሪ መቅጠር ነዋ! ሌላ ምን ጣጣ አለው…” ሊላችሁ ይችላል፡፡ እና የፖተሊካ ድርጅት ካርድ የ‘ቡድን አባልነት’ን እንጂ በፖለቲካ ድርጅቱ ፖሊሲዎች (ፖሊሲዎች ካሉት) እንደማያሳይ ልብ ይባልልንማ! በጎሉ አግዳሚ አርባ ሜትር ያህል ሽቅብ የሄደችውን ኳስ “ይቺ ኳስ ጎል የምትሆነው መቼ ነው?” ሲባል “ጎሉ ሲያዛጋ…” ያለው ሰውም የቡድን ደጋፊ ነው፡፡ (ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አልፎ፣ አልፎ አንዳንድ ስፖርት ጋዜጠኞቻችን የሚጠቀሙት አዘጋገብ ላይ…አለ አይደል…የማይመቹኝ ነገሮች አሉ፡፡

እንደው ዜናዎቹ፣ ትንተናዎቹ ምናምን ላይ የሆነ ወንፊት ቢጤ አበጁላቸውና ፍሬ ፍሬውን ለእኛ፣ ገለባ ገለባውን ለቅርጫት አድርጉልንማ! እግረ መንገዴን…የአገርና የዓለምን እግር ኳስ በደንብ የሚያውቅ — የኢንተርኔቱን ‘ከት ኤንድ ፔስት’ ማለቴ አይደለም! — አንድ የስፖርት ጋዜጠኛ “ኢትዮዽያ ሦስተኛ አፍሪካ ዋንጫ በላች የሚባለው ፊክሺን ነው…” ብሎ ክርክር ሊገጥመው እንደሞከረ ሲነግረኝ ነበር፡፡) “የቡድንና የቡድን አባቶች” “ከምንና ከምን?” “ከሰማይ በራሪ ከምድር ተሽከርካሪ” “የሰማይ በራሪ…” በቃ አለቀ፡፡ የቡድን አባል ለመሆን ተጨማሪ ‘ክራይቴሪያ’ አያስፈልግም፡፡ ይቺን ስሙኝማ…የአሁኖቹ ሳይሆን የ‘በፊተኛዎቹ’ ቡናና ጊዮርጊስ ሲጫወቱ በግራ ጥላ ፎቅ የገባ አንድ ተመልካች ኳሷ በየትኛውም አቅጣጫ በሄደች ቁጥር ይዘላል፣ ይጮሀል…ምን አለፋችሁ… የሚሆነውን ያሳጣዋል፡፡ ከብዙ ደቂቃዎች በኋላ አጠገቡ ወዳለው ሰው ተጠግቶ ምን ብሎ ቢጠይቀው ጥሩ ነው… “ቡኒ ካናቴራ የለበሰው ቡድን ስም ማነው?” ሰውየውም “ቡና” ሲል ይመለስለታል፡፡ ሰውየው ዝላዩን ቀጠለ፡፡

ትንሽ ቆይቶ እንደገና ወደሰወዬው ተጠግቶ ምን ብሎ ይጠይቃል መሰላችሁ…“ቢጫ የለበሰው ቡድን ስሙ ማነው?” ሰውየው ብሽቅ ብሎ ምን ብሎ መለሰለት መሰላችሁ…“ጠጅ!” (በ‘እውነተኛ ታሪክነት’ ይመዝግብልንማ፡፡) ሰውየው ያው ዝላዩን ቀጠለ፡፡ እናላችሁ…እንዲህ አይነት ‘የኳስ አፍቃሪ’ም ‘የቡድን ደጋፊ’ም ሳይሆኑ እንደ ጭቃ ሹም የሚቃጣቸው አሉ፡፡ ስሙኝማ…እግረ መንገዴን…ስለ ‘ቡድን ደጋፊነት’ ስናወራ ምን ይታየኛል መሰላችሁ…“ሁለት ጉድጓድ ያላት አይጥ አትሞትም” የሚለው አባባል፡፡ እንደምናወራው ሰው ‘ዲ.ኤን.ኤ.’ የ‘ቡድን ድጋፋችን’ ከአየሩ ጋር የምናዛምድ መአት ነን፡፡ የለየለት ቅሽምናው ያለው ደግሞ እኛ ዘንድ ነው፡፡ እናማ…አስቸጋሪ ጊዜ ላይ ነን፡፡

ልቤ ተሸበረ ከሩቅ ስትጣሪ ሰማሁሽ አገሬ ስንቱን ብሶት ላውራሽ እናቴ ዘርዝሬ፣ ይሉ ነበር፡፡ እናማ…የቡድናዊ አመለካከት ብሶታችንን እያበዛው ነው፡፡ ከበቂ በላይ ብሶቶች የሌሉን ይመስል የዚህ አይነት ‘ፕሪሚቲቭ’ አስተሳሰብ…‘የሰሞኑ አጄንዳ’ ሲሆን ያሳዝናል፡፡ ‘ዘ ሳይለንት ማጆሪቲ’ ዝም ማለቱ አለማወቅ ሳይሆን ነገርዬው… ሽምብራውን ዘርተን እሸቱን ስንበላ አወይ የእኛ ነገር ሁልጊዜ ጥርጨጠራ ሆኖበት ነው፡፡ የሚያምነን ጠፋ፣ የምናምነው ጠፋ! “የቡድንና የቡድን አባቶች…” መባባል በጎጥ፣ በወንዝ ልጅነት፣ በ‘ጠበል ጠዲቅ’ ተጣጪነት…ምናምን የማይሆንበትን ዘመን ያፍጥልንማ! ደህና ሰንብቱልኝማ!

Read 4709 times