Monday, 27 May 2013 15:13

የቢልቦርድ ሽልማት ገበያ ያሟሙቃል ተባለ

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(0 votes)

ከሳምንት በፊት ላስቬጋስ ከተማ ውስጥ በሚገኘው ኤምጂኤም ግራንድ የተካሄደው የቢልቦርድ ሚውዚክ አዋርድ ስነስርዓት ከ12 ዓመታት በኋላ ከፍተኛውን የቲቪ ተመልካች እንዳገኘ ታወቀ። በካንትሪ ሙዚቃ ስልቷ የምትታወቀው ቴይለር ስዊፊት፤ ስምንት የቢልቦርድ ሽልማቶችን በመሰብሰብ ከፍተኛውን ስኬት አስመዝግባለች፡፡ በሌላ በኩል በቢልቦርድ ሚውዚክ አዋርድ ለሽልማት መታጨት እና ማሸነፍ ገበያ እንደሚያሟሙቅ የቢልቦርድ መፅሄት ዘገባ አመልክቷል፡፡ በቢልቦርድ ሚውዚክ አዋርድ ምሽት ላይ 16 አርቲስቶች ለሦስት ሰዓታት የዘለቀ የሙዚቃ ዝግጅት አቅርበዋል፡፡ የቢልቦርድ ሚውዚክ አዋርድ በ45 የሽልማት ዘርፎች ለአሸናፊዎች ሽልማት የሚሰጥበት ሲሆን ከሳምንት በፊት በኤቢሲ ጣቢያ የነበረውን የቀጥታ ስርጭት በሰሜን አሜሪካ 9.7 ሚሊዮን ተመልካቾች ተከታትለውታል፡፡

ይህ የተመልካች ብዛት ከ12 ዓመታት በኋላ ከፍተኛው ቁጥር ሆኖ ሲመዘገብ ከባለፈው አመት 28 በመቶ እድገት እንዳሳየ ተጠቁሟል፡፡ ብዙ ሽልማት በመሰብሰብ የተሳካላት ቴይለር ስዊፍት የዓመቱ ምርጥ አርቲስት፤ የአመቱ ምርጥ ሴት አርቲስት እና ምርጥ የካንትሪ ሙዚቀኛ በሚሉ ዘርፎች ተሸልማለች፡፡ ሪሃና እና ጎትዬ እያንዳንዳቸው 4 ፤ ማዶና እና ኒኪ ማናጅ እያንዳንዳቸው 3፤ እንዲሁም ጀስቲን ቢበር፤ ጄና ሪቬራ፤ ባወር እና ቶክ ማግ እያንዳንዳቸው 2 የቢልቦርድ ሽልማቶችን ተቀብለዋል፡፡ ጀስቲን ቢበር የቢልቦርድ አዋርድ ልዩ ሽልማት ማይልስቶን አዋርድን አግኝቷል፡፡

ወደ ሙዚቃ ኢንዱስትሪው ከገባች ገና ስድስት አመት ብቻ ያስቆጠረችው ቴይለር ስዊፍት፤ በመላው ዓለም 26 ሚሊዮን የአልበሞቿን ቅጂዎች ከመሸጧም በላይ 75 ሚሊዮን ዜማዎቿ በኢንተርኔት ዲጅታል ገበያ ተቸብችበዋል፡፡ በአጭር የስራ ዘመኗ ባገኘችው ስኬትም 165 ሚሊዮን ዶላር አካብታለች፡፡ በርካታ የሙዚቃ ሽልማቶችን የሰበሰበችውና 7 የግራሚ ሽልማቶችን ያገኘችው ቴይለር፤ ከቢልቦርድ ሽልማቶቿ በኋላ ከፍተኛ የገበያ መነቃቃት ሊኖረው እንደሚችል ቢልቦርድ መፅሄት አብራርቷል፡፡ ከሰባት ወር በፊት ለገበያ ያበቃችው አዲስ አልበም ‹ሬድ›ሲሆን በመላው ዓለም 5.8 ሚሊዮን ቅጂ ተሰራጭቷል፡፡

Read 1850 times