Monday, 27 May 2013 15:21

አፍሪካና ሃምሳዎቹ የነፃነት አመታት የዘመን ትውስታዎች

Written by  አልአዛር ኬ
Rate this item
(0 votes)

የአፍሪካ የፀረ ቅኝ አገዛዝ ትግልና የነፃነት ገድል ተመዝግቦ በሚገኝበት የታሪክ መጽሀፉ ውስጥ የ1960ዎቹ አመታት ልዩና ሰፊ ምዕራፍ ይዘዋል። እነዚህ አመታት በእልህ አስጨራሽ መራራ የትግልና አስደናቂ የድል ታሪኮች የተሞሉ የአፍሪካ የመጀመሪያው የነፃነት ማዕከል አመታት ተደርገው ይቆጠራሉ፡፡ ምንም እንኳ እነዚህ አመታት ታሪከኛ አመታት ተብለው በታሪክ መዝገብ ውስጥ ይስፈሩ እንጂ የአፍሪካ የነፃነት ፀሀይ በወቅቱ ወጥታ ትታይ የነበረው በግማሹ ብቻ ነበር፡፡ ያኔ እጅግ መራራና እልህ አስጨራሽ የፀረ-ቅኝ አገዛዝ ትግልና ይህን ያህል ይሆናል ተብሎ በቁጥር ተሠፍሮ የማይነገር የህይወትና የአካል መስዋዕትነት ከፍለው ከምዕራባውያን የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ነፃነታቸውን መቀዳጀት የቻሉት የአፍሪካ ሀገራት ሠላሳ አንድ ብቻ ነበሩ፡፡ በሀያ ሶስት ሀገራት የሚገኙ በሚሊዮን የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ግን ያኔ ከቅኝ አገዛዝ ለመላቀቅና ነፃነታቸውን ለመጐናፀፍ ጦር ሠብቀው ዘገር ነቅንቀው በሀገራቸው ጫካና በረሀ ውስጥ የመረረ የነፃነት ትግል ውስጥ ተጠምደው ነበር፡፡ ክዌሜ ንከሩማህን የመሳሠሉ አፍሪካውያን የበርካታ ልጆቿን ደምና አጥንት ገብራ ነፃነቷን ጠብቃ የኖረችውን ኢትዮጵያን የትግልና የነፃነት አርአያ በማድረግ በ1950ዎቹ አመታት የፀረ-ቅኝ አገዛዝና የነፃነት ትግላቸውን በየሀገሮቻቸው ማቀጣጠል ችለዋል፡፡

በዘመኑ ከነበሩት አፍሪካውያን የፀረ ቅኝ አገዛዝ ታጋዮች መካከል ግንባር ቀደምና ስመጥር በነበረው ክዋሜ ንክሩማህ የተመራው የጋናውያን የነፃነት ትግል ጐልድ ኮስት በመባል ትጠራ ለነበረችው ሀገራቸውና ለእነሱም በ1957 ዓ.ም ከእንግሊዝ ቅኝ አገዛዝ ነፃነታቸውን አስገኝቶላቸዋል፡፡ እንደ ክዋሜ ንክሩማህ ሁሉ በሊወፖልድ ሴዳር ሴንጐር፣ በሁፌት ቧኝ፣ አህመድ ሴኩቴሬ፣ ሞዲቦ ኬታ፣ ሲልቫነስ ኦሊምፒዎ ጂሊየስ ኔሬጌ፤ ጆሞ ኬንያታ፣ ካሙዙ ባንዳና በመሳሠሉት የተመራው የነፃነትና የፀረ ቅኝ አገዝዝ ትግል የማታ ማታ ፍሬውን አፍርቶ ከ1960ዎቹ መጀመሪያ ጀምሮ ባሉት ጥቂት አመታት ውስጥ ሠላሳ አንድ የአፍሪካ ሀገሮችን የነፃነታቸውን ጌታ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል፡፡ የፀረ-ቅኝ አገዛዝ ትግሉን በየሀገሮቻቸው በዋናነት የመሩት እነኝህ ታጋዮች ከነፃነት በሁዋላም ሀገሮቻቸውን የመምራት ከባድ ሀላፊነት የወደቀው በእነሱው ላይ ነበር፡፡ ክዋሜ ንክሩማህ የመጀመሪያው የጋና ፕሬዚዳንት ሲሆን አህመድ ሴኩቱሬ የጊኒ ሞዲቦ ኬታ የማሊ ሊወፖልድ ሴንጐር የሴኔጋል፣ ሲልቫነስ ኦሊምፒዎ ደግሞ የቶጐ የመጀመሪያው ፕሬዚዳንቶች ለመሆን ችለዋል፡፡ ኬኔት ካውንዳ የዛምቢያ የመጀመሪያው መሪ መሆን ሲችሉ፣ ጆሞ ኬንያታ የኬንያን ጁልየስ ኔሬሬ ደግሞ የታንዛንያን የመጀመሪያ የፕሬዚዳንትነት መንበር ተረክበዋል፡፡ ካሙዙ ባንዳም በበኩላቸው የማላዊን የመጀመሪያ የፕሬዚዳንትነት ስልጣን ለመረከብ ቻሉ፡፡

እነዚህ መሪዎች በፀረ-ቅኝ አገዛዝ ትግሉ ወቅት የተጫወቱት ሚና ከተሸከሙት የመጀመሪያ የመሪነት ሀላፊነት ጋር ተዳምሮ የአፍሪካ መስራች አባቶች The founding fathers የሚል ቅጣያ መጠሪያ ሊያተርፍላቸው በቅቷል፡፡ እነዚህ መሪዎች ነፃነታቸዉን ለማስመለስ ከቅኝ ገዢዎች ጋር ነፍጥ አንግበው የጦር ሜዳ ትግል የገጠሙትን አፍሪካውያን ወድንሞቻቸውን ይህንኑ ትግላቸውን የበለጠ ለመደገፍና በአለም አቀፍ የፖለቲካና የኢኮኖሚ መድረክ ላይ አፍሪካ ተገቢውን ቦታ እንድትይዝና ድምጿም ተደማጭ እንዲሆን ለማድረግ ሲያካሂዱት የነበረው ህብረት የመፍጠር ትግል የማታ ማታ ግቡን መቶ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ለመመስረት መብቃታቸው በአፍሪካ የወንድማማችነት፣ የትብብርና፣ የአንድነት የትግል ታሪክ ውስጥም ጉልህ ስፍራ እንዲይዙ አስችሏቸዋል፡፡ በያዝነው ግንቦት ወር በ1963 ዓ.ም ከቅኝ አገዛዝ ነፃ የወጡ የሰላሳ አንድ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎችና ተወካዮች አዲስ አበባ ውስጥ ተገናኝተው ባደረጉት ስብሰባ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን መሠረቱ፡፡ የአፍሪካ አንድነተ ድርጅት በሀምሳ አመት የእድሜ ዘመኑ በርካታ በርካታ ውጣ ውረዶችን አሳልፎ አስቸጋሪና ጠመዝማዛ መንገዶችን ተጉዞና በርካታ ስኬቶችንና ውድቀቶችን አጣጥሞ እነሆ ዛሬ ለአፍሪካ ህብረትነትና የምስረታ የወርቅ ኢዩቤልዩ በአሉን በተወለደባት ከተማ በአዲስ አበባ ለማክበር በቅቷል፡፡

ምንም እንኳ ይዘታቸውን መጠናቸው የፈለገውን ያህል ቢለያይ የልደት በአሎች ናቸው። የልደት በአሎች የመጀመሪያም ሆነ የመጨረሻ ዝክራቸው አንዱ የአንዱን እግር ተከትሎ ያለማቋረጥ የሚፈሰው የዘመን ጅረት ነው፡፡ እናም በእያንዳንዱ የልደት በአል ላይ የትናንትናና የኮትናንት ወዲያ የትዝታ ማህደር የትዝታ ሙዳይ መፈከቱ ከቶም አይቀሬ ነው፡፡ ሀምሳኛው የአፍሪካ ህብረት የምስረታ የወርቅ ኢዮቤልዩ የልደት በአልም የመስራች አባት መሪዎችን የከትናንት በስቲያ የሃምሳ አመት የትዝታ ማህደርን ከፍቶልናል፡፡ ለመሆኑ ከእነዚህ መስራች አባት መሪዎች ውስጥ የእነ ንክሩማህ፣ ሴኩቱሬ፣ ኬንያታ ኔሬሬና ሴንጐር ትዝታ እንዴት ያለ ነው? ግለስብዕናቸው እንዴት ያለ ነበረ? ስለ ግለሰ ስብዕናቸው የሚያወሳው የማህደራቸው የመጀመሪያው ክፍል ከዚህ በታች ያለውን ያስቃኘናል፡፡ የዛሬ ሃምሳ አመት ስለተመሠረተው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የምስረታ ስንክሳሩን የሚመረምር ሰው ለምስረታው ወሳኝ ሚና ከተጫወቱት የአፍሪካ መሪዎች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚያገኘው አዲስ አበባ በሚገኘው የድርጅቱ ዋና ጽሕፈት ቤት ቅጥር ግቢ ውስጥ ሀውልት የቆመለትን የጋናውን የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩማህን ነው፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ክዋሜ ንክሩማህ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት የምስረታ ታሪክ ውስጥ በእርግጥም አንፀባራቂ ኮከብ መሪ ነበሩ፡፡

አባባ ጃንሆይ አንዳች አይነት ሀይለኛ ግርማ ሞገስ ነበራቸው እንደሚባለው ንክሩማህም የቀረቧቸውን ሁሉ እንደማግኔት የሚሰብ ግርማ ሞገስ እንደነበሯቸው በቅርብ የሚያውቋቸው ሁሉ ዛሬም ድረስ ይመሰክሩላቸዋል፡፡ የፕሬዚዳንት ንክሩማህ መላ ህይወት በፖለቲካና በፖለቲካ እንቅስቃሴ የተሞላ ብቻ ሳይሆን ጠቅላላውን የተዋጠ ነበረ፡፡ ለስፖርትና አካላዊ እንቅስቃሴ፣ ለምግብ እንዲሁም ለግላዊ ምቾት ጨርሶ ቁብ አይሰጡም ነበር፡፡ ንክሩማህ በካቶሊክ ሃይማኖት ህግና ስርአት የተጠመቁ ክርስቲያን ሲሆኑ የመጀመሪያ ምኞታቸውም ቄስ መሆን ነበረ፡፡ የቅስና አገልግሎት በውስጡ በያዘው አላማን የማሳካት ግላዊ ተልዕኮ እድሜ ዘመናቸውን ሙሉ በልባቸው እንደተሳቡና እንደተመሰጡ ኖረዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ንክሩማህን ትንባሆ ሲያጤሱና የአልኮል መጠጥ እየጠጡ ሲዝናኑ አይቻቸዋለሁ የሚል ሰው ቢገኝ እርሱ የለየለት ዋሾ ነው፡፡ የንክሩማህ ዋነኛው መዝናኛቸው ስራና ስራ ብቻ ነበረ፡፡ ከዚህ ውጪ የሚያስደስታቸውና በስራ የተወጠረ ስሜትና አካላቸውን ዘና የሚያደርግላቸው ክላሲካል ሙዚቃዎችን ማዳመጥና የባህል ጭፈራዎችን ማየት ነበር፡፡ የሙዚቃን ነገር በተመለከተ ለክላሲካል ሙዚቃዎች ቀልባቸው መሳቡን ያየ አንድ አውሮፓዊ ዲፕሎማት በአንድ ወቅት በአውሮፓ ታዋቂ የሆኑትን የክላሲካል ሙዚቃ አርቲስቶች ስም ዝርዝር ሰጣቸው፡፡

ንክሩማም የደቂቃ ጊዜ እንኳ ሳያጠፉ በእንግሊዛዊቷ ወዳጃቸው ኤሪካ ፓወል አማካኝነት ሁለት መቶ የክላሲካል ሙዚቃ አልበሞች ተገዝተው እንዲመጡላቸው አዘው በሶስት ቀናት ውስጥ ትዕዛዛቸው ተፈጽሞላቸዋል፡፡ ከእነዚህ ሁለት መቶ አልበሞች ውስጥ በጣም የወደዱትና እየደጋገሙ ለሰአታት ያዳምጡት የነበረው ግን The Messiah “Hallelujah chorus” የተባለውን ሙዚቃ ብቻ ነበር፡፡ የፕሬዚዳንት ንክሩማህን አፍዝ አደንግዝ የሆነ ግርማ ሞገሳቸውንና ከሰዎችጋር በቀላሉ የመግባባት አስገራሚ ችሎታቸውን ያየ ብቸኛ ሰው ናቸው ቢባል ለማመን መቸገሩ የማይቀር ነው፡፡ ይሁን እንጂ ሰውየው ከሁሉም ተለይተው ለብቻቸው የቆሙና እጅግ ብቸኛ ሰው ነበሩ፡፡ ንክሩማህ እጅግ ሲበዛ ተጠራጣሪና የቅርብ አጋሮቻቸውንና የትግል ጓዶቻቸውን እንኳ ጨርሰው የማያምኑ ሰው ነበሩ፡፡ ከቅርብ የትግልና የስራ አጋሮቻቸው ውስጥም በስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት የግልም ሆነ የስራ ምስጢራቸውን አካፍለውኝ ያውቃሉ ብሎ የምስክርነት ቃሉን የሚሰጥ ሰው በምድረ ጋሃ ከቶውንም ተፈልጐ አይገኝም፡፡ ፕሬዚዳንት ንክሩማህ በስልጣን ላይ በነበሩበት ወቅት የሚያገኟትን ጥቂት የእረፍት ጊዜ ለማሳለፍ የሚፈልጉት ከትግል ጓዶቻቸው ወይም ከቅርብ የስራ ባልደረቦቻቸው ጋር ሳይሆን ከሴቶች ጋር ብቻ ነበር፡፡ የንክ ሩማህ ልብ ስስ የነበረው በእርግጥም ለሴቶች ብቻ ነበር፡፡ ከሴቶች ጋር መቃበጥ ነፍሳቸው ነበር፡፡

Read 5644 times Last modified on Saturday, 01 June 2013 17:09