Monday, 27 May 2013 15:23

“ኢትዮጵያ ሆኜ መሳል ነው የምመርጠው”

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ሠዓሊ ማህሌት እቁባይ ትባላለች፡፡ ኑሮዋ በሀገረ ኖርዌይ ነው፡፡ እዚያ ለሰባት ዓመታት የሥዕል ሙያን አጥንታ በማስትሬት ዲግሪ ተመርቃለች፡፡ ሥዕል ከማስተማር ይልቅ ፋብሪካ ውስጥ የጉልበት ሥራ ስሰራ ነው ለሥዕል የምነሳሳው የምትለው ሰዓሊዋ፤ ባለፈው ቅዳሜ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ጥበባት ትምህርት ቤት የተለያዩ የኪነጥበብ ውጤቶች የተካተቱበት በለቅሶ ባህል ላይ የተሰናዳ የኢንስታለሽን ሥራ አቅርባለች፡፡ በዚሁ ወቅት ያገኛት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መልካሙ ተክሌ ከሰዓሊዋ ጋር አጭር ቆይታ አድርጓል፡፡

ኖርዌይ ምን እየሰራሽ ነው? ኑሮዬ ኖርዌይ ሀገር ነው፡፡ እዚያ ሰባት ዓመት ሥእል ተምሬአለሁ፡፡ በ1998 ዓ.ም በማስትሬት ዲግሪ በስእል ተመርቄ የተለያዩ ሥራዎች እየሰራሁ ነው፡፡ ከዚያ ሁለት አመት ቀደም ብሎ የሠራሁትን ነው ባለፈው ቅዳሜ ምሽት በአለ የሥነ ጥበብ ትምህርት ቤት ያቀረብኩት፡፡ የድምፅ ጥበብ (Sound art) ነው ለቅሶን አስመልክቶ የሠራሁት፡፡ ለስምንት ዓመት የለፋሽበት ነው ማለት ነው? በአንድ ሰዓት ትዕይንስ ያቀረብሽው? አዎ፡፡ ግን ይህንኑ ዝግጅት ካሁን ቀደም ሁለት ጊዜ አቅርቤዋለሁ፡፡ በኖርዌይና በጎረቤት ሀገር፡፡ መጀመርያ ድምጽ ብቻ ነበር የሰራሁት፡፡ ለለቅሶው የራሴን ድምጽ ነው የቀዳሁት፡፡ ለማስተርስ ዲግሪዬ መመረቂያ ሳቀርበው ተወዳጅነት አገኘና የገንዘብና ቁሳቁስ እገዛ አግኝቼ አዳበርኩት፡፡

ለቅሶ ብቻ ሲሆን ተመልካች አፈንግጦ ነው የሚወጣው፤ ይደነግጣል። ማዳመጥ አይፈለግም፡፡ ተመልካቹን ለመያዝ ለድምፄ ጎጆ ነገር ሠራሁ፡፡ ለሌላው ድምፅ ደግሞ ባለ 5 ሜትር ውሃ የተሞላ እቃ አዘጋጅቼ በጨርቅ የተሰሩ ሕትመቶች አከልኩበት፡፡ ሰው ጨርቁን በውሃ ውስጥ ሲያይ ሳይታወቀው ብዙ ይቆያል፤ ፎቶግራፍ ነው፣ ጨርቅ የማያልቅ ርእሰ ጉዳይ መሆኑን አወቅሁ፡፡ እንዴት ነው ሰዓሊ የሆንሽው? ጣሊያን ትምህርት ቤት ነው የተማርኩት። በስእል፣ በጂኦሜትሪ እና በሂሳብ ጎበዝ ነበርኩ። አስተማሪዬ ለቤተሰብ ስዕል ወይ አርኪቴክቸር ብትማር ብሎ ሃሳብ ሰጠ፡፡ ሁለት መሃንዲስ ወንድሞች ነበሩኝ፡፡ ቤተሰብ አካውንቲንግ አስገባኝ። ትምህርት ቤቱ አካውንቲንግና መሃንዲስ ብቻ ነበር የሚያስተምረው፡፡ አካውንቲንግ መማሩ ግን ፍላጎቴ አልነበረም፡፡ ከዚያ ምግብ ዝግጅት ተማርኩ፡፡ ፍላጎት ስለነበረኝ ግን በትርፍ ሰዓት እዚህ እያለሁ ሰዓሊ አብያለው አሰፋ ውሃ ቀለም ያስተምረኝ ነበር። ኖርዌይ እንደገባሁ አጋጣሚዎች ሲመቻቹልኝ ሥእል ትምህርት ቤት ገባሁ፡፡ ሥዕል ስዬ ዝም ብዬ እወረውረዋለሁ፡፡ ያ ተከማቸ፡፡ ጎረቤቴ የሆነች ፈረንጅ “ለጥበብ ለምን ክብር አትሰጪም” አለችኝና ሰበሰበችው፡፡ ይታይህ የምስለው ለማሳየት ሳይሆን ለስሜቴ ነው፡፡ ታዋቂ ኖርዌያዊ ሠዐሊ ነበር፡፡

እሱ ጋ ወሰደችኝ እዚህ እየመጣሽ ስቱዲዮ ተጠቀሚ አሉኝ - ሠዓሊውና ባለቤቱ፡፡ ሠዓሊ ባለቤቱ ሥራዎችሽን ሰብስቢና አመልክቺ አለችኝ፡፡ ሄጂ በሰባት ወሬ አመለከትኩ፡፡ የሥዕል ትምህርቴን ቀጠልኩ፡፡ በሁለት ዓመት ዲፕሎማ ሁሉን ነገር ተምሬ ወጣሁ፡፡ ቅርፃ ቅርፅ፣ ሥእል፣ ኢንስታሌሽን … ተማርን፡፡ ከዚያ አካዳሚ ተወዳድሬ ገባሁ፡፡ ከ1500 አመልካቾች 15 ብቻ ነው የተቀበሉት፡፡ በሥእል ነው የምትተዳደሪው? አይደለም፡፡ በመጀመርያዎቹ አመታት ሥእል ሰርቼ በመሸጥ እኖር ነበር፡፡ ያንን አልፈለግሁም። የተለያዩ የሥእል ጽንሰ ሀሳቦችን ለማወቅ ጓጓሁ። በተመረቅሁ ጊዜ የሠራኋቸው ሥእሎች በሙሉ ተሸጠዋል፡፡ ግን የበለጠ ማወቅ አለብኝ ብዬ ማስተርስ ቀጠልኩ፡፡ አሁን ግን መሳሉን ትተሽ በተመራማሪነት እየሰራሽ ነው… ኢንስታሌሽን ስትሠራ ለስሜት ነው የምትሠራው፡፡ ገቢ የለውም፡፡ አንድ ሰዓሊ ሥዕል ወይም ቅርፃ ቅርፅ አሊያም ግራፊክስ ሰርቶ ሊሸጥለት ይችላል፡፡ የእኔን የለቅሶ ባህል ላይ የተሠራ ኢንስታሌሽን ግን ማንም አይገዛም፡፡ ከኤግዚቢሽኑ በኋላ ግን ረክቻለሁ፡፡ አንዳንዴ ስፖንሰርም ልታገኝ ትችላለህ፡፡ ከኪስህም አውጥተህ ትሠራለህ ለእርካታ፡፡ ለእርካታ ብቻ እየሰሩ ግን መኖር አይቻልም… ትክክል ነው፡፡ ኖርዌይ አንዳንዴ ፕሮጀክት እሰራለሁ፡፡

አንዳንዴ ደግሞ እንደ አርቲስት ማስተማር ይቻላል፡፡ ኪዩሬተር መሆን ይቻላል። ትክክለኛ የአርት ሥራ ለመሥራት የጉልበት ሥራ ነው የምመርጠው፡፡ የማላስብበትና ብዙ እውቀት የማይጠይቅ ሥራ ላይ ስሆን ጭንቅላቴ ለአርት ይዘጋጃል፡፡ ገንዘብ ሲያስፈልገኝ ፋብሪካ ሄጄ የጉልበት ሥራ እሰራለሁ፡፡ ለምሣሌ አንድ ጊዜ ቺፕስ የሚያመርት ፋብሪካ ውስጥ ሠርቻለሁ፡፡ ብየዳና የመሳሰለውን ነው የምሰራው፡፡ በተደጋጋሚ አንድ ሥራ ሥሠራ ያዝናናኛል፡፡ ሥራውን ስለማመደው ስለ ስዕሌ አስባለሁ፡፡ ሥእል ላስተምር ብል ግን አእምሮዬ ሥራ ስለሚበዛበት ሥእል መሳል አልችልም፡፡ አምኜበት ስለምሰራ በጉልበት ሥራዬ እኮራበታለሁ፡፡ አበሾችም ፈረንጆችም አሉ አብረውኝ የሚሰሩ፡፡ ፈረንጆቹ ከስምንተኛ ክፍል ያላለፉ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ አንዳንዴ ሀበሾቹ ማስተርስ ሆና ከእኛ እኩል ትሠራለች ብለው ይገረማሉ፡፡ በአርቲስትነት ስትሰሪ ትኩረትሽን የሚስቡት ርዕሰ ጉዳዮች ምንድናቸው? በባህል ላይ ያተኮረ ሥራ እሰራለሁ፤ ለምሣሌ የበቀደሙን የለቅሶ ባህል ላይ ያተኮረ የኢንስታሌሽን ሥራ መመልከት ይቻላል፡፡ በእርግጥ ሌሎች አርቲስቶችም በሥራው ተሳትፈዋል። በየቦታው ስሄድ ከቦታው ጋር የተያያዘ ሥራ እሰራለሁ። ሥእል መሳል ከባድ ነው፤ ትልቅ ፈጠራ ይጠይቃል፡፡

አንዳንድ በኮምፒዩተር የታገዘ ስነ ጥበብን የሚቃወሙ ሰዓሊዎች አሉ፡፡ ማህበርም አቋቁመዋል፡፡ እኔ ይኼንን አልደግፍም፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሥራዎቻችን እንዲታወቁ ከፈለግን በኮምፒዩተር መታገዝ አለብን፡፡ ዛሬ እኮ ምዝገባ እንኳን የሚከናወነው በኢሜይል ነው፡፡ ኮምፒዩተር መጠቀም የፈጠራ ችሎታን ያቀጭጫል የሚሉ ሰዓሊዎች እንዳሉ አውቃለሁ? ያንቺ ሃሳብ ምንድነው? ኮምፒዩተር ሥራን በጣም ያግዛል፡፡ የፈጠራ ችሎታን ይቀንሳል ብዬ አላስብም፡፡ ስቱዲዮ ውስጥ ቁጭ ብዬ ብቻ ይህን ዓለም ልከተለው አልችልም፡፡ ከዘመኑ ጋር ካልተራመድክ ተቆራርጠህ ትቀራለህ፡፡ ከኢትዮጵያና ከኖርዌይ ለሰዓሊነት ሙያ የሚመቸው ማነው? በኖርዌይ ስፖንሰርሺፕ በደንብ ታገኛለህ። ኖርዌይ ሆነው ለመሥራት የሚመርጡ ኢትዮጵያውያን ሠዐሊዎች አሉ፡፡ ለኔ ግን ሁኔታዎች ቢሠምሩልኝ ኢትዮጵያ ሆኜ መሣል ነው የምመርጠው፡፡ ኖርዌይ ሀብታሞች ናቸው፡፡ ለአርት ስራ ድጋፍ በመስጠት ያላቸውን አክብሮት ይገልፃሉ፤ ያ ጥሩ ነው፡፡ ጥሩ ፕሮጀክት ካመጣህ ስፖንሰር የማግኘት እድልህ ሰፊ ነው፤ በኖርዌይ። ሀገርህ ሆነህ ስትሥል ግን ዘና ትላለህ፡፡ ጭንቀት የለብህም በጣም ደስ ያለኝ በተለያየ የሥራ አጋጣሚ ከኢትዮጵያ የወጡ አርቲስቶች ኢትዮጵያ ተመልሰው መስራታቸው ነው፡፡

የኖርዌዮች ገብረክርስቶስ ደስታ ወይም አፈወርቅ ተክሌ ማነው? እውቅ ሠዐሊያቸው ጩኸትን አስመልክቶ የሠራው ኤድዋርድ ሞንክ ነው፡፡ አፉን በጣም ከፍቶ ድባቡም ያንን ያጠናከረለት ሥዕል ነው፡፡ ቬጌራን የሚባል ቀራፂም አለ፡፡ በጣም ነው የምወደው፡፡ አንድ ትልቅ ፓርክ ሙሉ ቅርፅ የሳለ ነው፡፡ በጣም አደንቀዋለሁ፡፡ የኖርዌይ የሥእል ታሪክ ግን ከ100 ዓመት የሚበልጥ አይመስለኝም… የሥእል ታሪክ አላቸው፡፡ በዴንማርክና ስዊድን ግዛት ሥር ነበሩ፡፡ ያኔም ግን ሠዐሊዎች ነበሩ፡፡ ልዩነቱ ምንድነው ከዴንማርክና ስዊድን አገዛዝ ነፃ ሲወጡ በራሳቸው ቋንቋ ተጠቅመው ትያትሩንም፣ ሥእሉንም ድርሰቱንም ሌላውንም ማካሄድ መጀመራቸው ነው፡፡ በአገዛዝ ስር የነበሩት አርቲስቶች እኮ እስካሁንም ኖርዌያውያን ናቸው፡፡ ለሕፃናትና ለታዳጊዎች የሚስሉ ሠዐሊዎች ምን ያህል ናቸው? ኢትዮጵያ ውስጥ ምን ያህል ለልጆች የሚስሉ ሠዐሊዎች እንዳሉ አላውቅም፡፡ ግን አሉ፡፡ እንደውም ለሕፃናት መሣል ያዝናናል፡፡ ካርቱን የሚስሉ ጎበዝ ሠዐሊዎች አሉ፡፡ በመፃሕፍት ሥራቸውን ያኖራሉ። ሕፃናት መጻሕፍትንም በሥእል ያሳምራሉ፡፡ ክህሎትና ትዕግስት የሚጠይቀው አኒሜሽንም አለ። አኒሜሽን እና ካርቱን ብዙ ጊዜ ሊፈጅ ይችላል፡፡ ብዙ ገንዘብም ሊያስገኝ ይችላል፡፣

ኖርዌይ ውስጥ የሕይወታት ዘመናቸውን ለሕፃናት የሰጡ ብዙ ሠዓሊያን አሉ፡፡ እስካሁን ከሰራሻቸው የኢንስታሌሽንም ሆነ ሌሎች ሥእሎች ብዙ ገንዘብ አግኝተሽ ታውቂያለሽ? አዎ፡፡ ይህም የሆነው ዲፕሎማዬን ስጨርስ በሠራኋቸው ሥዕሎች ነው፡፡ በአንዴ ነው ስዕሎቹ የተሸዩት፡፡ በኢንስታሌሽንና ሌላ አርት ሥራም ተሳትፌአለሁ፡፡ በተለያዩ ዝግጅቶች ላይ በመስራቴ ትልቅ ሥም ባላቸው ዓለም አቀፍ አውደርእዮች ላይ ተሳትፌአለሁ፡፡ በዚህ ረገድ ሥም አለኝ፤ ምንም ገንዘብ ግን የለኝም፡፡ በሥእል ኤግዚቢሽኑ 34ሺህ የኖርዌይ ኪሮነር አገኘሁ፡፡ እንዲህ ይሸጥልኛል ብዬ ስላላሰብኩ ገንዘቡን በአንዴ ነው ያወደምኩት፡፡ ለቅሶን አስመልክቶ ባለፈው ቅዳሜ በአለ የሥነጥበብ ትምህርት ቤት የኢንስታሌሽንና ሌሎች የኪነጥበባት ስራዎች ተቀላቅለው የቀረቡበት ዝግጅት ከቦታ ጥበት አንፃር ለተመልካች ምቹ አልነበረም … ልክ ነው፡፡ ግን ይኼንኑ ተመልክተን ሥራው ሶስቴ እንዲደገም አድርገናል፡፡ ዝግጅቱ የሥዕል ትምህርት ቤቱና የትያትር ክፍለ ትምህርቶቹ መስተጋብር እንዲኖራቸው ተፈልጎ የተሰራ ነው። ከብሔራዊ ትያትርም ተዋንያን ተሳትፈዋል፡፡ ኬሮግራፈር እና ዳንሰኞችም ነበሩን፡፡ ኤግዚቢሽኑ በጥቅሉ ውጤታማ ሆኗል፡፡

አንድ ወር ተኩል ተዘጋጅታችሁ አንዲት ሰዓት ብቻ ማቅረብ አይደንቅም? እንዴ ከዚያ በላይ ከሆነ እኮ ተመልካቹ ይሰለቻል፡፡ እንዲህ አይነት ሥራ አነስ ብሎ ደረጃውን የጠበቀ ነው መሆን ያለበት፡፡ ቅልብጭ ብሎ ሲቀርብ ተመልካች ካልደገምኩ ይላል፡፡ በዚህ ዝግጅት ሁለቴ ለተመልካች፣ ሦስተኛውን ለተሳታፊዎቹ ፎቶ መነሻ ስንደጋግም ሦስቱንም ጊዜ ያዩ አሉ፡፡ ደጋግሞ ሲያይ ሐሳቡ የበለጠ ግልፅ ይሆንለታል፡፡ በዶክትሬት ዲግሪ ደረጃ ትምህርት ለመቀጠል አስበሻል? አስቤአለሁ፡፡ ለዚሁ የሚያዘጋጁኝን ስድስት መፃሕፍት አምና አንብቤአለሁ፡፡ የኤግዚቢሽን ጥያቄ ሲመጣ አቋረጥኩት፡፡ በአስጎብኚነት ስሰራ ደግሞ ኢትዮጵያን ለማየት ለሚፈልጉ ኖርዌያውያን ለሚጎበኙ ሀገር ጎብኚዎች የጉብኝት ማውጫ በጣሊያንኛና ሌሎች ቋንቋዎች እየሰራሁ አድላለሁ። በዚሁ ጊዜም ሰዎቹን ሊያስለቅሳቸው እንደሚችል እየጠየቅሁ ጥናቴን ቀጥያለሁ፡፡ የቀረ ነገር ካለ? በጣም ብዙ ተዳግሮት አለው ሥራው፡፡ ለሙያው ክብር ኖሯቸው ጊዜአቸውን መስዋእት አድርገው የለቅሶ ሥርአቱን ለማሳየት አብረውኝ የሰሩትን በጣም ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡

Read 3578 times