Saturday, 06 July 2013 11:20

ቤተ-እስራኤላዊቷ ድምፃዊት በእስራኤል ደምቃለች

Written by 
Rate this item
(2 votes)

በቅርቡ “ላይፍ ሃፕንስ” የተባለ አዲስ አልበም በእስራኤል ለገበያ ያበቃችው ቤተእስራኤላዊቷ ድምፃዊት ኤስተር ራዳ፤ በእስራኤል የሙዚቃ ኢንዱስትሪ መድመቅ ጀምራለች ተባለ፡፡ የኤስተር ራዳ አዲስ አልበም አርቲስቷ ኢትዮጵያዊ የዘር ግንዷን ሙሉ ለሙሉ የገለፀችበት ነው ያለው “ኒውስፖይንት አፍሪካ” ፤ “ላይፍ ሃፕንስ” በተባለው ዘፈኗ ዋሽንትና ማሲንቆን እንደተጠቀመች ጠቅሷል፡፡ የ28 አመቷ ድምፃዊት፤ የዘፈን ግጥም ደራሲ እና ተዋናይቷ በአዲሱ አልበሟ ውስጥ “ላይፍ ሃፕንስ” የተሰኘውን የአልበሙን መጠርያ ጨምሮ “ሞንስተርስ”፤ “ኤኒቲንግ ፎር ዩ” እና “ኩድ ኢትቢ” የተባሉ ዘፈኖችን አካትታለች፡፡ በኢትዮ ጃዝ እና በሶል የሙዚቃ ስልቶች የተሰሩት የድምፃዊቷ ዘፈኖች በእስራኤላውያኖቹ እውቅ የሙዚቃ ባለሙያዎች ኩቲ እና ሳቦ የተቀናበሩ እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኤስተር ቤተሰቦች እ.ኤ.አ በ1983 ዓ.ም በተከሰተው ረሃብ ሳቢያ ኢትዮጵያን ለቅቀው ወደ እስራኤል የተሰደዱ ሲሆኑ ኤስተር የተወለደችው ቤተሰቦቿ እስራኤል ገብተው ኪራያት ኡባ በተባለ ስፍራ መኖር ከጀመሩ ከአንድ አመት በኋላ ነው፡፡ ኤስተር እና ቤተሰቧ 10ኛ ዓመቷን እስክትይዝ ድረስ በሄብሮን ዳርቻ የኖሩ ሲሆን እድሜዋ ለእስራኤል የውትድርና አገልግሎት ሲደርስ ወደ ውትድርናው ገብታ እግረመንገዷን እዚያው በነበረ የሚሊታሪ ባንድ ድምፃዊ በመሆን ሰርታለች፡፡

ቤተእስራዔላዊ ብትሆንም በፀጉረ-ልውጥነቷ ብዙ አሳዛኝ ገጠመኞችን በወጣትነቷ ያሳለፈችው ኤስተር፤የሚሰማትን የመገለል ስሜት በሙዚቃዋ ስትከላከልና ስትዋጋ እንደኖረች አልደበቀችም፡፡ የውትድርና አገልግሎቷን ከጨረሰች በኋላ ኑሯዋን በቴል አቪቭ በማድረግም ወደ ትወና ሙያ እንደገባች ትናገራለች፡፡ በተዋናይነቷ የቴሌቭዥን ፊልሞች የሰራችው ኤስተር፤ ከአራት በላይ የሙሉ ጊዜ ፊልሞች ላይ መተወኗንና “ስቲል ዎኪንግ” እና “ዘ ሩቫቤል” የተባሉት ሁለት ፊልሞች በእስራኤል ፊልም አፍቃሪያን ዘንድ ተወዳጅነት ያተረፉ መሆናቸውን ገልፃለች፡፡

Read 2497 times