Saturday, 20 July 2013 10:04

የፊልም አዘጋጇ ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ ክስ ቀረበባት

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(13 votes)

ደራሲዋና አከፋፋዩ ለፖሊስ ቃላቸውን ሰጥተዋል

“ፔላማ” የተሰኘው ፊልም በጥንቆላና በመፍትሄው ዙሪያ የሚያጠነጥን እንደሆነ የፊልሙ ደራሲና አዘጋጅ ሜሊ ተስፋዬ የገለፀች ሲሆን፣ ፊልሙ እምነታችንን የሚካ ነው በሚል ቅሬታ አንድ የእምነት ተቋም ለፖሊስ አቤቱታ አቀረበ፡፡ ሜሊ ተስፋዬና የፊልሙ አከፋፋይ ወደ ማዕከላዊ ምርመራ ተጠርተው ለፖሊስ ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ የፊልሙ በርካታ ተዋናዮችም ቃላቸውን ይሰጣሉ ተብሏል፡፡ ፊልሙ ሃይማኖተን ይነካል የሚል ክስ ያቀረበው “ባፋ አባዩ ገዳ አንድነት የእምነት ተከታዮች ተቋም” መንፈሶቻችን ተነክተዋል፣ የሃይማኖት ተከታዮቻችን ተሰድበዋል ሲል ለፖሊስ አመልክቷል፡፡ ለእምነት የምንገለገልባቸውን ቁሳቁሶች ባካተተው ፊልም፤ ስማችን ጠፍቷል የሚለው ይሄው ተቋም፣ የእምነቱን ተከታዮች የሚያስጨንቅና የሚያሳቅቅ የድፍረት ስራ ተሰርቷል የሚል ክስ እንደቀረበባት ሜሊ ተስፋዬ ተናግራለች፡፡

“እኛ በፊልሙ ላይ የተጠቀሱትን መናፍስት የሚጠቀም የሃይማኖት ተቋም መኖሩን አናውቅም ነበር” የምትለው ሜሊ፤ ፊልሙ ከሁለት አመት በፊት በብሔራዊ ቲያትር ከተመረቀ በኋላ በተለያዩ የአገራችን ሲኒማ ቤቶች ከአገር ውጭም በዱባይ፣ በአቡዳቢ እና በሌሎች የአረብ ሀገራት እንዲሁም በጀርመን፣ በሆላንድ፣ በቤልጅየም፣ በፈረንሳይና በጣሊያን ከተሞች ፊልሙ ለእይታ መቅረቡንም ተናግራለች፡፡

በፖሊስ ፕሮግራም የተላለፉ የታምራት ገለታ ታሪኮች እንዲሁም “የአዳል ሞቴ” መንፈስ አለብኝ እያለ ብዙዎችን ያስጨነቀ የአንድ ጠንቋይ ታሪክ ለፊልሙ መነሻ እንደሆኑላት ትገልፃለች - ደራሲዋ፡፡ በዚህ መነሻ ጥናት አካሂዳ ፊልሙ እንደተሰራ ያወሳችው ሜሊ፤ ዋናው ገፀ ባህሪ በሀገራችን የሚታወቁትና አዳልሞቴ፣ ጠቋር፣ ወሰንጋላ የሚባሉ መናፍስትን እየጠራ ሰዎችን ሲያታልል፣ ገንዘባቸውን ሲበዘብዝና ለሞት ሲያበቃቸው ይታያል ብላለች፡፡ የፊልም ሙያዬን በመጠቀም ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ስራ ለማቅረብ እንጂ የማንንም መብት ለመንካት አስቤ አልሰራሁም የምትለው ሜሊ፤ ለፖሊስ ቃሏን ከሰጠች በኋላ በዋስ እንደተለቀቀች ተናግራለች፡፡

Read 27195 times