Saturday, 27 July 2013 13:44

የአገሪቱ ሦስተኛ ፕሬዝዳንት ማን ይሁን?

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ፕሬዝዳንት የሚሆነው ግለሰብ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል ብቻ ስለመሆኑ ወይም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዕጩ ሆኖ መቅረብ የሚችል ስለመሆኑ ግልጽ ባለ ሁኔታ የተደነገገ አንቀጽ በሕገ መንግስቱ ውስጥ አይገኝም፡፡ ይሁን እንጂ፣ አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 3 እንዲህ ይላል “የምክር ቤት አባል ፕሬዝዳንት ሆኖ ከተመረጠ የተወከለበትን ምክር ቤት ወንበር ይለቃል” ይላል፡፡ ይህ ጥቅል አገላለጽ በውስጡ በርካታ ጉዳዮችን የያዘ ይመስለኛል፡፡

 ሰሞኑን በመዲናችን እየተናፈሱ ካሉት የወሬ ቱማታዎች አንዱ፣ በመጪው መስከረም ወር 2006 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ሆኖ የሚመረጠው ሰው ማን እንደሆነ የመተንበይ ጉዳይ ነበር፡፡ በወሬው ሂደት በፕሬዝዳንትነት ዕጩ ሆነው ይቀርባሉ ከተባሉት ግለሰቦች አንዱ እውቁ አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ እንደሆነም ተደጋግሞ ሲጠቀስ ሰምተናል፡፡ 

ታዋቂው አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴም ይህንኑ ጉዳይ አስመልክቶ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ የሐምሌ 13 ቀን 2005 ዓ.ም እትም ላይ ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡ አትሌት ኃይሌ “በመጪው ምርጫ ፓርላማ እገባለሁ፤ ግን ወዲያው ፕሬዝዳንት አልሆንም” በሚል የሰጠውን ቃለ ምልልስ ካነበብኩ በኋላ እነሆ ይህቺን ጽሁፍ ለማዘጋጀት ተነሳሁ፡፡
በዚህ መጣጥፍ በሦስት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ማድረግን መረጥኩ፡፡ አንደኛ፤ ከሀገሪቱ ሕገ-መንግስት እና ከሁለቱ ምክር ቤቶች (ከሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት እና ከፌዴሬሽን ም/ቤት) የጋራ ስብሰባ መተዳደሪያ ደንብ አኳያ የፕሬዝዳንት አመራረጥን በተመለከተ የፈጻጸም ሂደቱን መቃኘት፣ ሁለተኛ፤ አትሌት ኃይሌ በቃለ ምልልሱ ባነሳቸው አንዳንድ ሃሳቦች ዙሪያ አስተያየት መስጠት እና ሦስተኛ፤ የሀገሪቱ 3ኛ ፕሬዝዳንት ማን ቢሆኑ ይሻላል? በሚለው ላይ የግል እይታዬን ማቅረብ ይሆናል፡፡
የፕሬዝዳንት አመራረጥ፣
ብዙ ሰዎች የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት የሚሆነው ሰው በግሉ ተወዳድሮ በማሸነፍ የፓርላማ አባል የሆነ ግለሰብ ብቻ እንደሆነ ሲናገሩ ይደመጣል፡፡ በዚህ ረገድ ያለውን ብዥታ ለማጥራትና ትክክለኛውን ግንዛቤ ለመያዝ የህገ መንግስቱን ድንጋጌ መመልከቱ ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 1 መሰረት ፕሬዝዳንት የሚሆንን ሰው ዕጩ አድርጎ የማቅረብ ስልጣን የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው፡፡ ይሁን እንጂ፣ ይህ ዕጩ ፕሬዝዳንት የሚሾመው በሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት እና በፌዴሬሽን ም/ቤት የጋራ ስብሰባ በተገኙ አባላት በሁለት ሦስተኛ (2/3ኛ) ድምፅ ድጋፍ ያገኘ እንደሆነም፣ በአንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 2 ላይ ተደንግጓል፡፡ ፕሬዝዳንት የሚሆነው ግለሰብ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል ብቻ ስለመሆኑ ወይም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዕጩ ሆኖ መቅረብ የሚችል ስለመሆኑ ግልጽ ባለ ሁኔታ የተደነገገ አንቀጽ በሕገ መንግስቱ ውስጥ አይገኝም፡፡ ይሁን እንጂ፣ አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 3 እንዲህ ይላል “የምክር ቤት አባል ፕሬዝዳንት ሆኖ ከተመረጠ የተወከለበትን ምክር ቤት ወንበር ይለቃል” ይላል፡፡ ይህ ጥቅል አገላለጽ በውስጡ በርካታ ጉዳዮችን የያዘ ይመስለኛል። እኔ እንደገባኝ ከሆነ፣ የዚህ አንቀጽ መንፈስ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ለፕሬዝዳንትነት እጩ ሆኖ መቅረብ የሚችል መሆኑን፤ ይሁን እንጂ እጩው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባል ከሆነ (የምክር ቤት አባልም ፕሬዝዳንትም መሆን ስለማይኖርበት) መቀመጫውን እንደሚለቅ ያስገነዝባል፡፡
የዚህን አንቀጽ ትርጉም ሰፋ አድርገው የሚያዩ አንዳንድ ሰዎች “የተወከለበትን ምክር ቤት ወንበር ይለቃል” ማለት የፓርቲ አባል ከሆነ ‘የፓርቲ መታወቂያውን ይመልሳል’ ማለት እንደሆነ አድርገው ሲናገሩም የሰማሁበት አጋጣሚ አለ፡፡ በኔ እምነት ይህ አተረጓጎም ግን ትክክል አይመስለኝም፡፡ ያ ቢሆን ኖሮ የመጀመሪያው የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት የነበሩት ዶ/ር ነጋሦ ጊዳዳ፤ እስከ ስልጣን ዘመናቸው ማብቂያ ድረስ የኦህዴድ አባል ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ አመራርም ሆነው አይዘልቁም ነበር የሚል መከራከሪያ ማቅረብ የሚቻል መስለኛል፡፡ ከላይ የጠቀስኩት የሕገ መንግስቱ ድጋጌ እንተጠበቀ ሆኖ፤ በሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት እና በፌዴሬሽን ም/ቤት የጋራ የአሰራርና የስብሰባ ሥነ-ስርዓት ደንብ ቁጥር 1/2000 ላይ፤ ስለ እጩ ፕሬዝዳንት አቀራረብ፣ አንድ እጩ ፕሬዝዳንት ማሟላት ስለሚገባው መስፈርት፣ ስለ ሌሎችም ጉዳዮችና ዝርዝር የአፈጻጸም ሂደቶች የተብራራበት ሁኔታ አለ፡፡በዚሁ ደንብ አንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 3 መሰረት፤በዕጩ ፕሬዝዳንትነት የሚቀርብ ሰው አራት መስፈርቶችን ማሟላት እንዳለበት ተደንግጓል። ይኸውም፤ (1) ለሕገ መንግስቱ ታማኝ የሆነ፣ (2) ሀገሪቱን በርዕሰ ብሔርነት ለመምራት የሚያስችል ብቃትና ሥነ-ምግባር ያለው፣ (3) ዕድሜው 21 ዓመት እና ከዚያ በላይ የሆነ እና (4) ኢትዮጵያዊ ዜጋ የሆነ፣ የሚሉ ናቸው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ “ለፕሬዝዳንትነት እጩ ሆኖ የሚቀርብ ማንኛውም ሰው ከማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ወገንተኛነት ነፃ ሆኖ ለማገልገል ፈቃደኛ መሆን አለበት” የሚል ድንጋጌ በዚሁ ደንብ በአንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 4 ላይ ተደንግጓል፡፡
አንድ ሰው ለሁለቱ ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ እጩ ፕሬዝዳንት ሆኖ ለመቅረብ ደግሞ በቅድሚያ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ስብሰባ በአብላጫ ድምፅ እጩነቱ ተቀባይነት ማግኘትና መጽደቅ እንደሚኖርበትና የዚህ አፈጻጸም ሂደትም በጋራ ደንቡ በአንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2 ላይ በዝርዝር ተብራርቷል፡፡
የአትሌት ኃይሌ ቃለ ምልልስ፣
አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ ከላይ በዝርዝር የጠቀስኳቸውን የሕገ መንግስት እና የሁለቱ ም/ቤቶች የጋራ ስብሰባ መተዳደሪያ ደንብ የፕሬዝዳንት አመራረጥ ድንጋጌዎች ይወቃቸውም አይወቃቸው በመጪው ሀገራዊ ምርጫ ተወዳድሮ በማሸነፍ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ለመሆን እና ከዚያም የሀገሪቱ ርዕሰ ብሔር ለመሆን መነሳቱ መልካም ነገር ይመስለኛል፡፡ ባደጉትና በሰለጠኑት ሀገሮች የጎላ የፖለቲካ ተሳትፎ የሚያደርጉት ምሁራንና ባለሀብቶች እንደሆኑ ይነገራል፡፡ የሀገራችን ምሁራን፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ባለሀብቶች በስልጣን ላይ ያለውን ገዢ ፓርቲ ፖሊሲዎችና አፈጻጸም በሩቁ ሆነው ከመተቸትና ከማማረር አልፈው ወደ ፖለቲካው መድረክ ብቅ ሲሉ ብዙም አይታይም፡፡ እናም በዚህ ረገድ አትሌት ኃይሌ ያሳየው ተነሳሽነት የሚያስመሰግነው እንደሆነ እገነዘባለሁ፡፡
ይሁን እንጂ፣ አትሌት ኃይሌ ወደ ፖለቲካው መድረክ “ዘው” ብሎ ከመግባቱ በፊት በጥልቀት ሊያያቸውና ሊመረምራቸው የሚገቡ ጉዳዮች ያሉ መሆኑን በዚህ ጽሁፍ መግቢያ ላይ በጠቀስኩት አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ከሰጠው ቃለ ምልልስ ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡ ለምሣሌ፤ “ፕሬዝዳንት ብትሆን ምን ምን ሥራዎችን እንደምታከናውን ግለጽልኝ” ተብሎ ለቀረበለት ጥያቄ “በስራ አጥነት፣ በመልካም አስተዳደር፣ በኤክስፖርት ላይ ብዙ መስራት ይቻላል…” የሚል መልስ ሰጥቷል፡፡
ይህንን የኃይሌን መልስ ሳነብ፣ አትሌት ኃይሌ ከተራ ሀገር ወዳድነት እና ከሥራ ተነሳሽነት ውጪ “ፖለቲከኛ” የሚያደርገው አቅም የገነባ አለመሆኑን ነው የተረዳሁት፡፡ የፕሬዝዳንቱ የስራ ድርሻ ምን ምን እንደሆነ እንኳ ሕገ መንግስቱን አንብቦ በቅጡ የተገነዘበ አልመሰለኝም፡፡ እንኳን የጠለቀ ግንዛቤ ሳይዙ የመጠቀ ግንዛቤ ተይዞም የኢትዮጵያ ፖለቲካ ዳር ላይ ሆነው እንደሚያዩት ቀላል አደለም፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው በእኛ ሀገር የፕሬዝዳንቱ ስልጣን ውሱን (በእንግሊዝኛው አገላለጽ Ceremonial) ነው፡፡ በሕገ መንግስቱ በተደነገገው መሰረት የፕሬዝዳንቱ የስራ ድርሻ በአጭሩ “በየዓመቱ የሁለቱን ም/ቤቶች የጋራ ስብሰባ በንግግር መክፈት፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲያቀርቡ አምባሳደሮችን መሾም፣ ፓርላማ ያጸደቃቸውን ሕጎች መፈረምና በነጋሪት ጋዜጣ ማወጅ፣ ኒሻንና ሽልማት መስጠት፣ ይቅርታ ማድረግ፣…ወዘተ.” የሚሉ ናቸው፡፡ በሕገ መንግስቱ ከተሰጠው ስልጣን ውጪ መስራት እንደማይቻልም ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ፣ አትሌት ኃይሌ ይህንን ባለመገንዘብ ይመስለኛል “ሥራ አጥነትን፣ መልካም አስተዳደርን፣ ጠቃሚ ያልሆኑ ባህሎችን፣ ሰርግን፣… ወዘተ.” የመሳሰሉትን በተመለከተ እሰራለሁ የሚል መልስ በቃለ ምልልሱ ያነሳው፡፡ ልክ በአትሌቲክሱ በማራቶን ለመወዳደር የተመዘገበ፣ በመቶ ሜትር ርቀት መወዳደር እንደማይችለው ሁሉ፣ፕሬዝዳንቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩን የሥራ ድርሻ ሊሰራ እንደማይችል ወንድሜ ኃይሌ ልብ አላለውም፡፡
እዚህ ላይ አንድ ነገር ለማለት ወደድሁ፡፡ አትሌት ኃይሌ፣ በአትሌቲክሱ መስክ የተዋጣለት ሥራ በመስራት ስኬታማ ሊሆን የቻለው በመስኩ የጠለቀ እውቀትና ግንዛቤ ያለው አሰልጣኝና ማናጀር በሚሰጠው ምክርና አቅጣጫ በመጓዙ ይመስለኛል። ስለሆነም፤ በፖለቲካውም መስክ የተሳካ ውጤት ላይ ለመድረስ በቂ ግንዛቤና ልምድ ያለው አማካሪ ቢኖረው መልካም ነው፡፡ በዚህ ረገድ እኔን ጨምሮ የቀድሞ የተቃዋሚ ወይም የኢህአዴግ አባል የነበርን “የፖለቲካ ጡረተኞች” ስላለን የአማካሪ ችግር የሚኖር አይመስለኝም፡፡ ባይሆን ከእጅህ ፈታ ማለት ነው - ወዳጄ ኃይሌ! (አጋጣሚውን በመጠቀም አዲስ አድማስ ያላወቀው ማስታወቂያ መስራቴ ነው)
ማን ፕሬዝዳንት ይሁን?
ባለፉት አስራ ስምንት ዓመታት ሁለት ፕሬዝዳንቶች በርዕሰ ብሔርነት ተሹመዋል። አሁን በስራ ላይ ያሉት ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የስልጣን ዘመን በመጪው መስከረም ወር 2006 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅና አዲስ ፕሬዝዳንት እንደሚመረጥ ይጠበቃል፡፡ እጩ ፕሬዝዳንቱን መርጦ በማቅረብ ረገድ ደግሞ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አብላጫ መቀመጫ ያለው መሪው ፓርቲ ኢህአዴግ ትልቁን ሚና እንደሚጫወትም ይታመናል፡፡ በመስፈርቱ መሰረት ኢህአዴግ ይህንን “እድል” ለማን እንደሚሰጥ ምንም ዓይነት ፍንጭ አልሰማሁም፡፡ ግን ለማን ቢሰጥ ይሻላል? ከፆታ አኳያ ለወንዶች ወይስ ለሴቶች? ከዕድሜ አኳያ ለወጣት፣ ለጎልማሳ ወይስ ለአረጋዊ? ከሃይማኖት አኳያ ለኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ፣ ለሙስሊም፣ ለካቶሊክ፣ ለፕሮቴስታንት ወይስ ለሌላ? ከብሔር ብሔረሰቦች አኳያ ለሶማሌ፣ ለአፋር፣ ለመዠንገር፣ ለሀዲያ፣ ለከንባታ፣ ለኩናማ፣ ለኤሮጵ፣ ለኛጋቶም፣ ለሙርሲ፣ ለሐመር፣…ወይስ? ኢህአዴግ ካለፉት ሁለት የእጩ ፕሬዝዳንት አቀራረቦች ሂደት የተገኙ ተሞክሮዎችን በማየትና ከላይ የጠቃቀስኳቸውን የፆታ፣ የዕድሜ፣ የሃይማኖትና የብሔር ብሔረሰቦች ስብጥር ከግንዘቤ በማስገባት፣ በአንፃራዊነት የኢትዮጵያን ሕዝቦች ሊወክል የሚችል እጩ ቢያቀርብ የተሻለ እንደሚሆን አስባለሁ፡፡ በተለይ ደግሞ ከሀገሪቱ ዜጎች ከግማሽ በላይ ለሚሆኑት ለሴቶች እድሉ ቢሰጥ የተሻለና አስፈላጊም ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዚህ ረገድ ይህንን ኃላፊነት ሊሸከሙ የሚችሉ እውቀትም፣ ልምድም ሆነ ችሎታ ያላቸው በርካታ ሴቶች እንዳሉ ቅንጣት ታህል ጥርጣሬ የለኝም፡፡ ከታሪክም አኳያ እንኳን አሁንና በጥንታዊት ኢትዮጵያ እነ ንግስት ሳባ፣ ንግስት እሌኒ፣ ንግስት ሀዲያ፣ ዮዲት ጉዲት (ባኑኤል ሃይሙያ?)፣ ዘውዲቱ እና ጣይቱ የነበራቸውን ሚና ማስታወስ መልካም ነው፡፡

Read 3145 times