Saturday, 27 July 2013 14:36

አንጀሊና ጆሊ በአርአያነቷ ተደነቀች

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ከሁለት ወር በፊት ራሷን ከጡት ካንሰር ለመታደግ ሁለት ጡቶቿን በቀዶ ጥገና ያስወገደችው አንጀሊና ጆሊ፤ለመላው ዓለም ስለ ጡት ካንሰር አስከፊነት ባስጨበጠችው ግንዛቤ ከፍተኛ አድናቆትን እንዳተረፈች ተገለፀ፡፡ ዝነኛዋ የሆሊውድ አርቲስት ህክምናውን ለማግኘት የወሰደችው ፈጣን እርምጃና ለመላው ዓለም ግልፅ መረጃ በማቀበል ባሳየችው ድፍረት የተመላበት ተግባር በህክምና ባለሙያዎች ዘንድ ተወድሶላታል። “ተግባሯ በሙያችን መነቃቃትና ግንዛቤ እንዲፈጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል” ብለዋል - ባለሙያዎቹ፡፡ የስድስት ልጆች እናት የሆነችው የ37 ዓመቷ አንጀሊና ጆሊ፤ሁለት ጡቶቿን የሚያስወግድ ቀዶ ህክምና ባታደርግ ኖሮ 87 በመቶ ለጡት ካንሰር፣ 50 በመቶ ለማህፀን ካንሰር ትጋለጥ እንደነበር ታውቋል፡፡ አንጀሊና በኒውዮርክ ታይምስ ላይ ባሰፈረችው ፅሁፍ፤ ህክምናውን ለመውሰድ የወሰደችው እናቷ በ56 ዓመታቸው በተመሳሳይ ችግር ለሞት በመዳረጋቸው እንደሆነ ገልፃለች። በመላው ዓለም በየዓመቱ ከ45ሺ በላይ ሴቶች በጡት ካንሰር እንደሚሞቱ መረጃዎች ያመለክታሉ።

Read 2699 times