Saturday, 03 August 2013 10:13

ባለ 4 ኮከቡ የቀነኒሳ ሆቴል ነገ ሥራ ይጀምራል

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(5 votes)

200ሚ. ብር የወጣበት ሆቴል በአዲስ አመት ይመረቃል

የዓለምና የኦሎምፒክ የ5 እና የ10ሺ ሜትር ሩጫ ሪከርድ ባለቤት ቀነኒሳ በቀለ፤ በ200 ሚሊዮን ብር ያስገነባው ባለ 4 ኮከብ ዘመናዊ ሆቴል ነገ አገልግሎት ይጀምራል፡፡ 
ከቦሌ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ፊት ለፊት የተሰራውና በጀግናው አትሌት ስም የተሰየመው ቀነኒሳ ሆቴል፤ ባለ 7 ፎቅ ሲሆን 51 የመኝታ ክፍሎች እንዳሉት ታውቋል፡፡
ሆቴሉ፣ ሱዊት፣ ጥንድ፣ ሲንግል፣ የቤተሰብና ለአካል ጉዳተኞች ታስቦ የተሰሩ ክፍሎች ሲኖሩት፣ ሱት የሚባሉትን 10 ክፍሎች ጨምሮ 22 ክፍሎች ጃኩዚ እንዳላቸው የሆቴሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ ወ/ሪት ሮማን ታፈሰወርቅ ገልፀዋል፡፡
ሥራ አስኪያጇ አክለውም፣ ሆቴሉ በአሁኑ ወቅት ለመቶ ሠራተኞች የሥራ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ጠቅሰው ሠራተኞቹ ቀደም ሲልም በሆቴል ሙያ እውቀትና ልምድ ቢኖራቸውም የአንድ ወር ሥልጠና እንደተሰጣቸውና ሥልጠናው ወደፊትም እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
በቂ የመኪና ማቆሚያ ስፍራ መኖሩ ልዩ ያደርገናል ያሉት ወ/ት ሮማን፤ የደንበኞቻቸውን ምቾት ለመጠበቅ፣ ለክፍሎቹ ብቻ ሳይሆን ለሆቴሉ በአጠቃላይ የአየር ሙቀትና ቅዝቃዜ መቆጣጠሪያ መሳሪያ (ኤሲ) መገጠሙን ገልፀዋል፡፡ ከሁሉም በላይ የእንግዶቻቸውን ደህንነት ማረጋገጥ አስፈላጊ በመሆኑ፣ ሁሉም ክፍሎች ጭስ ጠቋሚ (አነፍናፊ) መሳሪያ፣ የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከያ ሲስተም (ማምለጫ ደረጃዎች)፣ በየቦታው የውሃ መርጫና ጠቋሚ ካሜራዎች መገጠማቸውን አስረድተዋል፡፡
የድምፅ ብክለትን ለመከላከል በሮቹና መስኮቶቹ ድምፅ የማያስተላልፉ (ሳውንድ ፕሩፍ) መሆናቸውንና ዕቃዎቹ በሙሉ የባለ 5 ኮከብ ሆቴል መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡
ሰፊና ዘመናዊ ሎቢ ባር፣ ካፊቴሪያ፣ የባህላዊና ዘመናዊ ምግቦች ሬስቶራንት፣ ቪአይፒ ላውንጅ፣ እንግዳው በንፁህ አየር እየተዝናና ፒዛ መብላት፣ ቢራና ድራፍት መጠጣት እፈልጋለሁ ቢል ምቹ (ኦፕን አየር) ስፍራ ተዘጋጅቷል፡፡
ሆቴሉ፣ ሁለት የእንግዶችና አንድ የሠራተኞች መጠቀሚያ አሳንሰር (ሊፍት) ሲኖረው፣ ፈጣን ብሮድ ባንድ ኢንተርኔትና ሽቦ አልባ (ዋየርለስ)፣ ሳውና ባዝ፣ ስቲም ባዝ፣ ጃኩዚ፣ ሁለገብ ጂምናዚየም፣ ኤሌክትሮኒክስ ገንዘብ መቀበያ ካርድና የተለያዩ የንግድ ማዕከላት ሲኖሩ 24 ሰዓት አገልግሎት እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡ ወ/ሪት ሮማን ታፈሰወርቅ፤ ከሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በሆቴል ማኔጅመንት የመጀመርያ ዲግሪ ሲኖራቸው፣ ለሁለተኛ (ማስተርስ) ዲግሪያቸው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማርኬቲንግ ማኔጅመንት እየተማሩ ናቸው፡፡

Read 29233 times