Saturday, 10 August 2013 10:28

“የፀረ ሽብር አዋጁ ካልተቀየረ ማንንም አይምርም”

Written by 
Rate this item
(10 votes)

የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዲኤታው ፍ/ቤት ይቆሙ ነበር - ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ናፍቆት ዮሴፍ “ሰማያዊ ፓርቲ፣ ግንቦት ሰባት እና አክራሪዎች ጋብቻ ፈጽመዋል” በሚል የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ መናገራቸውን የተቃወሙት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት፤ “የፀረ ሽብር አዋጁ ካልተቀየረ ማንም አይምርም፣ የመንግስት ስልጣን ገደብ ቢኖረው ኖሮ ሚኒስትር ዴኤታው ፍ/ቤት መቆም ነበረባቸው” በማለት ምላሽ ሰጡ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በህዝብ ስም የተቋቋመ ስለሆነ የመንግስት ድክመቶችንና ክፍተቶችን እንዲያስተካክል መታገል ስራው ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ መንግስት የህዝብን ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ መፈረጅ ይቀናዋል፤ ይህ ግን ከትግላችን አያግደንም” ብለዋል፡፡

“ከሁለት ወር በፊት የህዝብ ችግሮችና ጥያቄዎች ናቸው ብለን በሰላማዊ ሰልፍ ያሰማናቸው ጥያቄዎች አልተመለሱም” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ነሐሴ 26 ቀን 2005 ዓ.ም ሁለተኛውን ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ “ኢትዮጵያ ከአገዛዝ ወደ ዴሞክራሲ ገና አልገባችም፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ገና የስልጣን ባለቤት አልሆነም” ያሉት ኢንጂነሩ፤ እነዚህ ነገሮች እውን እንዲሆኑ በምርጫ ቦርድ ህጋዊ እውቅና አግኝቶ በሰላማዊ መንገድ የሚታገልን ፓርቲ ከአሸባሪዎች ጋር ጋብቻ ፈጽሟል በማለት መወንጀል የአገዛዝ ባህሪ ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡ አሸባሪ የሚለው ቃል ትርጉሙን ስቷል የሚሉት ኢ/ር ዘለቀ፤ የፀረ ሽብር አዋጁ እስካልተቀየረ ድረስም ማንንም ከመፈረጅ የሚያግድ ነገር የለውም ብለዋል።

Read 22203 times