Saturday, 24 August 2013 10:29

በሎቲ ያጌጠው ‹‹ጆሮ›› አገሩ የት ነው?

Written by  ገዛኸኝ ፀጋው (ፀ.)
Rate this item
(0 votes)

ጆሯችንን መርገምት ደፍኖት፣
መርገምቱን ጥይት አቡኖት፣
ጥይቱን አንጠረኛ አድኖት፣
አንጠረኛውን ሙያው ሲያስንቀዉ፣
አእምሮዉን ክፋት ሲያደቀዉ፣
የቦዘኔዎች ምላስ ሲያደርቀዉ፣
አሜሪካዊ ጥቁር ወንድሙም፣ የማንነት
ቀውስ ሲደፍቀው!
አፍሪካዊነት ሲበለጨለጭ፣ ሕሊናችንን
ንዋይ ሲያቅፈው፣
ደናቁርት መሪዎች ታበዩ፤ መደማመጥን
በሀይል ቀፍፈው!
መንግስታት ቡድን አደራጅተው
ፖለቲካቸውንም አስደግፈው፣
ሰውን በሰው ሲያጠፋፉ፣ ከቶ ማን
ይሆን የሚተርፈው!?
የባሩድ ፍንዳታ ያደነቆረው፣
ድንቁርናውን በሌላ ጥይት ፣ እየበሳሳ
የወቀረው...
ወይ እንደ ምንጅላቱ የጠቆረ፣ ወይ
በባንዳነቱ የቀላ፣
የራሱን ጆሮ በሎቲ አስጊጦ፣ የወንድሙን
ግን ያተላ!
ሰዋዊነትም እንስሳነትም፣ እኩል አድኖ
የሚቋደስ፣
የጀግንነት እውቀት ሲያጥረው፣ ግዳይ
ጥሎ የሚፈወስ፣
ለዚህ ሳይሆን አይቀርም፣ አስተሳሰቡ
የደፈረሰው፣
ጀግንነትን እስከ መለኪያው፣ በድንቁርናው
የደቆሰው!
ባሩድ የሚጋት ልሙጥ ጆሮ፣ ሎቲ አንጠልጥሎ
ያየ ሰው፣
‹‹ይኼ ጆሮ አገሩ የት ይሆን?›› ብሎ
ሳይጠይቅ ያድሰው!
ምንም በቀይ ጭንቅላት ጎን፣ በደም
ጨቅይቶ ቢጣበቅም፣
ይኼ ጆሮ እንደሁ አፍሪካዊ ነው፤ ‹የት ነው?›
ተብሎ አይጠየቅም፡፡
የሚንጣጣ ምላሱ እንጂ፣ ግብሩ ማንነቱን
አይደብቅም፡፡
እርግጥ ነው አይደበቅም...!
እንስሳት ማደን ባይቻል፣ የሰው ግዳይ
መቼ ይታጣል፣
ዛሬም ፉከራው ይሰማል፤ የአደን
ጥሪው ይደመጣል፣
በአፍሪካ ‹‹ጀሮ›› ተወዷል፤ በሎቲው
ገና ያጌጣል!
(ለጽንፈኛ አስተሳሰባቸው ሳይሆን፣
የምር ለነጻነት ሲባል ሕይወታቸውን እየከፈሉ ላሉ ግብጻዊያን መታሰቢያ የተገጠመ፣
ነሀሴ 8ቀን 2005ዓ.ም.)

Read 2641 times