በበርካታ የፊልም ሥራዎቹ በተለይ “የወንዶች ጉዳይ” በሚለው ፊልም ተዋናይነቱ የሚታወቀው አርቲስት መስፍን ኃይለኢየሱስ (ጠጆ) ዛሬ ከሰዓት በኋላ በቦሌ ክፍለ ከተማ በሚገኝ አንድ መናፈሻ በሚደረግ የኮክቴል ግብዣ ይሞሸራል፡፡ ከ”ዕንቆቅልሽ” ፊልም አዘጋጅና ፕሮዲዩሰር ቤዛ ሃይሉ ጋር ዛሬ የጋብቻ ሥነ ሥርዓቱን የሚፈፅመው ሙሽራው፤ አርቲስት ቴዎድሮስ ስዩምን፣ አርቲስት ዘርይሁን አስማማውን እና አቶ ማይለፍ ጌታቸውን፤ እንዲሁም ሙሽሪቷ ወይዘሪት ቤዛ ሀይሉ እነ ማህሌት ሹመቴን በሚዜነት መርጠዋል፡፡
በአሜሪካ ነዋሪ የሆነችው ቤዛ ኃይሉ ላለፉት ሁለት ዓመታት አብዛኛውን ኑሮዋን በኢትዮጵያ ያደረገች መሆኑንና ከፊልም አዘጋጅነቷ ሌላ የፊልም ፅሑፍ (Play writing) ደራሲ መሆኗም ታውቋል፡፡ መስፍን በ”የወንዶች ጉዳይ” ቁጥር አንድና ሁለት፣ በ”ሚዜዎቹ”፣ “ምስጢሩ”፣ ”ፔንዱለም”፣ “ጥሪ አይቀበልም” ፊልሞች በተዋናይነቱ በ”መካኒኩ” ፊልም ደግሞ በደራሲነቱ የሚታወቅ ሲሆን በቅርቡ “ሜድ ኢን ቻይና” የተሰኘ አዲስ ፊልም እንደሚያስመርቅ ይጠበቃል፡፡