Saturday, 31 August 2013 11:44

“ሆራይዘን ቡዩቲፉል ፊልም ውዝግብ አሰነሳ” ለሚለው ዘገባ “ከብሉናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚ” የተሰጠ መልስ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

“ሆራይዘን ቢዩቲፉል ፊልም ውዝግብ አስነሳ” በሚለው ዘገባ ”ብሉ ናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚን የሚመለከት ዘገባ መውጣቱ ይታወሳል፡፡ ይሁን እና የቀረበው አጭር ዘገባ የተዛቡ መረጃዎችና ስህተቶችን የያዘ በመሆኑ እንደሚከተለው እንዲታረም እንጠይቃለን፡፡
ለመነሻ ያህል ሆራይዘን ቢዩቲፉል በብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚና ቴል ፊልም በተባለ የስዊዘርላንድ ድርጅት የተሰራ የትምህርታዊ ፕሮጀክት ፊልም ሲሆን፣ ትምህርት ቤቱ በፊልሙ ስራ የተሳተፈበት አላማም ተማሪዎቹ ልምድ ካላቸው የውጭ የፊልም ባለሞያዎች ጋር ጐን ለጐን የሚሰሩበትን ተግባራዊ ልምምድ በማመቻቸት፣ የፊልም ስራ ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ ማስቻል ነው፡፡
ተማሪዎች በትምህርታዊ ፕሮጀክቱ ላይ የሳተፉት ገንዘብ እንደሚከፈላቸው ተነግሯቸው ሳይሆን ከፕሮጀክቱ ለመማር እና ራሳቸውን የተሻለ የፊልም ባለሞያ ለማድረግ በሙሉ ፈቃደኝነትም ጭምር ነው፡፡ በፊልም ስራው ላይ ከተለያዩ የትምህርት ዘመን የተውጣጡ ከ35 በላይ የትምህርት ቤቱ ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን፣ በፕሮዳክሽኑ መጨረሻ ከተማሪዎቻችን ጋር በተደረገው ግምገማ እና ውይይትም ትምህርታዊ ፕሮጀክቱ እጅግ ውጤታማ እና ተማሪዎቹ በርካታ ጠቃሚ እውቀት እና ልማዶችን ያካበቱበት መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡
የጋዜጠኛዋ ዘገባ፣ በፊልሙ ላይ የተሳተፉ ተማሪዎች አካዳሚው የሚገባንን ክፍያ እንዲሁም አንድ አመት የተማርንበትን ሰርተፊኬት ከልክሎናል እንዳሉ ያትታል፡፡ “ሆራይዘን ቢዩቲፉል” ብሉ ናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚ ቀደም ሲል ያስመረቃቸው እንዲሁም በወቅቱ በትምህርት ላይ የነበሩ ከ35 በላይ ተማሪዎች የተሳተፉበት ፊልም ነው፡፡ ጋዜጠኛዋ ክፍያ እና ሰርተፊኬት ተከልክለናል ያሉትን ግለሰቦች ስም ለመጥቀስ አልፈለችም፡፡ ከትምህርት ቤቱ ምክትል ስራ አስኪያጅ ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ ሁሉንም ተማሪዎች እንደምታነጋግር ቃል የገባች ሲሆን ትምህርት ቤቱም በፊልሙ ላይ የተሳተፉትን ተማሪዎች ስም ዝርዝር እና ስልክ ቁጥር ሰጥቷት ነበር፡፡ ጋዜጠኛዋ በወቅቱ እንደገለፀችው “ከተማሪዎቹ አንዳቸውም እንኳን ከላይ ክፍያ እና ሰርተፊኬት ተከልክለናል በሚለው ባይስማሙ በዘገባው ላይ ይህ ጥያቄ የተማሪዎቹ ጥያቄ እንደሆነ አድርጐ ማውጣት አግባብ አይደለም” ብላለች፡፡ ይሁን እና ሁሉንም ተማሪዎች ይቅርና የተማሪዎቹን ድምጽ ለመወከል የሚበቃ ቁጥር ያላቸውን ሳታናግር ብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚ ከመላው ተማሪዎቹ ጋር ተቃርኖ ውስጥ የገባ በማስመሰል ለማቅረብ ሞክራለች፡፡ የጥቂት ግለሰቦች አጀንዳ የሆነን ጉዳይ ግለሰቦቹን በማንነታቸው ከማቅረብ ይልቅ “ተማሪዎች” ከሚል መከለያ ጀርባ በመደበቅ ለማራመድ መሞከር ተገቢ የጋዜጠኝነት ስነ ምግባር አይመስለንም፡፡
“ተማሪዎቹ ተከለከልን አሉ” ስለተባለው ሰርተፊኬት ጉዳይም ለጋዜጠኛዋ የሰጠነው መልስ “…ያላሟሉት ነገር ቢኖር ነው” የሚል የመላምት መልስ ሳይሆን የሚከተለውን ነው፡፡ በፊልሙ ላይ የተሳተፉት ከተለያየ አመት የተውጣጡ ተማሪዎች እንደመሆናቸው መጠን፣ ከፊሎቹ ትምህርታቸውን አጠናቀው ፊልሙ ከመጀመሩ በፊት ሰርተፊኬታቸውን የወሰዱ ሲሆን ቀሪዎቹ ደግሞ በወቅቱ በትምህርት ላይ የነበሩ ናቸው፡፡ ከእነዚህም መሀከል ከትምህርት ገበታ አለመቅረትን፣ የልምምድ እና የመመረቂያ ፕሮጀክት መስራትን እንዲሁም ስነ ምግባርን ጨምሮ በትምህርት ቤቱ መመሪያ መሰረት ማሟላት ያለባቸውን ቅድመ ሁኔታ ያሟሉ ተማሪዎች የመመረቂያ ሰርተፊኬት የወሰዱ ሲሆን ይህን ላላጠናቀቁ ተማሪዎች ሰርተፍኬት መስጠት ግን የትምህርት ቤቱ ደንብ አይፈቅድም፡፡
3. ዘገባው ብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚ ከቴል ፊልም ስዊዘርላንድ ጋር በመተባበር የሰራው ፊልም ወደፊት ትርፍ ከተገኘበት ለፀሐፊዎቹ 10% ይከፈላል እንዳለ ይገልጻል፡፡ ለጋዜጠኛዋ በሁለቱ ድርጅቶች መሀከል የተፈረመውን የፕሮዳክሽን ስምምነት ከነአማርኛ ትርጉሙ የሰጠናት ከመሆኑም በላይ በቃለ መጠየቁ ወቅት ቃል በቃል እያነበብን እንዳስረዳነው፣ ከፊልሙ ከሚገኝ ማናቸውም ገቢ የተጣራ ትርፍ ላይ ቴል ፊልም የተባለው የስዊዘርላንድ ድርጅት ለፊልሙ ዋና ፀሐፊ ለሆነው የውጭ ዜጋ 10 በመቶ የሚከፍል ሲሆን፤ ይህም በአራቱ ፀሐፊዎች መሀከል እኩል የሚከፋፈል ይሆናል፡፡ ብሉ ናይል ለፀሐፊዎች የ10 በመቶ ክፍያ ይከፍላል የሚል መረጃ አልሰጠንም፤ በፕሮዳክሽን ስምምነቱም ውስጥ የተገለፀው ይህን አይደግፍም፡፡
4. ዘገባው የፊልሙ ክፍያን በተመለከተ በተነሳው ውዝግብ ፊልሙ ለእይታ እንዳልበቃ ጠቅሷል፡፡ ይህ ዘገባ ስህተት ሲሆን ትምህርት ቤቱ እስከሚያውቀው ድረስ ፊልሙ ለእይታ ያልበቃው የፖስት ፕሮዳክሽን ስራው ተጠናቆ ባለማለቁ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ይህ ተጠናቆ ፊልሙ በተለያዩ የውጭ አገር ፌስቲቫሎች ላይ በመታየት ላይ መሆኑን ከፊልሙ የፌስ ቡክ ገጽ መረዳት ይቻላል፡፡ ፊልሙ በአገር ውስጥ ለመታየት ያልቻለውም እንደተባለው በክፍያ ውዝግብ ሳይሆን በፊልሙ ላይ ምንም መብት የሌለው እና የቀድሞ የትምህርት ቤቱ ተማሪ የነበረ ግለሰብ፣ ከትምህርት በቱ ፈቃድ ውጭ ፊልሙን ለማሳየት በዝግጅት ላይ መሆኑን ትምህርት ቤቱ በመረዳቱ እና ይህን ለማስቆም ለሚመለከታቸው አካላት ባቀረበው አቤቱታ መሰረት፤ ትምህርት ቤቱ የፊልም ባለቤትነቱን በማረጋገጥ ሂደት ላይ በመሆኑ ነው፡፡ ይህ ከተጠናቀቀ በኋላ ለእይታ የሚቀርብ ይሆናል፡፡ ከዚህ ውጭ ፊልሙ በሌሎች ወገኖች ለእይታ ቢቀርብ ግን ትምህርት ቤቱ ህጋዊ እርምጃ የሚወስድ ይሆናል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ጋዜጠኛዋ ያቀረበችው መረጃ የአንድ ወገን እይታን ብቻ ያንፀባረቀ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡
ዘገባው ተማሪዎቹን እና ጸሀፊዎቹን ለያይቶ ለማቅረብ ያልቻለ ቢሆንም የፊልሙ ጸሀፊዎች የፊልሙን ጽሁፍ በሚያዘጋጁበት ጊዜ እያንዳንዳቸዉ 2500 ብር ብቻ እንደተከፈላቸዉ እና ለትራንስፖርት እና ሌሎች ወጪዎች ከኪሳቸዉ ሲያወጡ እንደነበረ ይገልጻል፡፡ አሁንም የጸሀፈዎቹን ስም ለመግለጸ እንዳልተፈለገ ልብ ይሏል፡፡ በቃለ መጠይቁ ወቅት ጋዜጠኛዋ ጸሀፊዎቹ ምንም አይነት ክፍያ እልተሰጠንም እንዳሏት ገልጻ፣ ይህ ለምን እንደሆነ ጠይቃለች፡፡ በምላሹም ይህ ስህተት እንደሆነ እና ምንም እንኳን ፊልሙ ትምህርታዊ ፕሮጀክት ቢሆንም ጸሀፊዎቹ በስራ ወቅት ለሚያወጡት ወጪ እና ከሌላ ስራ ያገኙት የነበረዉን ገቢ በጥቂቱም ቢሆን ለማካካስ በየወሩ 2500 ብር ሲከፈላቸዉ እንደነበረ፣ ለትራንስፖርት እና ሌሎች ወጪዎችም ባቀረቡት ደረሰኝ መሰረት እንደተከፈላቸዉ ገልጻ ለዚህም በእጃችን የነበረዉን ማስረጃ አሳይተናል፡፡ ይሁን እና ጋዜጠኛዋ የእኛን መልስ እና ማስረጃ ወደጎን በመተዉ ይልቁንም ያቀረብነዉን ማስረጃ እነዚህ ግለሰቦች የሰጡትን የተሳሳተ ማስረጃ “የተከፈለን 2500 ብር ብቻ ነዉ” ወደሚል ማስተካከያ ለመቀየር ተጠቅማበታለች፡፡ አንድ ጋዜጠኛ የተሰጠዉ መረጃ ስህተት አንደነበረ የሚያረጋግጥ መረጃ ሲደርሰዉ ይህን እንዳላዩ ማለፍ እና ይበልጡንም የሀሰት ማስረጃ የሰጡትን ግሰቦች ቃል ለማስተካከል መጠቀሙ ወገንተኝነትን የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ የጋዜጠኛዉን ሀቀኝነት እና ተአማኒነት ጥያቄ ዉስጥ የሚጥል ነዉ፡፡
በዘገባዉ የቀረበዉ የገንዘብ መጠንም እንዲሁ ገንዘቡ ወደብር ሲለወጥ በፊልሙ ዝግጅት ወቅት ከአንድ አመት ከሰባት ወር በፊት ባለው የምንዛሪ ሂሳብ ሳይሆን ዛሬ ባለዉ በመሆኑ ስህተት ነዉ፡፡ በዚህም መሰረት የገንዘብ መጠኑ እንደተባለዉ 360,400 ብር ሳይሆን 252,000 ብር ነው፡፡
ከላይ የተገለጻዉን ገንዘብ አጠቃቀም በተመለከተም ብሉ ናይል የፊልም እና ቴሌቪዥን አካዳሚ ከተቋቋመበት አላማም ሆነ “ከሆራይዘን ቢዩቲፉል” ትምህርታዊ የፊልም ፕሮጀክት አላማ አኳያ፤ ትምህርት ቤቱ ገንዘቡን በደሞዝ መልክ ማከፋፈል ሳይሆን ተጨማሪ ትምህርታዊ የፊልም ፕሮጀክቶችን በመስራት ነባር እና መጪ ተማሪዎች ክህሎታቸዉን እንዲያዳብሩ የማድረግ አቋም ያለዉ መሆኑን እንገልጻለን፡፡
ከሰላምታ ጋር
ብሉ ናይል የፊልም እና የቴሌቪዥን አካዳሚ

Read 14442 times