Saturday, 07 September 2013 10:22

የ40/60 የቤት ፕሮግራም የግንባታ ሂደት

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(15 votes)

በ3 አመት ውስጥ 20ሺህ ቤቶች ለተጠቃሚ ይተላለፋሉ
በቀጣይ አመት የመጀመሪያዎቹ እድለኞች የቤት ባለቤት ይሆናሉ
በ5 አመት ውስጥ ሁሉም ተመዝጋቢዎች ቤት ያገኛሉ
ቀደም ብሎ በተዘጋጀው የ40/60 የቤቶች ፕሮግራም ስትራቴጂክ እቅድ መሠረት በሶስት አመት ውስጥ 20ሺ ቤቶች ተገንብተው ለተጠቃሚዎች እንደሚተላለፉ እንዲሁም ግንባታቸው አስቀድሞ የተጀመሩት በመጪው ዓመት ግንቦት ወር ላይ ለመጀመሪያዎቹ እድለኞች ተጠናቀው እንደሚሠጡና ባለፈው ነሐሴ የተመዘገቡ 164ሺ ቤት ፈላጊዎች በአምስት አመት ውስጥ የቤት ባለቤት እንደሚሆኑ ተገለፀ፡፡
ይህንኑ ፕሮግራም ተከታትሎ እንዲያስፈፅም የተቋቋመው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቁጠባ ቤቶች ልማት ፅ/ቤት የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ደጋፊ የስራ ሂደት መሪ አቶ ዮሐንስ አባይነህ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ከ2005-2006 ዓ.ም ሊገነቡ ለታሠቡት የ40/60 መኖሪያ ቤቶች ግንባታ በአጠቃላይ 1.25 ሚሊዬን ብር በጀት የተያዘ ሲሆን በአሁን ወቅት 10ሺ 820 ለሚሆኑ ቤቶች ግንባታ ወደ 50 ሄክታር መሬት ተዘጋጅቷል፡፡
እነዚህ በአጠቃላይ በሶስት አመት ውስጥ ይጠናቀቃሉ የተባሉ ቤቶችም በሠንጋ ተራ ክራውን ሣይት፣ እህል ንግድ፣ ቦሌ፣ መሪ፣ አስኮ እንዲሁም ቦሌ ቡልቡላ አካባቢዎች ለመልሶ ማልማት በተመረጡ ቦታዎች ላይ ይገነባሉ የሚሉት ሃላፊው፤ ቀደም ብሎ በሠንጋ ተራ፣ ክራውን ሣይት እንዲሁም ቦሌ ቡልቡላ አካባቢዎች የቤቶቹ ግንባታ ተጀምሯል ብለዋል፡፡ አቶ ዮሐንስ አክለውም፤ በሠንጋ ተራ አካባቢ ግንባታው 20 በመቶ የደረሠ መሆኑን በማመልከት፣ የሚገነቡት ቤቶች በአምስት ብሎኮች የተከፋፈሉ ሆነው ብዛታቸው 410 መሆኑን፤ በክራውን ሣይት ደግሞ በ14 ብሎኮች ተከፋፍለው 882 ቤቶች የሚገነቡ ሲሆን ግንባታው 10 በመቶ ደርሷል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በእነዚህ አካባቢዎች የሚገነቡት ቤቶች በግንቦት ወር 2006 ግንባታቸው 95 በመቶ ይደርሣል ተብሎ የሚገመት ሲሆን ቀሪውን የማጠናቀቂያ ስራ የቤቱ ባለቤቶች የሚፈፅሙት ይሆናል ብለዋል፤ ሃላፊው፡፡
በመስከረም አጋማሽ ግንባታቸው በሚጀመረው በኢምፔሪያል አካባቢ ወደ 650 ቤቶች፣ በእህል ንግድ አካባቢ 1476 ቤቶች፣ በመሪ አካባቢ 1148 ቤቶች፣ በአስኮ አካባቢ 1148 ቤቶች እንዲሁም በቦሌ ቡልቡላ 550 ቤቶች እንደሚገነቡ የተናገሩት አቶ ዮሐንስ፤ እቅዱ ምናልባት አዲስ ይፀድቃል ተብሎ የሚጠበቀውን የከተማዋን ስትራቴጂክ እቅድ ታሣቢ ባደረገ መልኩ ሊቀየር እንደሚችልም ጠቁመዋል፡፡
ግንባታቸው የተጀመሩት ቤቶች ሙሉ በሙሉ በሃገር ውስጥ ደረጃ 1 የህንፃ ተቋራጮች የሚገነቡ ሲሆን በአሁን ሠአት ከ1226 በላይ ለሚሆኑ ሠዎች የስራ እድል መፈጠሩን በቀጣይ ደግሞ ቁጥሩ ወደ 10ሺህ ያድጋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የሥራ ሂደት መሪው ገልፀዋል፡፡
የሚገነቡት ህንፃዎች ቁመት እንደየአካባቢው የሚለያይ ሲሆን አሁን በተጀመሩት ሣይቶች ላይ የሚገነቡት በሠንጋ ተራ ባለ 12 ፎቅ፣ በቦሌ ቡልቡላ ባለ 7 ፎቅ እንዲሁም ክራውን ሣይት ባለ 9 ፎቅ ህንፃዎች ይገነባሉ፡፡
በምዝገባው ወቅት በርካቶች በባለ ሁለት እና ሶስት መኝታ ቤት የተመዘገቡ በመሆኑም ቀደም ብሎ የነበረው የቤቶቹ የውስጥ ዲዛይን ለውጥ እንደሚደረግም አቶ ዮሐንስ ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል ሁለት የ40/60 ቤት ግንባታዎች የሚከናወኑት በአዲስ አበባ በ10 ኪሎ ሜትር ራዲየስ ውስጥ ሲሆን የሁሉም አካባቢ ቤቶች ዋጋ ተመሣሣይ መሆኑን ሃላፊው ገልፀዋል፡፡

Read 7597 times