Monday, 16 September 2013 07:38

“ሁዋዌ ኢትዮጵያ” ለክብረ የአረጋውያን ምግባረ ሰናይ ድርጅት ዕርዳታ ሰጠ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

“ሁዋዌ ኢትዮጵያ” በአዲስ ዓመት ዕለት ለክብረ የአረጋውያን ግብረ ሠናይ ድርጅት የተለያዩ ቁሳቁስ ስጦታ ያበረከተ ሲሆን የምሳም ግብዣ አድርጓል፡፡
ሁዋዌ፣ ያበረከተው ቁሳቁስ ትልቅ የልብስ ማጠቢያ ማሽን፣ የውሃ ማጣሪያ፣ ፍራሾች፣ ብርድልብሶችና የምግብ እህሎች ሲሆኑ፣ ጠቅላላ 60ሺህ ብር ግምት እንዳላቸው ታውቋል፡፡
ስጦታውን ለማዕከሉ መሥራችና ዳይሬክተር ለወ/ሮ ወርቅነሽ ሙንኤ ያስረከቡት የ “ሁዋዌ ኢትዮጵያ” ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሚ/ር ቶኒ ዱዋን ባደረጉት ንግግር፤ በዚህ ልዩ ዕለት ከአረጋውያን አባቶቻችንና እናቶቻችን እንዲሁም ከማዕከሉ ሠራተኞች ጋር ተጋርተን የተመገብነው ምሳ የበዓል ስሜት መፍጠሩን እርግጠኛ ነኝ ብለዋል፡፡
ወ/ሮ ወርቅነሽ በዚሁ ጊዜ ባደረጉት ንግግር፤ ክብረ የአረጋውያን ምግባረ ሰናይ ድርጅትን ከስድስት ዓመት በፊት በቤተሰባቸው በጀት መጀመራቸው ጠቅሰው በአሁኑ ሰዓት 14 ሴትና 24 ወንድ አረጋውያንን በቀን ሦስት ጊዜ እያበሉ፣ እያለበሱና ንጽህናቸውን እየጠበቁ በመንከባከብ ላይ መሆናቸውን እየተንከባከቡ መሆኑን ገልፀዋል።
በማኅበረሰብ አቀፍ ፕሮግራማቸው ደግሞ፣ የአቅመ ደካሞችን ቤቶች ማደሳቸውን፣ የመሥራት አቅም ላላቸው ሴቶች ከ100 እስከ 150 ብር የገንዘብ ድጐማ በመስጠት ገቢያቸውን ከፍ እንዲያደርጉ መርዳታቸውን ጠቅሰው፣ በዚህ ፕሮግራም እስከ አሁን ድረስ 716 አረጋውያንን መርዳታቸውን አስታውቀዋል፡፡
የአዲስ አበባ መስተዳድር ለአረጋውያን መርጃ መሬት በነፃ ስለሰጣቸው አመስግነው፣ በቦታው ላይ 200 አረጋውያንን መያዝ የሚችል መኖሪያ፣ ሆስፒታል፣ እንግዳ ማረፊያ፣ የስብሰባ አዳራሽና የገቢ መፍጠሪያ ማዕከል እየገነቡ መሆኑን ጠቅሰው፣ አቅሙ ያለው ሁሉ ለግንባታው ድጋፍ እንዲያደርግላቸው ጠይቀዋል፡፡ “ሁዋዌ ኢትዮጵያ” በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ የተሰማራ የቻይና ኩባንያ መሆኑ ታውቋል፡፡

Read 10100 times