Monday, 16 September 2013 07:41

የኤርፖርት ሚኒባስ ታክሲ ሹፌሮች ዩኒፎርም ልበሱ ተባሉ

Written by  ሰላም ገረመው
Rate this item
(6 votes)

የ1ሺ 500 ብር ሱፍ ወደ 500 ብር ዩኒፎርም ዝቅ ተደርጓል
ጫት የሚቅም ፣ሲጋራ የሚያጨስና ፀጉሩ የተንጨባረረ ሹፌር መግባት አይፈቀድለትም

ኤርፖርት ውስጥ ገብተው የሚጭኑ የሚኒባስ ታክሲ ሾፌሮችና ረዳቶች ዩኒፎርም እንዲለብሱ የታዘዘ ሲሆን ከሚቀጥለው ረቡዕ ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚሆንም ተገለፀ፡፡
ቀደም ሲል ሹፌሮቹ የ1ሺ 500 ብር ሱፍ እንዲለብሱ ተወስኖ የነበረ ቢሆንም አቅማቸውን ያላገናዘበ በመሆኑ በ500 ብር ዩኒፎርም መተካቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በቦሌ ዞን የንስር ታክሲ ባለንብረቶች ማህበር የስምሪት እና የቁጥጥር ሃላፊ አቶ አያሌው ሲሳይ እንደገለፁት፤ በቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ቅጥር ግቢ ገብተው እንዲሰሩ የተፈቀደላቸው የሚኒባስ ታክሲ ሾፌሮችና ረዳቶች ለአየር መንገዱ ስርዓትና ክብር ሲባል አንድ አይነት ዩኒፎርም እንዲለብሱ ተወስኗል፡፡
የኤርፖርቱን ደረጃ ለመጠበቅና “ታክሲ አሽከርካሪዎች ነን፣ ረዳቶች ነን” በሚል ማጭበርበር እንዳይፈፀም ታስቦ ዩኒፎርሙን ማስለበስ እንዳስፈለገ የሚናገሩት አቶ አያሌው፤ ቀደም ሲል ሹፌሮቹም ረዳቶቹም ሱፍ እንዲለብሱ ታስቦ እንደነበረ ገልፀው ነገር ግን ዋጋው 1ሺህ 500 ብር በመሆኑና የሹፌሩንና የረዳቱን አቅም ያገናዘበ አይደለም በመባሉ ከተወካዮቻቸው ጋር ተወያይተን ሹፌሮቹ 500 ብር የሚያወጣ ጥራቱን የጠበቀ እንደጋውን ያለ ሸሚዝ እንዲለብሱ፣ ረዳቶች ደግሞ በ300 ብር ወጪ ዩኒፎርም እንደሚያሰፉ ገልፀው፤ ዩኒፎርሙ የሚያገለግለው ታክሲዎቹ በኤርፖርቱ ለሚመደቡበት የሶስት ወር ጊዜ ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ዩኒፎርሙን ያልለበሱ የታክሲ ሹፌሮችና ረዳቶች ወደ ተርሚናሉ እንደማይገቡ የገለፁት አቶ አያሌው፤ ፀጉራቸውን ያንጨባረሩ፣ ጫት የሚቅሙና ሲጋራ የሚያጨሱም ወደ ኤርፖርቱ መግባት አይፈቀድላቸውም ብለዋል፡፡ ዩኒፎርም መልበሳቸው ብቻ ሳይሆን ንፅህናቸውንም መጠበቅ እንዳለባቸው የተናገሩት አቶ አያሌው፤ ይህንን ማሟላት የማይችሉ ሹፌሮች ውስጥ መግባት ባይችሉም ከቦሌ ድልድይ ጀምረው መስራት እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡በኤርፖርት ውስጥ ገብተው የሚሰሩ ታክሲዎች ሲወጡና ሲገቡ ሰዓት ከመመዝገብ አንስቶ ከፍተኛ ቁጥጥር እንሚደረግባቸው የገለፁት አቶ አያሌው፤ ይህም አገልግሎቱ በስርዓት እንዲሰጥ ከማድረጉም በተጨማሪ የተሳፋሪዎች ንብረቶች እንዳይጠፉ ለመከላከል ያስችላል ብለዋል፡፡

Read 13113 times