Monday, 16 September 2013 07:43

“አንድነት” የነገውን ሰላማዊ ሰልፍ ለመስከረም 19 አዛወረ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

አንድነት ለዲሞክራሲ እና ለፍትህ ፓርቲ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ለማካሄድ አቅዶት የነበረውን ሰላማዊ ሰልፍ ለመስከረም 19 ማዛወሩን የፓርቲው ዋና ፀሃፊ አቶ ዳንኤል ተፈራ ገለፁ፡፡
ፓርቲው “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል ለሶስት ወራት ሲያደርግ የቆየውን የተቃውሞ ሰልፍ ማጠናቀቂያ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ለማድረግ አቅዶ የነበረ ሲሆን ከመስተዳደሩ ጋር ባደረጉት ውይይት ሰላማዊ ሰልፉን ለመስከረም 19 ለማዛወር ስምምነት ላይ መደረሱን አስታውቋል፡፡ ፓርቲው እስካሁን በተለያዩ ክልሎች ባካሄዳቸው ሰላማዊ ሰልፎች ላይ በራሪ ወረቀቶችና ፖስተሮች እንዳይበትኑና እንዳይለጠፉ እንዲሁም ቅስቀሳ እንዳያካሂዱ ጫና ይደረግባቸው እንደነበር የጠቆሙት የፓርቲው ዋና ፀሃፊ፤ እንዲህ ያሉ ችግሮች እንደማይደርስባቸው ከመስተዳደሩ ጋር ባደረጉት ውይይት እንደተገለፀላቸው ተናግረዋል፡፡
መስተዳደሩ እስከ መስከረም 16 ድረስ ምንም ዓይነት ሰልፍ ማድረግ እንደማይቻል የገለፀላቸው መሆኑን የተናገሩት አቶ ዳንኤል፤ ለዚህ ምክንያቱም ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤት የሚሄዱበት፣ የበዓል ወቅት በመሆኑና ለባቡር ዝርጋታ ተብሎ የተከለለው አጥር መነሳት ስላለበት እንደሆነ መስተዳደሩ ገልፆልናል ብለዋል፡፡ ፓርቲው ምክንያቱን ተቀብሎ የሰላማዊ ሰልፉን ቀን እንደለወጠና ከመስተዳደሩ ሰላማዊ ሰልፉ መፈቀዱን የሚገልፅ ደብዳቤ መቀበሉን ዋና ፀሃፊው ገልፀዋል፡፡
ቀኑ መቀየሩ ለእኛም ጥቅም አለው ያሉት አቶ ዳንኤል፤ ፖስተር ለመለጠፍ እና ፍላየር ለመበተን ጊዜ ያስፈልገን ነበር፤ ጊዜው መራዘሙ ይህንን በስፋት እንድናከናውን ያግዘናል ብለዋል። መስከረም 19 ቀን የሚደረገውን ሰላማዊ ሰልፍ የፓርቲው ሊ/መንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እንደሚመሩትም አክለው ገልፀዋል - አቶ ዳንኤል።

Read 15219 times