Print this page
Monday, 16 September 2013 07:51

የዶ/ር መረራ ጉዲና መፅሃፍ በጨረፍታ

Written by 
Rate this item
(17 votes)

ከአዘጋጁ፡- ከዚህ በታች የቀረበው ፅሁፍ ከዶ/ር መረራ ጉዲና የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞና የህይወቴ ትዝታዎች መፅሃፍ አለፍ አለፍ ተብሎ የተወሰደ ሲሆን መፅሃፉን ያላገኙ አንባቢያን መጠነኛ ግንዛቤ እንዲያገኙ በሚል ያወጣነው ነው፡፡
ምዕራፍ 11፡ የ2002 ምርጫና አዳዲስ የኢህአዴግ ሴራዎች
በሀገር ውስጥም ከሀገር ውጪም የብዙ ሰዎች ዓይን የተተከለው በ1997ቱ ምርጫ ላይ ነው። እስከ 1997ቱ ምርጫ ድረስ ደግሞ የብዙዎች የፖለቲካ እይታ የተሰራው በተጨናገፈው የ1966ቱ አብዮት ላይ ነበር፡፡ የ1997ቱ ምርጫ ለሁለተኛ ጊዜ የትውልድን ቀልብ ስቦ አልፎአል፡፡ ህዝቡን ከዛ አላቆ ወደፊት እንዲመለከት ለማድረግ ቀላል አልሆነም፡፡ በምርጫ ውጤት ተደናግጦ የነበረው ኢህአዴግም አስተማማኝ ምርኩዜ ነው በሚለው ጠመንጃ ስር መደበቁን መርጧል፡፡ ተቃዋሚውም ድርጅት ከመፈልፈልና ከመከፋፈል በሽታው አልዳነም። በተለይ አንባቢ ልብ እንዲልልኝ የምፈልገው፣ ተቃዋሚው በ1997ቱም ሆነ ዛሬ ሰፊ ህዝባዊ ድጋፍ (popular support) አለው። ዛሬም ከአንድ ወር ባነሰ እንቅስቃሴ ኢህአዴግን ኮርቶ ማሸነፍ ይችላል። የኢህአዴግ ባለስልጣናትም በህዝብ እውነተኛ ድጋፍ ሳይሆን የሀገሪቷን ፀጥታ ኃይል ምርኩዝ አድርገው እንደሚኖሩ ልቦናቸው ያውቃል፡፡ ተቃዋሚው በ1997ቱም ሆነ ዛሬም በቂ የተደራጀ ድጋፍ (organized support) የለውም፡፡ ደጋግሜ ለማሳየት እንደሞከርኩት ይህ ክፍተት ካልተደፈነ በስተቀር ሁሉም ነገሮች በጎ ፈቃድ እስከምን ድረስ ድረስ እንደሆነ በ2002ቱ ምርጫ በሚገባ አይተናል። ስለሆነም፣የተቃዋሚዎች አጣዳፊ ተግባር መሆን ያለበት ክፍተቱን በመድፈን አቅም ፈጥሮ መንቀሳቀስ ብቻ ነው፡፡
እስከሚገባኝ ድረስ የሀገራችን ፖለቲካ አንድ ወሳኝ እርምጃ ወደፊት ሊሄድ የሚችለው ሁሉም ከራሱ የህልም ዓለም በመውጣት፣ ዲሞክራቲክ ኢትዮጵያን ለመፍጠር ዋነኛ አጀንዳ ላይ መረባረብ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ፣ በአንድ በኩል መገንጠልን እንደዋነኛ የፖለቲካ አጀንዳ ማራመድንና በሌላ በኩል ደግሞ “ኢትዮጵያ እምዬ ምኒሊክ በፈጠሯት መልኳ ትኑር” የሚሉትን ሁለቱን የሀገራችንን የፖለቲካ ጫፎች በማቀራረብ በመሃል መንገድ ላይ ወርቃማ አማካይ (the golden mean) መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ ከታሪክ ጣጣችን የሚመነጩ ልዩነቶች በአንድ ጀንበር ካልተፈቱ ብሎ የሙጥኝ ማለት የዲሞክራቲክ ኢትዮጵያን መወለድ ማዘግየትና የገዢው ፓርቲ የከፋፍለህ ግዛ ሴራ ሰለባ ከመሆን ያለፈ ምንም ፋይዳ የለውም። የአንዳንዶች ህልም እስኪሟላ የጋራ ህልም እንዳይሳካ ማጨናገፍ፣ከራስ ህልም ጋር እየዋዠቁ ከመጓዝ ያለፈ የፖለቲካ ፋይዳ የለውም፡፡ ያለፉት የአርባ ዓመታት ታሪካችንም የሚያረጋግጥው ይህንኑ ሃቅ ነው፡፡
ምርጫ 97 እና 2002
በሁሉም መንገድ የ2002 ምርጫ የ1997ቱን አይመስልም፡፡ ኢህአዴግ የ1997ቱ ጎርፍ ተመልሶ እንዳይመጣበት በዓለም ሊኖሩ የሚችሉ ሁሉም ምርጫን የማዛባት ታክቲኮችን ቀምሞ ነበር የጠበቀን፡፡ ከሁሉም በላይ የ1997ቱን የሕዝብ ጎርፍ የቀሰቀሰውን የቀጥታ ስርጭት ክርክር እንዳይኖር አድርጓል፡፡ ጥቂት የተፈቀዱ ክርክሮችም የተደረጉት በተመልካች አልባ ስቱዲዮ በቀጥታ የማይሰራጩ ነበሩ፡፡ በቴሌቪዥንና ሬድዮ እንዲነበብ የሚደረጉ የሳንሱር መቀስን ማለፍ ነበረባቸው፡፡ ህዝባዊ ስብሰባዎችም በብዙ መንገዶች ተተብትበው እንዳይካሄዱ ተደርገዋል፡፡ የተካሄዱትም የ1997ቱን ጎርፍ የሚመስሉ በጥቂት ቦታዎች ብቻ ነበር፡፡ ለአብነት መኪናችንን እንዲሰብሩ የንብ ምክንቶች (ንብ ኢህአዴግ የምርጫ ምልክት ነው) የያዙ ወጣቶች በብዙ ቦታዎች ተሰማርተው መንገድ ይዘጉብን ነበር፡፡ አንዳንድ ቦታዎች እስታዲየሞች ተፈቅዶልን ቁልፍ የያዙ ዘበኞች እንዲሰወሩ ተደርገዋል፡፡ እዚህ ላይ አንባቢው የተሻለ ሥዕል እንዲኖረው ትንሽ ልዘርዝር፡፡
በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ባልታዬ መንገድ በተደረገው የ1997ቱ ክርክር ውስጥ በተደጋጋሚ ተሳትፎ የነበረኝ ሰው፣በ2002ቱ ምርጫ የተሳተፍኩት አንድ ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ እሷም በተደረገችው በጠባብ ስቱዲዮ ያለተመልካች ስትሆን፣ኢህአዴግ ጋዜጠኛ ጠያቂ ሆኖ፣አጠቃላይ ሁኔታውን በተቆጣጠረበት መንገድ ነው፡፡ የቀጥታ ስርጭቱን ስለከለከሉ ፕሮግራሞች ተቆራርጠው ይተላለፉ ነበር፡፡ ኢህአዴግ በፈለገበት ሰዓትና መንገድ ብቻ ነበር የሚቀርቡት፡፡ ንፅፅር ካስፈለገ ጣሊያን የአድዋን ሽንፈትዋን ለመቀበል የቻለችውን ሁሉ ተዘጋጅታ ከ40 ሰዓት በኋላ እንደመጣች ሁሉ ኢህአዴግም የ1997ቱን ሽንፈቱን ለመቀበል ሊያደርግ የሚችለውን ሁሉ አድርጎ ነበር ተዘጋጅቶ የመጣው፡፡ በእንግሊዝ ዲፕሎማቶች አቀናባሪነት (ሴራም ለማለት ይቻላል) አቶ ሃይሉ ሻውልም የፈረሙት ስነ-ምግባር ተብዬው ምን ያክል እንደጎዳን ያወቅሁት ለቅስቀሳ መስክ በወጣሁ ጊዜ ነበር፡፡ “እዚህ ቤተክርስቲያን አለ፣ቅስቀሳ ክልክል ነው፤ እዛ መስጊድ አለ መቀስቀስ አይቻልም፤ ዛሬ ገበያ ነው ቅስቀሳ አይፈቀድም፤ እዚህ ትምህርት ቤት አለ፤ መቀስቀስ ፈፅሞ የተከለከለ ነው” እየተባለ እንቅስቃሴዎቻችንን ገደቡ፡፡ ከሌሎቹ የመድረክ መሪዎች በተለየ መንገድ ለመንቀሳቀስ ስለሞከርኩ ኢህአዴግም እያንዳንዱን እንቅስቃሴዬን ለመቆጣጠር መንቀሳቀሱን ያወቅሁት ከውስጥ ከተገዙት አባሎቻችን፣ ሲፈን ጐንፋ የሚባል ወጣት በመጨረሻ ላይ ከያዘው ለየት ያለ የድምፅ መቅጃ መሣሪያ ጋር የተያዘ ጊዜ ነው፡፡ ይህን ልጅ ብጠረጥር በኦነግነት እንጅ በጭራሽ በመንግሥት ሰላይነት አልነበረም፡፡ ሲፈን እውነተኛ የኦሮሞ ልጅ ለመሆን ስሙን ወደ ኦሮሞ የቀየረና፣ አንድ ጊዜ ኦፒድኦ ብዙ የኦሮሞ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ጂማ ላይ ሰብስቦ የድርጅት አባል እንዲሆኑ የጠየቀ ጊዜ “ኦፒዲኦ ከመሆን እራሴን እሰቅላለሁ” ብሎ ገመድ ይዞ ሲሮጥ ተማሪዎች ተረባርበው እንዳስጣሉት መረጃው ስለነበረኝ፣ በፍጹም ለመንግስት ሰላይ ሆኖ ይሠራል ብዬ አልጠረጠርኩትም፡፡ ከነድምፅ መቅጃው እጅ ከፍንጅ ባይያዝ ኖሮ ሰው ሰላይ ነው ብሎ ቢነገረኝ አላምንም ነበር፡፡ ከመኢሶን ዘመን ጀምሮ በክህደት ባልደነግጥም፣ የዚህኛው ልጅ ትንሽ ገርሞኛል። ፖሊሶች ሊይዙት ሲሉ፣ የያዘውን ወረቀት አኝኮ ውጧል ተብሎ የሚወራለት አበራ የሚባል ዘመዱም እንዲሁ በቀላሉ ከድቶናል፡፡ የኦሮሞ ልጆች ለዓላማቸው ሳይሆን ለሆዳቸው ብለው ሕዝባቸውን ሲክዱ ከመናደድ ይልቅ በጣም ያሳዝነኛል፡፡ ሲፈን ጎንፋ የሚባለውን ልጅ ከኔ ጋር ለቅስቀሳ ወደ ወለጋ ስንሄድ፣ ቶኬ የምትባል የትውልድ አካባቢዬ ላይ ሆዱ እጅግ በጣም ገፍቶ እርጉዝ ሴት የመሰለ ሰው፣ “ኢህአዴግን ለልማት ምረጡ” የሚል መፈክር ይዞ ቆሞ አገኘነው፡፡ ሲፈን ቶሎ ብሎ የዚህን ሰው ያረገዘ ሆድ እያሳየ “የቶኬ ህዝብ በአንተ ሀብት የለማው አንተ ሳትሆን የእሱ ሆድ ነው” ማለቱንና የኢህአዴግ ካድሬዎች የሰበሰቡት ሕዝብ ጭምር ሲስቅበት፣ ሰውዬው አፍሮ ቦርጩንና የኢህአዴግን መፈክር ይዞ መሰወሩ ዛሬም ትዝ ይለኛል፡፡ ከዛን ጊዜ ጀምሮ ሲፈንን ባላየውም ሆዱ እንደዛ ሰው ለምቶ ይሆናል። እሱም የከዳን ከዛ ለተሻለ ዓላማ አይመስለኝም፡፡
“የሐረርጌ ህዝብ ልብ ከናንተ ጋር ነው”
…ከ1997ቱ ምርጫ ይልቅ በሰሜን ሸዋ/ስላሴ በ2002ቱ ምርጫ ብዛት ባላቸው ወረዳዎች ውስጥ ብንወዳደርም፣ እንቅስቃሴያችን ብዙ የተሻለ አልነበረም፡፡ መለስተኛ ሕዝባዊ ስብሰባዎችን ያደረግነው በኩዩና ወረጀርሶ (ጐኃጽዮን) ከተማ ብቻ ነበር፡፡ በቀሩት ከተሞች፣ እንደቡ አቦቴ የነጄኔራል ታደሰ ብሩ ወረዳ ጨምሮ በብዙ ቦታዎች ያደረግነው በጎዳና ላይ ቅስቀሳ ብቻ ነበር፡፡ የመንገድ ላይ ቅስቀሳውን ግን ብዙ ሠርተንበታል፡፡
ከሰላሌ ቀጥሎ ጉዞአችን ወደ አንዱና ትልቁ መሥመራችን የሐረርጌ መሥመር ነበር፡፡ በዚህ መሥመር፣ በሁለት ፓርላማ አባላት የሚመሩ ሁለት ቡድኖችን አስቀድመን አስመርተን ነበር፡፡ እኔ ተከትያቸው ስደርስ፣ በምዕራቡም፣ በምሥራቁም የ1997ቱ ምርጫን የመሰለ የሕዝብ ጐርፍ አልነበርም። ተወዳዳሪዎቻችንም ከጫት ያለፈ ዓላማ የነበራቸው አይመስልም፡፡ ከ90ሺ በላይ ሕዝብ ወጥቶ፣ እኔንም ሰዎች ተሸክመው መድረክ ላይ ያወጡበት የሐረር ከተማ ጭር ብላ ነበር የጠበቀችን፡፡ ሐሮማያ/ዓለማያ ዩኒቨርሲቲ አጠገብ በጠራነው ስብሰባ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንኳ አልነበሩም፡፡ ስብሰባውን ለማዳመጥ ከመጡት ሰዎች የመንግሥት ቪዲዮ አንሺዎች ይበዙ ነበር፡፡ የነበረን ብቸኛ አማራጭ በጎዳና ላይ ሰፊ ቅሰቀሳ አድርገን ወደ ድሬዳዋ ማምራት ነው፡፡ የድሬዳዋ ከተማ የኦሮሚያ ክልልና የሱማሌ ክልል ካድሬዎች የሚራኮቱበት ቦታ ስለሆነችና በከተማው ላይ ስብሰባ የምናካሂድበት ቦታ ስለከለከሉን በሦስት ላንድክሩዘሮች የመንገድ ላይ ቅስቀሳችንን አድርገን ወደጨለንቆ ጉዞአችንን ቀጠልን፡፡ ጨለንቆ ላይ የነበረው አህመድ ነጃሽ የሚባለው ተወዳዳሪያችን የጃራ አባ ገዳ የቅርብ ዘመድ የሆነ ሰው ስለሆነ እራሱን ችሎ ለመንቀሳቀስ የሚችል ነበር፡፡ ከዛ ሁለት ቀን በፊት ደደር ላይ ከባድ ዝናብ ዘንቦ ስብሰባ እንደከለከለን፣ ጨለንቆ ላይም ከለከለን። ተፈጥሮም ከነዚህ ሰዎች ጋር ተባብሮብናል ብለን ወደ ጭሮ አመራን፡፡ ጭሮ ላይ ኦፒዲኦ መሆናቸውን ባይረሱም፣ ቢራ የጋበዙን የኦፒዲኦ ልጆችን አገኘን፡፡ ገለምሶና ጭሮ ላይ መለስተኛ ስብሰባዎችን አድርገን ወደ ሸገራችን ተመለስን፡፡ እንደ ሐረር ከተማው፣ ጭሮም ላይ የ1997ቱን ስብሰባ የመሰለ ነገር ማካሄዱ አልተሳካልንም፡፡ የ1997ቱ ምርጫ ላይ አግኝታኝ የነበረች ልጅ “የህዝብ ብዛቱን አይተህ አትዘን፤ የሀረርጌ ህዝብ ልብ ከእናንተ ጋር ነው” አለችኝ፡፡ በዚሁ ጥሩ ማፅናኛ የሐረርጌን ህዝብንና ምድር ተሰናብተን ጉዟችንን ወደ ሸዋ ቀጠልን፡፡

Read 5791 times
Administrator

Latest from Administrator