Print this page
Saturday, 21 September 2013 09:53

ሰማያዊ ፓርቲ የሰላማዊ ሰልፍ ቦታ ላለመቀየር ወሰነ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(4 votes)

            ሰማያዊ ፓርቲ ነገ እሁድ በመስቀል አደባባይ የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ እንቅፋት እንዳጋጠመው የተናገሩት የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ ቦታው ለተቃዋሚዎች አይፈቀድም እንደተባሉ ገለፁ፡፡ በአዲስ አበባ መስተዳድር፣ የስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል ሃላፊ አቶ ማርቆስ ብዙነህ በበኩላቸው፤ ስፍራው ለልማት የታጠረ በመሆኑ የትኛውም አካል በስፍራው ሰላማዊ ሰልፍ እንዲያካሂድ አይፈቀድለትም ብለዋል፡፡ ሰላማዊ ሰልፉን በጃንሜዳ እንዲያካሂዱ ሃሳብ አቅርበንላቸዋል ይሉት አቶ ማርቆስ፤ “በዚህ ካልተስማሙ አማራጭ ቦታ እንዲያቀርቡ በደብዳቤ አሳውቀናቸዋል” ብለዋል፡፡ በመስቀል አደባባይ ሰላማዊ ሰልፍ እንደምናካሂድ ለመስተዳድሩ በደብዳቤ ያሳወቅነው ከ10 ቀን በፊት ነው የሚሉት ኢ/ር ይልቃል በበኩላቸው፤ መስተዳድሩ ቅሬታውን በ12 ሰዓት ውስጥ ካልገለፀ እንደተስማማ ስለሚቆጠር ፅሁፎችን አትመን ስናሰራጭ፣ በሚዲያ በይፋ ስናስተዋውቅ ቆይተናል፤ ስለዚህ በዚያው እንቀጥላለን ብለዋል፡፡

ጃንሜዳ በክረምቱ ዝናብ በሙጃና በጭቃ ስለተሸፈነ ለሰላማዊ ሰልፍ አያመችም ይላሉ፡፡ ቦታው ለተቃዋሚዎች አይፈቀድም ተብለናል የሚሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ለልማት ታጥሯል መባሉም ተቀባይነት እንደሌለው ሲናገሩ፤ ቦታው ከጥቂት ቀናት በኋላ የደመራ በዓል ይካሄድበታል፤ ክልከላው “እኛን ለማዳከም የታሰበ ስራ ቢሆንም ትግላችንን እንቀጥላለን” ብለዋል፡፡

የመስቀል በዓልን አከባበር በተመለከተ ጥያቄ ያቀረብንላቸው አቶ ማርቆስ፣ “የመስቀል በዓል ብሔራዊ እና ሃይማኖታዊ በዓል በመሆኑ፣ እኛ መፍቀድም መከልከልም አንችልም” ብለዋል፡፡ ኢህአዴግስ ሠልፍ በስፍራው ማካሄድ ይችላል ወይ ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ “ጉዳዩ የገዢ ፓርቲ ወይም የተቃዋሚ ፓርቲ የሚል አይደለም፤ ስፍራው በከፍተኛ በጀት በውጭ ኮንትራክተሮች እየለማ ስለሆነ፣ የትኛውም አካል ሰላማዊ ሰልፍ ማካሄድ አይችልም” ብለዋል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲም ጃንሜዳ አይመቸኝም የሚል ከሆነ አማራጭ ቦታ ያቅርብና አስተዳደሩ ተወያይቶ ይወሰናል በሚል ሃሳባችንን በደብዳቤ ገልፀናል ብለዋል - አቶ ማርቆስ፡፡

Read 15815 times