Saturday, 28 September 2013 10:49

በ “ሆቴልሾው ኢትዮጵያ” የንግድ ትርኢት ከ10ሺህ በላይ ጐብኚዎች ይጠበቃሉ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(0 votes)

በአገራችን እያደገ የመጣውን የእንግዳ አቀባበል (ሆስፒታሊቲ) ኢንዱስትሪ በባለሙያ የታገዘ ለማድረግ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው የተነገረለት “ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2013”፤ ከመስከረም 30 እስከ ጥቅምት 2 ቀን 2006 ዓ.ም አዳራሽ ሊካሄድ ነው፡፡ በሶስቱ ቀን የንግድ ትርኢት ከ10ሺህ በላይ ጐብኚዎች እንደሚጠበቁ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡

በንግድ ትርኢቱ ላይ ከ65 በላይ በሆቴል፣ በአስጐብኚ፣ በሆቴል እቃ አቅርቦትና በዘርፉ ተያያዥነት ያላቸው ድርጅቶች እንደሚሳተፉ የአዘጋጁ የኦዚ ትሬዲንግ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ቁምነገር ተከተል ተናግረዋል፡፡ የንግድ ትርኢቱ ሆቴሎች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሆቴል ተጠቃሚ ከሆኑ ድርጅቶችና ተቋማት፣ ኤምባሲዎች፣ አስጐብኚ ድርጅቶች እና የዲፕሎማት ማህበረሰብ ጋር የገበያ ትስስር ለመፍጠር መልካም አጋጣሚ ይሆናል ተብሏል፡፡

ከንግድ ትርኢቱ ጐን ለጐን በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ስብሰባዎችና ውይይቶች የሚካሄዱ ሲሆን ስብሰባዎቹ በሆቴል ልማት፣ በሰው ሀብት አስተዳደርና በውድድሮች ዙሪያ ከአረብ ኤምሬትስ በመጡ ባለሙያዎች እንደሚካሄዱ ታውቋል፡፡ በአካባቢ ተቆርቋሪነት ዙሪያ ለሚካሄደው ውድድርም እስካሁን ከስምንት በላይ ሆቴሎች መመዝገባቸው ተጠቁሟል፡፡ በሌላ በኩል በሆስፒታሊቲ ዙሪያ አዲስ አስተሳሰብ ያመጡና ሀሳብ ያላቸው ወጣቶች ይሸለማሉ ተብሏል፡፡ የንግድ ትርኢቱ በአመት ሁለት ጊዜ የሚካሄድ ሲሆን በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪ መድረክ ለማድረግ መታቀዱን አቶ ቁምነገር ተናግረዋል።

የሆቴል ደረጃን በተመለከተም እስካሁን ያለውን የደረጃ አሰጣጥ ዘመናዊና አለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ለማድረግ፣ በተባበሩት መንግስታት የአለም የቱሪዝም ድርጅትና ከአለም ባንክ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ፣ አዲስ መስፈርት በማዘጋጀት፣ በአዲስ አበባና በክልል ባህልና ቱሪዝም፣ እስከ 600 ለሚሆኑ ሆቴሎች ከአንድ እስከ አምስት ኮከብ ደረጃ ይሰጣል ሲሉ የኢፌድሪ ባህልና ቱሪዝም ተወካይ አቶ ሲሳይ ተክሉ ተናግረዋል፡፡ የንግድ ትርኢቱ በነፃ የሚጐበኝ እንደሆነም ተገልጿል፡፡

Read 4617 times