Print this page
Saturday, 28 September 2013 10:51

በ10 ቀን ውስጥ የተገጣጠመው ህንፃ ዛሬ ለእይታ ይቀርባል

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(4 votes)

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ አርክቴክቸር ህንፃ ግንባታ እና ከተማ ልማት ኢንስቲትዩት ተማሪዎች፣ የጀርመኑ ዊመር ዩኒቨርስቲና በደቡብ ሱዳን ጁባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ትብብር በአስር ቀን ውስጥ የተገጣጠመ ባለ አንድ ፎቅ ህንፃ ዛሬ ለእይታ ይቀርባል፡፡ የህንፃው የመጀመሪያው ወለል የኮንክሪት ምሰሶና የብሎኬት ግድግዳ ያለው ሲሆን ሁለተኛው ወለል (ፎቁ) ከእንጨት እንደተሰራ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአርክቴክቸር፣ ህንፃ ግንባታና ከተማ ልማት ኢንስቲትዩት የዲዛይን ክፍል ዳይሬክተር አቶ ብሩክ ተ/ሀይማኖት ገልፀዋል፡፡ ከሶስቱ አገር ዩኒቨርስቲዎች በተውጣጡ 30 ተማሪዎች በ10 ቀን ውስጥ የተገጣጠመው ህንፃ፤ በልደታ ክ/ከተማ ባልቻ ሆስፒታል አካባቢ የሚገኝ ሲሆን ህንፃውን በዋናነት 20 ተማሪዎች እንደሰሩትና አስሩ ተማሪዎች በረዳትነት እንደተሳተፉበት የዲዛይን ክፍሉ ዳይሬክተር አብራርተዋል፡፡

የጁባና የጀርመኑ ዊመር ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለልምድ ልውውጥ ወደ ኢትዮጵያ መምጣታቸውን ገልፀው፤ ባለፈው አመት የኢትዮጵያ ተማሪዎች ጀርመን ዊመር ዩኒቨርሲቲ ሄደው የልምድ ልውውጥ ማድረጋቸውንና የጁባ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ለመጀመሪያ ጊዜ መምጣታቸውን ተናግረዋል፡፡ ዛሬ ረፋድ አምስት ሰዓት ላይ ለእይታ በሚቀርበው ባለ አንድ ፎቅ ህንፃ ምርቃት ላይ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት፣ አምባሳደሮችና የዩኒቨርስቲው ሀላፊዎች እንደሚገኙ ተጠቁሟል። እንደ አቶ ብሩክ ገለፃ፤ አንድን ህንፃ በአጠቃላይ ለመገጣጠም በአማካይ 14 ቀን የሚወስድ ሲሆን የመገጣጠሚያ ቁሳቁስ ተዘጋጅቶ ካለቀ ለመገጣጠም ብቻ ዘጠኝ ቀናት በቂ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

Read 6414 times