Saturday, 12 October 2013 12:21

ቴዲ አፍሮ ለዓለም ዋንጫ ዘፈን እንዲያቀርብ ተመረጠ

Written by  ማህሌት ፋሲል
Rate this item
(27 votes)

ታዋቂው የአገራችን ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) በብራዚል ለሚካሄደው የአለም ዋንጫ ዘፈን እንዲያቀርብ፣ በውድድሩ ዋና ስፖንሰር በኮካኮላ ኩባንያ ተመረጠ፡፡
እ.ኤ.አ በ2014 ለሚካሄደው የአለም እግር ኳስ ጨዋታ ከሚከናወኑ ዝግጅቶች መካከል ውድድሩን የሚያደምቁ ሙዚቀኞችን መምረጥ ከፍተኛ ትኩረት እንደሚሰጠው ምንጮቻችን የገለፁ ሲሆን፤ ቴዲ አፍሮ መመረጡ ለዘፋኙና ለአገሪቷ ትልቅ ትርጉም አለው ብለዋል፡፡
ቴዲ አፍሮ ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን አፍሪካንም የሚወክል ይሆናል ተብሎ እንደሚገመት የገለፁልን እነዚሁ የመረጃ ምንጮች፤ የሙዚቃው ሙሉ ቀረፃ የሚከናወነው በኬንያ እንደሆነ ተናግረዋል። የሙዚቃ ስራው መቼ በይፋ ለሕዝብ ጆሮ እንደሚደርስ በእርግጠኛነት አልታወቀም፡፡ በቅርቡ ዝርዝር መግለጫ ይሰራጫል ተብሎ እንደሚጠበቅ ምንጮቹ ጠቅሰዋል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ባስተናገደችው የ2010 የአለም ዋንጫ ዝግጅት ሶማሌያዊው ድምፃዊ ወጣት ኬናን በኮካኮላ ተመርጦ የሙዚቃ ስራውን እንዳቀረበ የሚታወስ ሲሆን፤ በአለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ እውቅናን እንዳተረፈ ይታወቃል፡፡

Read 8597 times