Saturday, 19 October 2013 11:12

በኤርትራ የስደተኞች ካምፕ ረብሻ ተቀሰቀሰ የአንድ ሰው ህይወት አልፏል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

          ትግራይ ክልል የማይአይኒ በተባለ ስፍራ የሚገኝ የኤርትራ ስደተኞች ካምፕ ውስጥ በተቀሰቀሰ ረብሻ የአንድ ሠው ህይወት ከጠፋ በኋላ፣ ተጠያቂ ናቸው የተባሉ ሰዎች እንደታሰሩ ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ ስደተኞች የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን በመቃወም ቢሮዎች የሰባበሩ ሲሆን፣ ወደ ጎንደር የሚወስደውም መንገድ ተዘግቶ ነበር፡፡
የረብሻው ምንጭ፣ ከሊቢያ ወደ ጣሊያን ሲጓዙ ለሞቱ በርካታ ኤርትራውያን የተዘጋጀ የመታሰቢያ ስነ ስርዓት እንደሆነ ምንጮቻችን ጠቅሰው ሻማ በማብራት የተጀመረው የመታሰቢያ ምሽት ወደ ተቃውሞ ረብሻ መቀየሩን አስታውሰዋል፡፡ በካምፑ ውስጥ የተፈጠረው ረብሻ ከቁጥጥር ውጭ ሆኗል በሚል ውሳኔ የፀጥታ ሀይሎች ጣልቃ እንደገቡ ምንጮቹ ጠቅሰው፤ በረብሻውና በግጭቱ የአንድ ሰው ህይወት እንደጠፋ ተናግረዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) የህዝብ ግንኙነት ተወካይ አቶ ክሱት ገብረእግዚአብሔር፤ በሜዲትራኒያን ባህር ላምፑዱስ የተባለ ደሴት አቅራቢያ ህይወታቸውን ላጡ ወገኖች የሻማ ማብራት ስነ ስርአት እናደርጋለን በሚል የተጀመረው ፕሮግራም ለምን ወደ አመፅ እንዳመራ አናውቅም ብለዋል፡፡ ስደተኞቹ ወደ ጎንደር የሚወስደውን መንገድ እንደዘጉ አቶ ክሱት ጠቅሰው፣ የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን እና አብረውን የሚሠሩ የሌሎች መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ላይ ተቃውሞ ተቀስቅሶ የቢሮ መስኮቶችና በሮች ተሠባብረዋል ብለዋል፡፡ ካምፕ ውስጥ የነበሩና አማራጭ ያጡ ወገኖች በሊቢያ በኩል ወደ ጣሊያን ለመግባት ሲሞክሩ ሞተዋል የሚል ሃሳብ በስደተኞች በኩል እንደተሰነዘረ አቶ ክሱት ጠቁመዋል፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን፣ በህጋዊ መንገድ ስደተኞችን ቢያጓጉዝ ኖሮ የበርካቶች ህይወት አይጠፋም ነበር በማለት በኮሚሽኑ ቢሮዎች ላይ ጥቃት እንደተፈፀሙ ሰምተናል ብለዋል-አቶ ክሱት፡፡ ስደተኞች ወደተለያዩ አገራት የሚጓጓዙት በኮሚሽኑ ፍላጎት ሳይሆን በተቀባይ አገራት በጎ ፈቃድ ነው ያሉት አቶ ክሱት፤ ኮሚሽኑ ለስደተኞች እንግልት ተጠያቂ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡

Read 3275 times