Saturday, 30 November 2013 10:44

የ“ሎሚ” መፅሄት ዋና አዘጋጅ ክስ ቀረበበት

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(7 votes)

          በትግራይ ክልል ፖሊስ ክስ የቀረበበት የ“ሎሚ” መፅሄት ዋና አዘጋጅ ሰናይ አባተ የክሱ መነሻ በግንቦት ወር 2005 ዓ.ም “የትግራይ እስር ቤትና ጓንታናሞ” በሚል ርዕስ የታተመ የአቶ አስገደ ገብረስላሴ ፅሁፍ እንደሆነ ገለፀ። በትግራይ ክልል ሁለት ልጆቻቸው መታሰራቸውን በመጥቀስ አቶ አስገደ ባቀረቡት ጽሑፍ፣ እስር ቤቱ በተራራ የተከበበ አስጨናቂ ሸለቆ በማተት አሸባሪዎች ከሚታሰሩበት፣ ከጓንታናም ጋር አመሳስለውታል፡፡ የትግራይ ፖሊስ በበኩሉ፣ የአቶ አሰገደ ጽሑፍ የእስረኞች አያያዛችንን ለማጠልሸት እና የፖሊስን ተአማኒነት ጥርጣሬ ላይ ለመጣል ያለመ ነው ሲል ክስ ማቅረቡን የሎሚ መጽሔት ዋና አዘጋጅ ተናግሯል፡፡ ሐሙስ ረፋድ ላይ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ተገኝቶ ቃሉን የሰጠው ዋና አዘጋጁ፤ “ፅሁፉ በሎሚ መፅሄት ከመታተሙ በፊት በኢትዮ ምህዳር ጋዜጣም ላይ ተስተናግዷል” ብሏል፡፡ ታተመ የመጣ ጽሑፍ በህግ ሊያስጠይቅ የሚችለው ከስድስት ወር ላልበለጠ ጊዜ እንደሆነ በመገናኛ ብዙሃን አዋጅ ላይ የተገለፀ ሲሆን፤ ፅሁፉ ከተስተናገደ ከሰባት ወራት በኋላ ክስ የቀረበበት ምክንያት አልገባኝም ብሏል - ሲሳይ አባተ፡፡ “አቶ አሰገደ ትግራይ ውስጥ እየበጠበጠ ያለ ሰው ነው፤ ፅሁፉን እንዴት አግኝታችሁ አስተናገዳችሁ” በሚል በመርማሪዎች ጥያቄ እንደቀረበበት የገለፀው ዋና አዘጋጁ ሲሳይ አባተ፤ በተለያዩ ጋዜጦችና መፅሄቶች ላይ በመፃፍ የሚታወቁት አቶ አሰገደ ፅሁፉን ልከውልን እንዳስተናገድን ተናግሬያለሁ ብሏል፡፡

Read 3904 times