Saturday, 30 November 2013 10:55

“ዜጐች የተሰደዱት መንግስት የሥራ ዕድል ባለመፍጠሩ ነው”

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(12 votes)

መንግስት ከሣውዲ የሚመለሱ ዜጐች ቁጥር አስቀድሞ ከተገመተው በላይ መሆኑን ገልጿል። ቀድሞ የተመላሾቹ ቁጥር  

28 ሺህ እንደሚሆን ቢገመትም አሁን ወደ 80ሺህ እንደሚደርስ ተነግሯል፡፡ በስደተኞቹ ላይ እየደረሰ ያለውን እንግልት

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም፤ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ከማውገዝ አልተቆጠቡም፡፡ ጉዳዩ በሰከነና

የዲፕሎማሲ መርሁ በሚፈቅደው መንገድ መያዙንም ገልፀዋል፡፡ መንግስት ከዚህ በላይ በዲፕሎማሲው ርቆ ሊሄድባቸው

የሚችልበት አማራጮች  እንደሌሉ የሠሞኑ መግለጫዎቹ ያመለክታሉ፡፡ ይሁን እንጂ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ

ሣይንስ ምሁሩ ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ መንግስት የዜጐቹን መብት በማስከበርም ሆነ የሃገርን ክብር በማስጠበቅ ረገድ ምንም

አልተራመደም ይላሉ - ተመላሾቹን ከመቀበል የዘለለ ዲፕሎማሲያዊ እርምጃዎች መውሰድ አለመቻሉን በመግለፅ፡፡ ዶ/ር

መረራ ጉዲና በጉዳዩ ዙሪያ የሰጡንን አጭር ማብራሪያ እነሆ:-


በሣውዲ አረቢያ በዜጐቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን በደል ተከትሎ መንግስት ጉዳዩን የያዘበትን መንገድ እንዴት

ገመገሙት?
ሁለት ሶስት ነገሮች አሉ፡፡ አንደኛው አሜሪካ፣ ጀርመን፣ ስዊድን በመሳሰሉት ሃገሮች ያሉ ኢትዮጵያውያን በሣውዲ

አረቢያ ላይ ተቃውሞ ሲያሰሙ እየፈቀዱላቸው፣ እዚህ መከልከሉ በዜጐች ላይ ተጨማሪ ወንጀል መስራት ነው፡፡

ሁለተኛው በተለያየ መንገድ እየሰማን እንዳለው አሁንም ቢሆን በ40ሺህ የሚቆጠሩ ዜጐች እየተንገላቱ ነው፡፡ እሪታና

የይድረሱልን ጥሪ እያሰሙ ነው። የኢትዮጵያ መንግስት ደግሞ የሚያወራው ሌላ ነው፡፡ መደብኩ እንኳን ያለው 50

ሚሊየን ብር አንድ እነሱ “የመንግስት ሌባ” የሚሉት የሚሠርቀው እኮ ነው። 50 ሚሊየን ብር ለ70ሺህ ሰው ነው

የመደቡት። ነገር ግን በሙስና የተከሰሱት ሰዎቻቸው እኮ የዚያን ሶስት እጥፍ ሰርቀዋል ተብሏል፡፡ በእውነቱ የተመደበው

ገንዘብ በጣም ትንሽ ነው፡፡ ሌላው ደጋግመው የሚያሰሙት፤ የሣውዲ አረቢያ መንግስትን ድርጊት የሚኮንን ሳይሆን

ወዳጅነት እንዳይበላሽ ትልቅ ስጋት ያላቸው የሚያስመስላቸው ነው፡፡ ከዜጐች ድብደባ፣ ግድያና እንግልት ይልቅ

የሣውዲ መንግስት ፍቅር የያዛቸው ነው የሚመስለው፡፡ ስለዚህ በሚፈለገው መንገድ ለጉዳዩ ምላሽ እየሰጡ አይደለም

የሚል መደምደሚያ ላይ መድረስ ይቻላል፡፡ ድሮውንም ቢሆን እነዚህ ዜጐች የተሰደዱት የኢትዮጵያ መንግስት የስራ

እድል መፍጠር ባለመቻሉ ነው፡፡ ሃገሪቷን የስደት ሃገር ያደረገው ራሱ መንግስት ነው፡፡
በሃላፊነትም ያስጠይቀዋል፡፡ ስለዚህ መንግስት በቀን ይሄን ያህል ሰው መለስኩ ከሚል፣ በመሠረታዊነት ዜጐች

የማይሰደዱባት ሃገር መፍጠር አለበት፡፡ የስራ እድል ሊኖርና የሰብአዊ መብት ሊከበር ይገባል፡፡
መንግስት በዜጐቹ ላይ ለተፈፀመው ግፍ፣ በአለማቀፍ ፖለቲካዊ ዲፕሎማሲው ምን ድረስ ነው ሊሟገት የሚችለው?
መንግስት እኮ ደጋግሞ የሚነግረን በህገወጥ መንገድ ከሃገር የወጡ ናቸው እያለ ነው፡፡ እንኳን በዚህ ዘመን ቀርቶ በጥንት

ዘመንም ስደተኞች ክብር አላቸው፡፡ ዝም ብሎ ይገደሉ፣ ይፈለጡ፣ ይቆረጡ አይባልም፡፡ ስለዚህ ሣውዲ አረቢያ ኋላቀር

በሆነ መንገድ ዜጐቻችንን ስታንገላታ በህግ መክሰስም ይቻላል፡፡ ሌላ አማራጭ ከተፈለገም እንደወዳጅ መንግስትና

የንግድ ሸሪክ ብዙ ተጽእኖ ማድረግ ይቻላል፡፡ ይልቁንስ የኢትዮጵያ መንግስት እያየ ያለው፣ እዚህ ያሉ ተቃዋሚዎች ምን

አሉ የሚለውን ብቻ ነው፡፡ ተቃዋሚዎች ከሰሱን፣ አጣጣሉን የሚለው ላይ ነው ያተኮረው፡፡
ከዚያም ሲያልፍ ሌት ተቀን እንደ መጽሐፍ ቅዱስ የሚነግረን ዜጐቹ በህገወጥ መንገድ መሄዳቸውን ነው፡፡ ዋናው ጉዳይ

መጀመሪያ የዜጐችን ነፍስ ማዳን ነው፤ ሌላው ደግሞ ለስደት የዳረገንን የኢኮኖሚ ችግር በመፍታት፣ ኢትዮጵያን ከስደት

ሀገርነት ዝርዝር ለማውጣት መንቀሳቀስ አለበት፡፡ ግን አሁን ባለው ሁኔታ የዚህ አዝማሚያ እምብዛም እየታየ አይደለም፡፡
መንግስት በሣውዲ አረቢያ ላይ ይከተል የነበረውን የዲፕሎማሲ አቅጣጫ ለመፈተሽና ለመቀየር የእነዚህ ዜጐች እንግልት

ምክንያት ሊሆን ይችላል ብለው ያስባሉ?
አሁን እኮ መንግስት ጠንከር ያለ መግለጫ እንኳ አላወጣም፡፡ በመኮነን ደረጃ እንኳ ደፍሮ መግለጫ ማውጣት

አልቻለም፡፡ ሌሎች ሀገሮች እኮ ቢያንስ በዜጐቻቸው ላይ በደል ሲፈፀም በመንግስት ደረጃ የመረረ ጩኸት ያሰማሉ፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት ግን ከህዝቡ ጋር አብሮ ሊጮህ ቀርቶ፣ የህዝቡንም ድምጽ እያፈነ ነው፡፡ ለዚህ ነው በተለይ

በፖለቲካ ዲፕሎማሲው በኩል እየተወሰደ ያለው እርምጃ በቂ አይደለም የምለው፡፡
መንግስት ዜጐቹን ከሃገሪቱ ከማስወጣት ባለፈ እርምጃ ያልወሰደው የኢኮኖሚ ጥገኝነት ጉዳይ ስላለ ነው፤ የኢትዮጵያ

ዋነኛዋ የውጪ ንግድ ሸሪክ ሣውዲ በመሆኗ ነው የሚሉ አስተያየቶችንስ እንዴት ያዩዋቸዋል?
በእርግጥ የኢኮኖሚ ጥገኝነቱ አለ፡፡ እናውቃለን። ታላላቅ የሣውዲ አረቢያ ከበርቴዎች በዚህች አገር ኢንቨስት ያደርጋሉ፡፡

ነገር ግን ለኢኮኖሚ ሲባል የዜጐችን መብትና ብሔራዊ ጥቅምን አሣልፎ መስጠት በየትኛውም የፖለቲካ አማራጭ ፈጽሞ

አይመከርም፡፡ ከምንም በላይ የዜጐች መብትና የሃገር ክብር ይቀድማል፡፡ በመቶ ሺህ የሚቆጠር ሰው እየተንገላታ

ለኢኮኖሚ ጥገኝነቱ ሲባል ዝምታን መምረጥ እንዲሁም የዜጐችን ጩኸት ወደማፈኑ መሄድ ተገቢ አይደለም፡፡
አንድ መንግስት በሌላ ሀገር የሚኖሩ ዜጐቹን መብት ለማስከበር ከአለማቀፍ ህግና ፖለቲካ ተመክሮ አንፃር ምን ያህል

ርቀት ነው ሊጓዝ የሚችለው?
ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን ጨርሶ እስከማቋረጥ ይደርሳል፡፡ ከዲፕሎማሲ ግንኙነት ማቋረጥ ባለፈም ችግሩን ለአለማቀፉ

ህብረተሰብ በጩኸት ማሰማትም ይገባል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ግን አፉን ሞልቶ ‘በዜጐቻችን ላይ እየተሰራ ያለውን

ግፍ እንኮንናለን’ ለማለት እንኳ እየጨነቀው ነው፡፡ እዚህ ያለውን ኤምባሲ እንኳ ሲያነጋግሩ፣ ዋናውን አምባሳደር

አይደለም፡፡ በሰለጠኑትን ሃገሮች ደረጃ ቢሆን በ30ሺህ፣ 60ሺህ የሚቆጠሩ ዜጐች እንዲህ ያለ እንግልት ሲደርስባቸው

ቀላል ጉዳይ አድርገው አይመለከቱትም፡፡ የህንድ፣ የፊሊፒንስ እና የሌሎች ሃገሮች ዜጐች ከኢትዮጵያውያኑ በተለየ

ክብራቸው ተጠብቆ ነው ከሃገር የወጡት፡፡ ይሄ ለምን ሆነ ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡
የስደተኞቹ ስቃይ ለፖለቲካ መጠቀሚያነት እንዳይውል መንግስት ጠይቋል፡፡ በእርግጥ ለፖለቲካ መጠቀሚያነት ውሏል?
የኢትዮጵያ ዜጐች በያሉበት ብሶት እያሰሙ ነው። በተለያዩ መንገዶች በየሃገራቱ በኢትዮጵያውያኑ ላይ የሚፈፀሙት

በደሎች ሲሰሙ ይዘገንናሉ፡፡ እኛ እኮ እየጠየቅን ያለነው የእነዚህ ኢትዮጵያውያንን መብት ነው፡፡ ነገር ግን መንግስት

ጉዳዩን በሌላ እየተረጐመው እኮ ነው የተቸገረው፡፡ 

Read 5161 times