Saturday, 07 December 2013 11:24

534 አባወራ የልማት ተነሺዎች አቤቱታቸውን ለከንቲባው ፅ/ቤት አቀረቡ

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(2 votes)

ከቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 አስተዳደር ልዩ ቦታው ስፖርት ኮሚሽን እየተባለ በሚጠራ አካባቢ የሚኖሩ 534 አባወራዎች ሥፍራው የብሔራዊ ስታዲየም ግንባታ የሚካሄድበት በመሆኑ ቤታቸውን በሰባት ቀናት ውስጥ ለቀው እንዲወጡ የተሰጠውን ውሣኔ በመቃወም አቤቱታቸውን ለከንቲባው ፅ/ቤት ማቅረባቸውን ገለፁ፡፡ የክፍለ ከተማው አስተዳደር የወረዳ 3 ፅ/ቤት ለእነዚሁ ነዋሪዎች የሰጠው ደብዳቤ፤ ሥፍራው ለብሔራዊ ስቴዲየም ግንባታ የተመረጠ እንደሆነና ነዋሪዎቹ ሥፍራውን ያለ አግባብ ወሮ በመያዝ የልማት ሥራው እንዲዘገይ ማድረጋቸውን ጠቅሶ፤ በሰባት ቀናት ውስጥ ንብረታቸውን በማንሣት የልማቱ ተባባሪ እንዲሆኑ ይጠይቃል፡፡ የአስተዳደር ፅ/ቤቱ ስለ ጉዳዩ ከ6 ወራት ጀምሮ ለነዋሪዎቹ ማሳወቁንም በደብዳቤው ላይ ጠቁሟል፡፡ 534 አባወራ ነዋሪዎቹ ለከንቲባው ፅ/ቤት ባቀረቡት የቅሬታ አቤቱታ ላይ እንደገለፁት፤ ቀደም ሲል የክፍለ ከተማው ምክትል ሥራ አስፈፃሚና የመሬት ልማት ባንክ ፅ/ቤት ኃላፊ፣ የአካባቢውን ህዝብ ሰብስበው እስከ አዲሱ ሊዝ ስሪት አዋጅ ድረስ የተያዙ ይዞታዎች በሙሉ በሰነድ አልባ ፕሮግራም በየደረጃ የሚስተናገዱ መሆኑን እንደነገሯቸው ጠቅሰው፤ አሁን በድንገት በሰባት ቀናት ውስጥ ቤታቸውን እንዲለቁ መጠየቁ አግባብነት የለውም ብለዋል፡፡ ነዋሪዎቹ በአብዛኛው በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ አቅመ ደካሞችና አካል ጉዳተኞች እንደሆኑ የገለፁት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ለአመታት የኖርንበትን ቤት በሰባት ቀናት ውስጥ ለቀን ህፃናት ልጆቻችን ይዘን የምንሄድበት አቅም የለንም ብለዋል፡፡ የአገሪቱን የልማት እንቅስቃሴዎች እንደግፋለን የሚሉት ነዋሪዎቹ፤ ሆኖም እኛም ዜጐች እንደመሆናችን መጠን መንግስት ለልማት ተነሺዎች በሚያመቻቸው ዕድል ተጠቃሚዎች ልንሆን ይገባል ብለዋል፡፡ ነዋሪዎቹ ለከንቲባው ፅ/ቤት ያቀረቡት አቤቱታ ምላሽ ከማግኘቱ በፊት ከቤታቸው እንዳይፈናቀሉም ተማፅነዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ መሬት አስተዳደር ለልማት ተነሺ የሆኑ ዜጐችን ባላቸው መረጃ መሰረት እያስተናገደ እንደሚገኝና እስከ 1997 ዓ.ም ድረስ ያሉ ይዞታዎች ህጋዊ ሠነድ እንዲያገኙ በማድረግ፣ ተተኪ ቦታና ካሳ እየከፈለ ሲሆን የ2003 ካርታ በመመሪያው እንዳልተካተተና እነዚህ ዜጐችም መመሪያው የማይደግፋቸው ከሆነ ለማስተናገድ እንደማይቻል የመሬት አስተዳደር ቢሮው አመልክቷል፡፡ ከንቲባው ለአቤቱታቸው የሚሰጡትን ውሣኔ እየተጠባበቁ እንደሆነም ነዋሪዎቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል።

Read 1615 times