Saturday, 07 December 2013 11:27

ለጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ሊዘጋጀ ነው

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(0 votes)

ከአንድ ወር በፊት በሀዋሳ ከተማ የመኪና አደጋ ደርሶበት በኮሪያ ሆስፒታል እየታከመ ላለው ጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነ፣ የገንዘብ ማሰባሰቢያ የእራት ፕሮግራም እንደሚዘጋጅ የእርዳታ አሰባሳቢ ኮሚቴው ሰብሳቢ ጋዜጠኛ አያሌው አስረስ ገለፁ፡፡ የእራት ምሽቱ የሚዘጋጀው አትላስ ሆቴል አካባቢ በሚገኘው “ኦካናዳ” ባርና ሬስቶራንት ውስጥ ሲሆን፤ የሃሳቡ አመንጪዎች የሬስቶራንቱ ባለቤቶች እንደሆኑም ሰብሳቢው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ ታህሳስ 7 እና 8 ከ11 ሰዓት ጀምሮ የሚካሄደው የራት ምሽት መግቢያው 500 ብር ሲሆን የፋሽን ትርኢትና በዲጄ ሳሚ የሚዘጋጅ የሙዚቃ ግብዣንም ያካትታል ተብሏል፡፡

“ጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነን ከጉዳቱ ለመታደግ ፈቃደኛ ግለሰቦች ድጋፍ ቢያደርጉም ወጭውና የሚሰበሰበው ገንዘብ ሊመጣጠን አልቻለም” ያሉት የኮሚቴው ሰብሳቢ፤ በዚህ ምክንያት ተጨማሪ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራሞችን ማዘጋጀት እንዳስፈለገ ገልፀዋል፡፡ በእራት ምሽቱ ከ250 በላይ ሰዎች እንደሚጠበቁና ከ80ሺህ ብር በላይ ለመሰብሰብ እንደታቀደ ሰብሳቢው ተናግረዋል፡፡ የ“ኦ ካናዳ” ባርና ሬስቶራንት ባለቤት ወ/ሮ ሊሊ ካሳሁን በበኩላቸው፤ ከእርዳታ አሰባሳቢ ኮሚቴው ጋር በመተባበር ልዩ የእራት ምሽቱን እያዘጋጁ እንደሆነ ገልፀው፤ ህብረተሰቡ የመጀመሪያዎቹን ትኬቶች በመግዛት ለጋዜጠኛው ወገንተኛነታቸውን እንዲገልፁ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡ የኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ አያሌው አስረስ በበኩላቸው ሃሳቡን በማፍለቅና ተነሳሽነት በማሳየት የእራት ምሽቱን ለማዘጋጀት የፈቀዱትን የ“ኦ ካናዳ” ባርና ሬስቶራንት ባለቤቶችን አድንቀው፣ የራት ምሽቱን ትኬቶች በሬስቶራንቱና ሌሎች ቦታዎች በመግዛት ህብረተሰቡ ትብብር እንዲያደርግ ጥሪ ካስተላለፉ በኋላ ኮሚቴው ሌሎች የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራሞችን ለማዘጋጀት ቅድመ ዝግጅቶችን ማጠናቀቁን ተናግረዋል፡፡” ጋዜጠኛ ኤፍሬም በየነ “የሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ የማኔጅመንት አባል በሙስና እጅ ከፍንጅ ተያዘ” በሚል ርዕስ በኢትዮ-ምህዳር ጋዜጣ ላይ ባወጣው ዘገባ የተነሳ ሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በጋዜጣውና በአዘጋጆቹ ላይ ክስ መመስረቱ የሚታወስ ሲሆን፤ ጋዜጠኛው ፍ/ቤቱ ለሚያነሳው ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ወደ ሀዋሳ በተጓዘበት ወቅት በደረሰበት የመኪና አደጋ በአከርካሪውና በሳንባው ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበት በኮሪያ ሆስፒታል እየታከመ ይገኛል፡፡

Read 1664 times