Print this page
Saturday, 07 December 2013 11:34

የብሪጅስቶን የጎማ ማዕከል ተመረቀ

Written by 
Rate this item
(6 votes)

በኢትዮጵያ የብሪጅስቶን ጎማ ብቸኛ አስመጪና አከፋፋይ ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር በ15 ሚሊዮን ብር ወጪ በአዲስ አበባ ቃሊቲ መናኸሪያ አካባቢ ያስገነባው ‘ብሪጅስቶን ትራክ ታየር ሴንተር’ (BTTC) የተሰኘ አዲስ የጎማ ጥገና ማዕከል ትናንት ተመርቆ ተከፈተ፡፡ ላለፉት አስራ ሶስት አመታት ጥራታቸውን የጠበቁ የብሪጅስቶን ጎማዎችን በማስመጣት የሚታወቀው ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር፤ በአገሪቱ የትራንስፖርት ዘርፍ ውስጥ የራሱን ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንዳለ ይታወቃል፡፡ አገራት በሚጠቀሙበት ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ዘርፈ ብዙ የተሽከርካሪ ጎማ ጥገናና ተያያዥ አገልግሎት ለመስጠት በማሰብ ማዕከሉን እንደገነባ የብሪጅስቶን ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሁሴን አህመድ በምረቃ ሥነሥርዓቱ ላይ ተናግረዋል፡፡

ደንበኞች የተለያዩ አገልግሎቶችን በምቹ ሁኔታ በሚያገኙበት መልኩ በ6 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የተገነባውና በዘመናዊ ቁሳቁስ የተደራጀው ማዕከሉ፣ ከፍተኛ የጥራት ደረጃ ያላቸውን የጎማ ምርቶች ከማቅረቡ በተጨማሪ፣ የካበተ ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች አማካይነት ሰባት አይነት የተለያዩ የተሽከርካሪ ጎማ ጥገናና ተያያዥ አገልግሎቶችን እንደሚሰጥም ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉ ከዚህ በተጨማሪም፤ ከጎማ አጠቃቀም፣ ከአጠቃላይ የተሽከርካሪዎች ደህንነት አጠባበቅና ጥገና ጋር በተያያዘ ለአሽከርካሪዎችና ባለሃብቶች የተሟላ መረጃና ሙያዊ ምክር ይሰጥበታል ተብሏል። ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ በጥናት ላይ ተመስርቶ ባቋቋመው በዚህ ማዕከል ሊሰጣቸው ያቀዳቸው በቴክኖሎጂ የታገዙና የተሻሻሉ አገልግሎቶች፣ የተሽከርካሪዎችንና የጎማዎችን ዕድሜ ከማራዘም ባለፈ ለአዳዲስ ጎማዎች ግዢ፣ ለጥገናና ለእድሳት የሚወጣውን ወጪ በመቀነስ ረገድም የጎላ ሚና እንደሚጫወት በማዕከሉ ምረቃ ላይ ተነግሯል።

ከካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ ከአቶ ሰኢድ አል አሙዲ ጋር በመሆን ማዕከሉን መርቀው የከፈቱት የዕለቱ የክብር እንግዳና የብሪጅስቶን ኩባንያ የአፍሪካና የመካከለኛው ምስራቅ ፕሬዚዳንት ሚስተር ሳኩማ በበኩላቸው፤ የማዕከሉ መገንባት ለተሽከርካሪዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡ ኩባንያው ለወደፊትም ከካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ ጋር ያለውን የስራ ግንኙነት በማጠናከር፣ የተሻሻሉ አሰራሮችንና ጥራታቸውን የጠበቁ የጎማ ምርቶችን ለደንበኞች ማቅረቡን እንደሚቀጥልበትም ሚስተር ሳኩማ ገልጸዋል፡፡ ካቤ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ፣ ከብሪጅስቶን ጎማ አስመጪነት በተጨማሪ በቡና ኤክስፖርት፣ በሲኖትራክ ተሽከርካሪዎች አስመጪነትና በሳኡዲ ኤርላይንስ ብቸኛ ወኪልነት ሰፋፊ የንግድና ኢንቨስትመንት ስራዎችን በማከናወን ላይ የሚገኝ ድርጅት ነው፡፡

Read 2654 times
Administrator

Latest from Administrator