Saturday, 07 December 2013 11:45

ከንቲባ ድሪባ የእሳት ቃጠሎ ተጐጂዎችን አቤቱታ አጣራዋለሁ አሉ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(14 votes)

አንዳንድ የእሳት አደጋ ሰራተኞች ጉቦ እንድንሰጣቸው ሲደራደሩ ብዙ ንብረት ጠፍቷል - ተጐጂዎች ችግሩ በተነገረው መጠን አይደለም - እሳት አደጋ

             በመርካቶ የጅምላ መደብሮችና መጋዝኖች ላይ ረቡዕ ዕለት የተከሰተውን ቃጠሎ ለማጥፋት የተጠሩ የእሣት አደጋ መከላከያ ተቋም ሠራተኞች ጉቦ ጠይቀውናል በማለት ተጐጂዎቹ ለከተማዋ ከንቲባ አቤቱታ ያቀረቡ ሲሆን፣ ተቋሙ አቤቱታውን በማስተባበል ሦስት ሰራተኞች እንደቆሰሉበት ገለፀ፡፡ ለ5 ሰዓታት የዘለቀው ቃጠሎ፤ ከ40 በላይ መደብሮችና መጋዘኖች ላይ ከፍተኛ ጉዳት ከማድረሱም በተጨማሪ ከ30 በላይ ሰዎችም እንደተጐዱ ተገልጿል፡፡ የአዲስ አበባ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ በስፍራው ተገኝተው ተጐጂዎችን ያነጋገሩ ሲሆን፣ በእሣት አደጋ መከላከያ ተቋም ሠራተኞች ላይ አቤቱታ አሰምተዋል። የተቋሙ ሰራተኞች በቦታው ከደረሱ በኋላ፣ “እሳቱን ለማጥፋት ከበላይ አካል መመሪያ አልተላለፈልንም” በሚል ሰበብ “ቆመው ሲያዩ ነበር” በማለት ምሬታቸውን የገለፁ ተጎጂዎች፤ አንዳንድ የተቋሙ ሰራተኞች ደግሞ “ጉቦ እንድንሰጣቸው ሲደራደሩ ብዙ ንብረት ጠፍቷል” ብለዋል፡፡ መጋዘንና መደብር እንደወደመባቸው ለአዲስ አድማስ የገለፁ ነጋዴ፤ እሣት አደጋዎች የድረሱልን ጥሪው ከተላለፈላቸው በኋላ ዘግይተው ነው የመጡት፤ እዚህ ከደረሱ በኋላም መመሪያ አልተላለፈልንም በሚል ቆመው ይመለከቱ ነበር ብለዋል፡፡

ከዚህ ቀደም በአካባቢው ከ4 ጊዜ በላይ የእሣት አደጋ መድረሡንና የአሁኑ ቃጠሎ ከሁሉም የከፋ መሆኑን የተናገሩ ሌላ ነጋዴ በበኩላቸው፤ የአካባቢው ሰው እሳቱን ለማጥፋት ሲረባረብ የእሣት አደጋ ሠራተኞች ከበላይ ትእዛዝ እየጠበቅን ነው በማለት ቆመው መመልከታቸው እንዳሣዘናቸው ገልፀዋል፡፡ “ከዚህ ቀደም በፍጥነት እሳት ለማጥፋት ክሬን ይጠቀሙ ነበር፤ አሁን ለምን ክሬን እንዳልተጠቀሙ እንዲገለፅልን እንፈልጋለን” የሚሉት እኚሁ ቅሬታ አቅራቢ፤ የወገን ንብረት እየወደመ መመሪያ እንጠብቃለን ብሎ መቆም አሣዛኝ ነው ብለዋል፡፡ ከንቲባ ድሪባ ኩማ፤ የተጐጂዎቹን አቤቱታ ካዳመጡ በኋላ “መመሪያ አልተላለፈልንም ወይም ገንዘብ ክፈሉኝ” ብሎ ዳተኝነት ያሳየ ሰራተኛ ካለ፣ ራሴ የማጣራው ጉዳይ ነው፣ የአደጋው መንስኤም በቶሎ ተጣርቶ ይገለጻል” ብለዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው በአዲስ አበባ እሣትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከያ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሃላፊ አቶ ንጋቱ ማሞ በበኩላቸው፤ የአደጋውን የጥፋት መጠን በገንዘብ ለማስላት ለጊዜው ባይቻልም 40 የንግድ ሱቆች እና 5 መጋዘኖች ከነሙሉ ንብረታቸው መውደሙን ተናግረዋል፡፡

32 ሰዎች ቀላል ጉዳት እንደደሠረባቸውና ከነዚህ መካከል ሶስቱ የእሣት አደጋ ባለሙያዎች ሲሆኑ በጦር ሃይሎች ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው ነው ብለዋል-አቶ ንጋቱ፡፡ እሣቱን ለማጥፋት አስፈላጊው መስዋዕትነት ተከፍሏል ያሉት አቶ ንጋቱ፤ “ጉዳት የደረሠበት ሠው ቅሬታ ለምን አቀረብክ ባይባልም፤ ባለሙያዎቹ በቸልታ ይመለከቱ ነበር፣ በገንዘብ ይደራደሩ ነበር የሚለው አባባል ስሜታዊነት የተንፀባረቀበት ነው፤ ችግሩ በተነገረው መጠን አይደለም” ሲሉ ምላሽ ሠጥተዋል፡፡ በፍጥነት ባለሙያዎች አልደረሡም ለተባለውም በትራንስፖርት መጨናነቅ ምክንያት 10 ደቂቃ ያህል ብቻ መዘግየት ማጋጠሙን የተናገሩት አቶ ንጋቱ፤ ቦታው አመቺ ባለመሆኑ፣ ተቀጣጣይ ነገሮች በብዛት በመኖራቸው፣ በአቅራቢያው ውሃ ባለመኖሩ እና ስራውን ለባለሙያዎች ያለመተው ችግር ተደማምረው በሚፈለገው ፍጥነት እሣቱን መቆጣጠር አልተቻለም ብለዋል፡፡ እሣቱን ለማጥፋትም 10 የአደጋ መከላከያ መኪኖችና 7 አምቡላንሶችን በመጠቀም 585 ሺህ ሊትር ውሃ እና 144 የአደጋ ጊዜ ሠራተኞችን ድርጅታቸው መጠቀሙን የገለፁት ሃላፊው፤ ክሬን መምጣት ነበረበት ለተባለው ድርጅቱ ያሉት ክሬኖች ለዚህ ጉዳይ አገልግሎት መስጠት የሚችሉ አይደሉም ብለዋል፡፡

Read 3753 times