Sunday, 05 January 2014 00:00

“አንድነት” የፀረ-ሽብር አዋጁን ለማሠረዝ የሚያስችል ድምፅ ማግኘቱን ገለፀ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(9 votes)

የህዝብ ፊርማ ይዘን በፍ/ቤት ክስ እንመሰርታለን ብሏል
የፀረ-ሽብር አዋጁን በመቃወም “የሚሊዮኖች ድምፅ” በሚል መርሃግብር የህዝብ ፊርማ ሲያሠባስብ የቆየው አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ፤ ህጉን ለማሠረዝ የሚያስችል በቂ ድምፅ ማግኘቱን አስታወቀ፡፡ ከ1ሚ. በላይ ፊርማ አሰባስቤአለሁ ያለው ፓርቲው፤ የህዝቡን ፊርማ በመያዝ ክስ እንደሚመሰርት ገልጿል፡፡
ፓርቲው ለ3 ወራት ባካሄደው ፊርማ የማሰባሰብ ዘመቻ የፀረ ሽብር አዋጁን ለማሰረዝ የሚያስችል ድምጽ ማግኘቱን የገለፁት የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ዳንኤል ተፈራ፤ አሁንም ድረስ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በኦንላይን እየፈረሙ በመሆኑ አጠቃላይ የፈራሚዎቹን ቁጥር መግለጽ ቢያዳግትም፣ እስካሁን ከ1 ሚሊዮን በላይ ፊርማ መሰባሰቡን አረጋግጠናል ብለዋል፡፡ የተሰባሰበው የፊርማ ብዛት ፓርቲው ከገመተው በላይ ስኬት መቀዳጀቱን ይጠቁማል ያሉት ሃላፊው፤ በአጠቃላይ የተሰበሰበውን የፊርማ ብዛት ፓርቲያቸው በቅርቡ ይፋ እንደሚያደርግ ገልፀዋል።
“አንድነት” ፓርቲ በፀረ ሽብር ህጉ ላይ ያለው አቋም ሙሉ ለሙሉ ይሰረዝ የሚል እንደሆነ የጠቆሙት አቶ ዳንኤል፤ የተሰበሰበውን የህዝብ ፊርማ ለፍ/ቤት በማቅረብ፣ ህጉ ከህገመንግስቱ ጋር እንደሚጋጭና የዜጐችን መሠረታዊ መብት እንደሚጥስ በመጥቀስ ክስ እንመሠርታለን ብለዋል። ከፍ/ቤት ቀጥሎም ጉዳዩን ለፌደሬሽን ምክር ቤት እንደሚያቀርቡ የገለፁት ሃላፊው፤ ምንም እንኳ ከዚህ ቀደም በህዝብ ድምፅ ህግ የማሠረዝ እንቅስቃሴ ተሞክሮ ባያውቅም ፍ/ቤቶች እና  ምክር ቤቱ የፓርቲውንና የፈራሚውን ህዝብ ጥያቄ ተቀብለው ውሳኔ እንደሚሰጡ ተስፋ እናደርጋለን ብለዋል፡፡ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጐችን ድምፅ ዝም ብለን ሜዳ ላይ አንጥልም ያሉት አቶ ዳንኤል፤ የፍ/ቤቶች ገለልተኝነት አጠያያቂ ከመሆኑ አንፃር ጥያቄው ተቀባይነት ባያገኝ እንኳን ህዝቡ የተሣተፈበት የፓርቲው የትግል አካል ተደርጐ ለታሪክ ተመዝግቦ ይቀመጣል ብለዋል፡፡
ህጉ ይሠረዝ የሚል አቋማቸው በመንግስት በኩል “ለሽብርተኝነት ድጋፍ ከመስጠት አይለይም” የሚል ትችት ማስከተሉን ያነሳንባቸው አቶ ዳንኤል በሰጡት ምላሽ፤ “የወንጀለኛ ህጉ አልበቃ ብሎ የፀረ-ሽብር ህግ ራሱን ችሎ የሚያስፈልግ ከሆነም ከውጭ የተቀዳ ሣይሆን ከፍተኛ የህግ ባለሙያዎች የተሣተፉበት እንዲሁም ህብረተሠቡ በየደረጃው ውይይት ያደረገበትና የመላውን ህዝብ ይሁንታ ያገኘ ህግ ማውጣት ይቻላል” ሲሉ የፓርቲያቸውን አቋም አንፀባርቀዋል፡፡  ፓርቲያቸው በስራ ላይ ያለው የፀረ - ሽብር አዋጅ እንዲሠረዝ ጥብቅ አቋም የያዘበትን ምክንያት ሲያስረዱም፤ “ህጉ ከወጣ በኋላ በቀጥታ ፖለቲከኞችንና ጋዜጠኞችን ለማስፈራሪያና ለማጥቂያ በመዋሉ ነው” ብለዋል - ሃላፊው፡፡  
የፀረ - ሽብር ህጉን ለማሠረዝ የሚያስችል ድምጽ ማሠባሠብ መቻላችን አገሪቱ አቤቱታ ለማቅረብ ምቹ የዲሞክራሲ ቁመና ላይ መገኘቷን ፈፅሞ አያመለክትም ያሉት አቶ ዳንኤል፤ ፓርቲያቸው የፀረ-ሽብር አዋጁን በተመለከተ ህጋዊ መነሻ ይዞ ለመላ ኢትዮጵያውያን በይፋ የተቃውሞ ጥሪ ያቀረበ ቢሆንም ሠሞኑን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እየተላለፈ በሚገኘው ዘጋቢ ፊልም ላይ “አንድነት ፀረ-ሠላም ለማድረግ መሞከሩ ተገቢ አይደለም” ሲሉ ቅሬታቸውን ገልፀዋል፡፡ በ97 ምርጫ ትልቁ የኢህአዴግ አጀንዳ “ኢንተርሃሞይ” እንደነበር ያስታወሱት ሃላፊው፤ በ2002 ምርጫ “ተቃዋሚዎች አጀንዳ የላቸውም” ወደሚል ቅስቀሣ መቀየሩን ጠቁመው፤ ለቀጣዩ ዓመት ምርጫ ደግሞ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን “ፀረ-ሠላም ናቸው” የማለት እንቅስቃሴ  ከወዲሁ መጀመሩን ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል ፓርቲው፤ ከዚህ ቀደም ሠላማዊ ሠልፍ እንዳላደርግ እንቅፋት ሆነውብኛል ባላቸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና ፖሊስ ላይ ክሡን ለመመስረት በዝግጅት ላይ እንደሆነ አቶ ዳንኤል ተናግረዋል፡፡ በዛሬው እለት አዲስ በተመረጡት የፓርቲው ሊቀመንበር በኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው ይፋ የሚደረገው የፓርቲው ካቢኔ የመጀመሪያ ስራ፣ የፀረ - ሽብር አዋጁን ማሠረዝ እና ክስ የሚቀርብባቸው አካላት ላይ ክስ መመስረት እንደሚሆን ሃላፊው አክለው ገልፀዋል፡፡   

Read 3672 times