Monday, 27 January 2014 08:00

በ‹‹ልማታዊ ጋዜጠኝነት›› እና በ“ኢትዮ ሱዳን ድንበር” ላይ ውይይቶች ተዘጋጁ

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(14 votes)

አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ “በልማት ጋዜጠኝነት” ዙሪያ የፓርቲና የመንግስት ተወካዮች አቋማቸውን የሚገልፁበት ውይይት ለዛሬ ያዘጋጀ ሲሆን፤ ሰማያዊ ፓርቲ የኢትዮ ሱዳን ድንበር በተመለከተ ፕ/ር መስፍን ወልደማርያም ሃሳብ የሚያቀርቡበት ውይይት ያካሂዳል፡፡
‹‹ልማታዊ ጋዜጠኝነት›› በሚለው ርዕሰ ጉዳይ የተለያዩ ሃገሮችን ልምድ የሚያሳይና በኢትዮጵያ የሚኖረውን ቦታ የሚፈትሽ ውይይት በኢንተር ኮንቲኔንታል ሆቴል እንደሚካሄድ የገለፀው የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒዩኬሽን ትምህርት ክፍል፤ የፓርቲ እና የመንግስት ተወካዮች አቋማቸውን እንደሚያቀርቡ ጠቁሟል፡፡
“ልማታዊ ጋዜጠኝነት” ለድሃ አገራት የሚጠቅምና የሚስማማ ነው በማለት የሚደግፉ እንዳሉ ሁሉ፤ በተቃራኒው ጋዜጠኝነት የመንግስት ጥገኛና አፈቀላጤ እንዲሆን ያደርጋል በማለት የሚተቹ መኖራቸው ይታወቃል፡፡
በሌላ በኩል የኢትዮ-ሱዳን ድንበርን በተመለከተ ዛሬ በዘጠኝ ሰዓት በጽ/ቤቱ ውይይት የሚያዘጋጀው ሰማያዊ ፓርቲ፤ ፕ/ር መስፍን ወልደማርያም በጉዳዩ ላይ ከፍተኛ ልምድ እንዳላቸውና ሃሳባቸውን እንደሚያቀርቡ ገልጿል፡፡ መንግስት፣ ከሁመራ እስከ ቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ድረስ ባለፉት ሁለት ወራት ድንበር እያካለለ መሆኑን በሱዳን የመገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች እንደተሰራጨ የገለፀው የፓርቲው የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ ዮናታን ተስፋዬ፤ መንግስት ጉዳዩን ደብቆ ይዟል ብሏል፡፡
መንግስት በድንበር ጉዳይ የሚሰነዘሩ ትችቶች መሰረት የለሽ ናቸው ብሎ ማስተባበሉ ይታወሳል።

Read 3530 times