Monday, 03 February 2014 13:47

አልበሽር ከተቃዋሚዎች ጋር ለመሥራት እፈልጋለሁ አሉ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

             የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር ሀሰን አልበሽር ባለፈው ሰኞ በቀጥታ የአገሪቱ ቴሌቪዥን የተሰራጨ ንግግር አድርገዋል፡፡ የአልበሽር ንግግር በሶስት ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሲሆን ለመጀመርያ ጊዜ  የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካዮችን ያካተተ ነበር። በቻይና መንግስት ትብብር በተሰራው የብሉ ናይል የመሰብሰቢያ አዳራሽ ከተሳተፉት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች መካከል አልበሽር ወደ ስልጣን የመጡበትን የ1989ኙን መፈንቅለ- መንግስት በማቀነባበር ወሳኝ ሚና የተጫወቱትና በ2000 ዓ.ም ከገዢው ፓርቲ የ“ናሽናል ኮንግረስ ፓርቲ” ተገንጥለው “ኦፖዚሽን ፖፑላር ኮንግረስ” ፓርቲን ያቋቋሙት ሀሰን አልቱራቢ፣ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የአልበሽር አማካሪ የነበሩትና ታህሳስ ላይ የ“ለውጥ ፓርቲ”ን የመሰረቱት ጋዚ ሳላሀዲን አትባኒ እና የ“ኡማ ፓርቲ” መሪ  ሳዲቅ አልመሃዲ ይገኙበታል፡፡
አልበሽር በንግግራቸው ላይ ሶስት የለውጥ ፕሮግራሞች ያሏቸውን ነጥቦች ይፋ አድርገዋል። የመጀመሪያው ፕሮግራም ከተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በሚደረግ ተከታታይ ውይይት አሁን በስራ ላይ ባለው የአገሪቱ ህገመንግስት እና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ በመምከር፣ ህገመንግስቱ የገዥው ፓርቲ ሰነድ ብቻ ሆኖ እንዳይቀር፣ ሁሉንም ሀይሎች ያሳተፈ ህገመንግስት ማርቀቅን ያካትታል።  ሁለተኛው ፕሮግራማቸው በአገሪቱ ውስጥ ፀጥታ እና መረጋጋትን  በማምጣት፤ሱዳንን ከአማፂያን ሽኩቻ ነፃ ማድረግ እንደሆነ የገለፁት አልበሽር፤ለዚህ ደግሞ የአቡጃ፣ የዶሃ፣ የስርት እና ሁሉን አቀፉን የሰላም ስምምነት ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ ሶስተኛው ፕሮግራም የአገሪቱ ኢኮኖሚ እንዳይንኮታኮት እርምጃ መውሰድን የሚመለከት ሲሆን ለዚህም የኢኮኖሚ ማሻሻያ እንደሚደረግ አልበሽር ገልፀዋል፡፡ “ደቡብ ሱዳን ነፃነቷን ካወጀች በኋላ ነዳጅ መደጎማችንን እንድናቆም  በኢኮኖሚ ባለሙያዎች ስንመከር ተግባራዊ አለማድረጋችን ስህተት ነበር፡፡ በአለም ላይ የነዳጅ ዋጋ እያሻቀበ ቢመጣም  ህዝባችን ላይ ጫና እንዲፈጠር ስላልፈለግን ተግባራዊ ሳናደርገው ቀርተናል፡፡ አዲሱ የኢኮኖሚ ፓኬጅ ድሆችን አይጎዳም፤ምክንያቱም ድሆች መኪና የላቸውም፡፡ እነሱን በዘካት ቻምበር እና በደሞዝ ጭማሪ እንዳይጎዱ ማድረግ ይቻላል” ብለዋል፡፡
ሁሉም ሱዳናውያን የተሃድሶው ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ ያቀረቡት አልበሽር፤ሰላም ቅድሚያ የሚሰጠው አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል - ያለ ሰላም ፖለቲካዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ እድገት እንደሌለ በመጥቀስ፡፡ አልበሽር ይሄን ይበሉ እንጂ የተኩስ አቁም ስምምነትን በተመለከተ ትንፍሽ ያሉት ነገር የለም ተብሏል፡፡ “በሱዳን ውጤት የሌለው የፖለቲካ ሽኩቻ ማብቃት አለበት” በማለት ብቻ  ነው ጉዳዩን አድበስብሰው ያለፉት፡፡
  የአልበሽር የሰሞኑ ንግግር ከቀደምት ንግግሮች የሚለየው ተቃዋሚዎችን በማካተቱ ሲሆን ይሄም በ25 ዓመት የስልጣን ዘመናቸው የመጀመሪያው እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ከአስራ አራት አመት መለያያትና ተደጋጋሚ እስር በኋላ በአልበሽር ንግግር የታደሙት ሀሰን አልቱራቢ፣“ከንግግሩ የምንጠብቀውን አላገኘንም፤ስለፖለቲካ  እንቅስቃሴም ሆነ ስለሚዲያ ነፃነት ምንም አልተባለም” ሲሉ ቅሬታቸውን ሰንዝረዋል፡፡ የኡማ ፓርቲ መሪ  ሳዲቅ አልመሀዲ ግን በችኮላ አስተያየት ለመስጠት የፈለጉ አይመስሉም፡፡    “በፕሬዚዳንቱ ንግግር ላይ አስተያየት ከመስጠቴ በፊት ጉዳዩን በደንብ ማጤን ይገባኛል” ነው ያሉት፡፡ የአገሪቱን ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥምረት የሚመሩት ፋሩቅ አቡ አሊ፣ከአልበሽር ንግግር ቀደም ብለው ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ በሰጡት መግለጫ፤“ፕሬዚዳንቱ በፖሊሲያቸው ምክንያት ለተጎዱ ወገኖች በተለይ በመስከረሙ ግጭት የሞቱትን ሰዎች አስመልክቶ ይቅርታ ሲጠይቁ መስማት እፈልጋለሁ” ብለዋል። አልበሽር ግን የተባለውን  ይቅርታ ባለፈው ሰኞ ንግግራቸው ላይ  አልጠየቁም፡፡  
እንዲያም ሆኖ ግን የአልበሽር ድንገተኛ የለውጥና የህዳሴ ንግግር እንዲሁም የ“እንወያይ” ጥሪ ብዙዎችን አስገርሟል - ድንገተኛና ያልተጠበቀ በመሆኑ፡፡ አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ደግሞ ከፍርሃት የመነጨ ነው ይላሉ - የአልበሽርን የለውጥና የህዳሴ ንግግር፡፡
በደቡብ ሱዳን ያለው የፖለቲካ አለመረጋጋት በተለይም ከነዳጅ አቅርበት ጋር ተያይዞ በሰሜን ሱዳን ላይ አሉታዊ ጫናውን እንዳያሳርፍ በመፍራት የወሰዱት እርምጃ ነው የሚሉት ተንታኞች፤በሌላ በኩል የሚፈነዳበት ወቅት የማይታወቀው ነገር ግን አይቀሬው ህዝባዊ አመፅ ከመምጣቱ በፊት እድላቸውን ለመሞከር ሲሉ ያደረጉት ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም በተለያዩ የአረብ አገሮች የተካሄዱና አሁንም ያልበረዱ ህዝባዊ አመፆችን በማስረጃነት ይጠቅሳሉ -ተንታኞቹ፡፡
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ደግሞ የአልበሽር አዲስ የለውጥ ጥሪ  ከአለምአቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ጋር ያለባቸውን እሰጥ አገባ በአገር ውስጥ  ነፍጥ ከታጠቁ  ወገኖች ጋር በመደራደር ከራሳቸው ከሱዳናውያን የሚመጣውን ግፊት ለመቀነስ ያለመ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ አስተያየት ሰጪዎቹ እንዲህ ይበሉ እንጂ አልበሽር ቢያንስ በሰኞው ንግግራቸው መሳሪያ ከታጠቁ  ኃይሎች ጋር ስለሚደረገው ውይይት ምንም የሰጡት ፍንጭ የለም፡፡
የአልበሽር ንግግር ከመደረጉ በፊት የገዢው ፓርቲ ባለስልጣናት የተለያዩ መረጃዎችነ ለሚዲያዎች መስጠታቸውም ሌላው ትኩረት የሳበ ጉዳይ ነው፡፡ አንድ የመንግስት ባለስልጣን  ቀድመው በሰጡት አስተያየት፤ አልበሽር በንግግራቸው ሁሉን አቀፍ የሆነ የለውጥ እቅድ እንደሚያቀርቡና የሱዳንን ቀውስ ለመፍታት ሁሉንም ወገኖች ያካተተ መፍትሄ እንደሚፈለግ ሲገልፁ፤ ሌላ ባለስልጣን ለሮይተርስ  በሰጡት መግለጫ፤ አልበሽር ሁሉም ተቃዋሚ ኃይሎች የአገሪቱን ህገመንግስት እንደገና አርቅቀው መንግስትን እንዲቀላቀሉ ጥሪ ያቀርባሉ ብለው ነበር። ከአልበሽር ንግግር በኋላ የተደበላለቁ እስተያየቶች መደመጣቸውን ተከትሎ የገዢ  ፓርቲው ምክትል ሊቀመንበርና  የፓርቲ ጉዳዮች ሀላፊ ኢብራሂም ጋንዱር በሰጡት መግለጫ “በሽር ለህዝቡ ንግግራቸውን ለማቅረብ ያቀዱት ከፓርቲዎች ጋር ከተወያዩ በኋላ ነበር፤ነገር ግን ብዙ ጥርጣሬዎች እና መላምቶች ቀድመው በመናፈሳቸው ለህዝቡ ንግግር ለማድረግ ተገደዋል” ብለዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ላይ ከተሳተፉ በኋላ የንግግራቸውን ቀጣይ ክፍል እንደሚያቀርቡና ሁለተኛው ክፍል ብዙ ጉዳዮችን ዘርዘር ባለ መልኩ እንደሚያካትት ኃላፊው ተናግረዋል፡፡
“የሱዳን ህዳሴ” የሚለው ሰነድም በገዢው ፓርቲ በኩል የቀረበ በመሆኑ የመንግስት ሰነድ አድርጎ መውሰድ እንደማይቻል የገለፁት ኢብራሂም፤ፓርቲያችን ለሱዳን ችግሮች የመፍትሄ አቅጣጫዎች እያቀረበ ሳይሆን ሌሎች የፖለቲካ ሀይሎችም የራሳቸውን ሀሳብ እንዲያመጡ እድል እየሰጠ ነው ብለዋል፡፡
በሰኞው የአልበሽር ንግግር “ብዙዎች ተስፋ ቆርጠዋል” የሚለውን አስተያየት ኢብራሂም አይቀበሉትም፡፡  “አስተያየቱ ትክክል አይደለም፤ምክንያቱም ከአልበሽር ንግግር በኋላ የተሰራ ፈጣን ቅኝት ህዝቡ  በፕሬዚደንቱ ንግግር መርካቱን ነው የሚያሳየው” ብለዋል፡፡
በአለምአቀፍ ተቋሟት ይፋ የሚደረጉ የጥናት ሪፖርቶች እንደሚያመለክቱት፤ሱዳን በሙስና፣ በልማት  እና በፕሬስ ነፃነት ረገድ  ከመጨረሻዎቹ የዓለም አገራት ተርታ ትመደባለች፡፡ ፕሬዚዳንት አልበሽርም  አስራ አንድ አመቱን ካስቆጠረው የዳርፉር ጦርነት ጋር በተያያዘ በሰዎች ግድያና በዘር ማጥፋት ወንጀል በአለምአቀፉ የወንጀለኞች ፍርድቤት የሚፈለጉ መሪ ናቸው፡፡ ባለፈው መስከረም ወር  ከነዳጅ ዋጋ ጋር ተያይዞ በሱዳን በተፈጠረ አለመረጋጋት፣ ከሁለት መቶ በላይ ሰዎች በፀጥታ ሀይሎች መገደላቸውን አምነስቲ ኢንተርናሽናል ቢገልፅም፤የአልበሽር መንግስት ቁጥሩ እጅግ የተጋነነ ነው ሲል አጣጥሎታል፡፡

Read 3571 times