Monday, 10 February 2014 06:58

መርካቶን ከነስሞቿ ለትውልድ ለማስተላለፍ ዘመቻ ሊጀመር ነው

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(4 votes)

        በዘመናዊ ግንባታ የተነሳ የቀድሞ ስሞቿን እያጣች ነው የተባለችውን መርካቶን ከነስሞቿ ለትውልድና ለቱሪስቶች ለማቆየት ዘመቻ ሊጀመር እንደሆነ ተገለፀ፡፡
መርካቶ ውስጥ ከ50 በላይ የሚጠጉ “ተራዎች” እንደሚገኙም ተጠቁሟል፡፡
ባለፈው ረቡዕ መሳለሚያ አማኑኤል ፀጋ ህንፃ ላይ በሚገኘው የአዲስ ከተማ ክ/ከተማ አስተዳደር ፅ/ቤት በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ በመርካቶ ከዘመናዊ ግንባታ ጋር በተገናኘ እንደነ ምን ያለሽ ተራ፣ ጭድ ተራ፣ ቦንብ ተራ፣ ሳጥን ተራ፣ በርበሬ ተራ፣ ያሉ ስሞች ሊጠፉ መቃረባቸው የተጠቆሙ ሲሆን ይህም 75 ዓመት እድሜ ያላትንና በአፍሪካ ትልቋ የገበያ ማዕከል እንደሆነች የሚነገርላትን መርካቶን ታሪክ አብሮ ያጠፋል ተብሏል፡፡ የአዲስ ከተማ ክ/ከተማ ባህልና ቱሪዝም ጽ/ቤትና ኤርቦሬ ኮሚዩኒኬሽንና ቢዝነስ ፒኤልሲ የመርካቶን ታሪክ ለመታደግ በትብብር የሚያካሂዱት ዘመቻ የካቲት 15 እና 16 እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡
ዘመቻው በዋነኝነት የንግዱን ማህበረሰብ በማሳተፍ በሚገነቡ የንግድ ህንፃዎች ላይ የተራዎቹ ስም ከነ ታሪካዊ ምክንያታቸው ተገልፆ በእምነበረድ እንዲፃፍና ለትውልድና ለቱሪስት መስብህነት እንዲተላለፍ ለማድረግ ያለመ እንደሆነም የክ/ከተማው ባህልና ቱሪዝም ጽ/ቤት ኃላፊ ወ/ሪት አዜብ ገ/ማሪያም ተናግረዋል፡፡
“ለመርካቶ ጌጦቿ ጥንታዊ ስሞቿ” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው ዘመቻ ላይ የካቲት 15 ቀን በሜትሮ ሆቴል ሲምፖዚየም እንዲሁም መነሻውንና መድረሻውን ምዕራብ ሆቴል ያደረገ የንግዱ ህብረተሰብና ሌሎች አላማውን የሚደግፉ ግለሰቦች የሚካፈሉበት ሩጫ፣ የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽን፣ የተመረጡ የመርካቶ አካባቢዎች ጉብኝትና መርካቶ ላይ የሚያጠነጥን ዶክመንተሪ ፊልምና መሰል ፕሮግራሞች እንደተዘጋጁ ታውቋል፡፡
በሁለቱ ቀን ዘመቻ ላይ የኢፌዲሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር፤ ሚኒስትር ዲኤታዎች፣ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር፣ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ፣ የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ተወካይ፣ የኢትዮጵያ ቅርስ ባላደራ ተወካይ፣ የክፍለ ከተማው ስራ አስፈጻሚዎችና ሌሎች የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች ተሳታፊ እንደሚሆኑ የኤርቦሬ ኮሚዩኒኬሽንና ቢዝነስ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ዘሪሁን ግርማ ተናግረዋል፡፡

Read 3784 times