Monday, 10 February 2014 06:59

የህፃናት ሽያጭንና ህፃናትን በጦርነት ማሳተፍን የሚከለክሉ አለም አቀፋዊ አዋጆች ፀደቁ

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(1 Vote)

አገሪቱ አዋጆቹን አለማፅደቋ በተመድ የሰብአዊ ምክር ቤት አባል እንዳትሆን አግደዋት ቆይተዋል

ኢትዮጵያ የህፃናት ሽያጭን፣ የህፃናት የወሲብ ንግድንና ህፃናትን በወሲብ ተግባር ማሳተፍን የሚከለክልና ህፃናትን በጦርነት ማሳተፍን የሚያግዱ ሁለት አለም አቀፋዊ የህፃናት መብቶች ኮንቬንሽን አፀደቀች፡፡ አገሪቱ እስከአሁን ኮንቬንሽኑን ካላፀደቁት አስራ አራት የዓለም አገራት አንዷ ሆና ቆይታለች፡፡
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰሞኑን በይፋ ያፀደቀው የኮንቬንሽኑ ፕሮቶኮል እንደሚያመለክተው፤ 162 አገራት ፕሮቶኮሉን አፅድቀው አባል ሆነዋል፡፡ የተባበሩት መንግስታት የህፃናት  ድርጅት (ዩኒሴፍ) ያወጣው መረጃ እንደሚጠቁመው፤ የህፃናት ሽያጭ፣ የህፃናት የወሲብ ንግድና ቱሪዝም እንዲሁም ህፃናትን ወሲብ ቀስቃሽ ፊልሞች የማሰራት ወንጀሎች በዓለም ዙሪያ እጅግ አስደንጋጭ ደረጃ ላይ ደርሰዋል፡፡ በየዓመቱ አንድ ሚሊዮን ህፃናት በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር በሚሰበስቡ ህገ-ወጥ ነጋዴዎች የወሲብ ንግድ ተግባር ላይ እንዲሰማሩ ይደረጋሉ ያለው መረጃው፤ በህፃናቱ ላይ ለሚደርሱ ኢሰብአዊ ድርጊቶች ለዚህ መነሻ ምክንያቱም ኋላቀርነት፣ ድህነት፣ የኢኮኖሚ ልዩነት፣ ፍትሃዊ ባልሆነ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መዋቅር የፈረሱ ቤተሰቦች፣ የትምህርት አቅርቦት እጥረት፣ ከገጠር ወደ ከተማ ስደት፣ የፆታ ልዩነት፣ ጎጂ ባህላዊ ልማዶችና ጦርነቶችን እንደምክንያት ጠቅሷል አዋጁ እነዚህን ተግባራት በህግ መከልከልና የህፃናት ጥበቃና እንክብካቤ ማድረግ እንደሚገባ  ይደነግጋል፡፡
ህፃናትን በጦርነት ማሳተፍን ለመከልከል የወጣው የህፃናት መብቶች ኮንቬንሽን በበኩሉ፤ ሁሉም አገራት ወንዶችንም ሆነ ሴት ህፃናትን በጦርነት እንዳያሳትፉ የሚጠይቅ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶት ምክር ቤት አባል ለመሆን በተወዳደረችባቸው ጊዜያት ሁሉ ይህንን የህፃናት መብት ኮንቬንሽን ፕሮቶኮል አለማፅደቋ እንቅፋት ሆኗት እንደቆየ የጠቀሰው ለፕሮቶኮል ማፅደቂያ የወጣው መግለጫ፤ የመንግስታቱ ድርጅት የሰብአዊ ምክር ቤት የአገሪቱን አጠቃላይ ወቅታዊ ግምገማ ሪፖርት ባቀረበበት ጊዜም አገሪቱ ይህንኑ ኮንቬንሽን እንድታፀድቅ ምክር ሰጥቷት እንደነበርና ግዴታ ከገባችባቸው ጉዳዮች አንዱ እንደሆነም ጠቅሷል፡፡
በአዋጁ አገሪቱ ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ህፃናትን በጦርነት እንዲሳተፉና በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ እንዲቀጠሩ አለመደረጋቸውን የማረጋገጥ ኃላፊነትን የጣለባት ሲሆን አባል አገራቱ 18 ዓመት ያልሞላቸውን ህፃናት በግዳጅ ለወታደራዊ ተግባር እንዳይመለምሉ ግዴታ ይጥላል፡፡  አለም አቀፋዊ የህፃናት መብት ኮንቬንሽኑ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት በፀደቀበት ወቅት እንደተገለፀው፤ ኮንቬንሽኑን ለማስፈፀም የሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ጉዳይ ሚኒስቴር ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡

Read 3225 times