Monday, 10 February 2014 07:02

የህወሓት የልደት በዓል ህዝባዊ ስብሰባ አስተጓጐለብኝ - ዓረና

Written by  አበባየሁ ገበያው
Rate this item
(3 votes)

ዓረና፤ በትግራይ ሁመራ ከተማ ህዝባዊ ስብሰባ ለማድረግ ፍቃድ ካገኘ በኋላ ወሩ የህወሓት 39ኛ ዓመት የልደት በዓል የሚከበርበት ወቅት ነው በሚል የከተማው አስተዳደር ስብሰባውን እንዳገደበት የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ አባል አቶ አብርሃ ደስታ ገለፁ፡፡
አቶ አብርሃ ደስታ ለአዲስ አድማስ እንደጠቆሙት፤ ባለፉት ሳምንታት በሁመራ ከተማ ህዝባዊ ስብሰባ ለማካሄድ ቅስቀሳ ሲያደርጉ የሰነበቱ ሲሆን፤ ስብሰባውን ቅዳሜ እና እሁድ እንዳያደርጉ ተከልክለው ለትናንት አርብ ፈቃድ አግኝተው ነበር፡፡ ይሁንና በሰላማዊ መንገድ ህዝባዊ ጥሪ አድርገን ቅስቀሳውን በተሳካ ሁኔታ ከፈፀምን በኋላ በህወሓት የልደት በዓል ተጨናንቀናል፤ የተቃውሞ ስብሰባ ማድረግ አትችሉም፤ ህገወጥ ናችሁ” ተባልን ብለዋል - አቶ አብርሃ፡፡
ህዝባዊ ስብሰባው  በፓርቲው ፖሊሲ፣ በኢትዮ-ኤርትራና ኢትዮ-ሱዳን ድንበር ጉዳይ እንዲሁም በአገር ሉዓላዊነት ዙርያ የሁመራን ህዝብ ለማወያየት ያለመ ነበር ያሉት የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ አባል፤ ኢህአዴግ የተለያየ ምክንያት ይደርድር እንጂ ስብሰባችንን ያስተጓጐለው ፓርቲያችን ስጋት ስለሆነበት ነው ብለዋል፡፡
ከሁለት ሳምንት በፊት ፓርቲው በዓዲግራት ስብሰባ ለማካሄድ ቅስቀሳ ሲያደርግ፣ አባላቱ እንደተደበደቡና እንደታሰሩበት አቶ አብርሃ አስታውሰዋል፡፡

Read 2133 times