Saturday, 15 February 2014 12:33

ኢትዮጵያዊው የኢኮኖሚ ባለሙያ የዓለም ባንክን ከሰሰ

Written by  አንተነህ ይግዛው
Rate this item
(17 votes)
  • ባንኩ በሰራተኞቹ አያያዝ ዘረኝነት እንደሚያጠቃው አምኗል
  • ከ3ሺ500 ሰራተኞቹ በከፍተኛ ሃላፊነት የተመደቡት ጥቁሮች 4 ብቻ ነበሩ
  • የባንኩ ቃል አቀባይ ውንጀላው አግባብ አይደለም ብለዋል


       ነዋሪነቱ በአሜሪካ የሆነው ኢትዮጵያዊው የኢኮኖሚ ባለሙያ ዮናስ ብሩ፤ ከአስር አመታት በላይ በከፍተኛ የሃላፊነት የስራ መደብ ተቀጥሮ ይሰራበት የነበረው የአለም ባንክ፣ ያለአግባብ ከስራ በማፈናቀልና የዘረኝነት ጥቃት በማድረስ ለፈጸመበት ወንጀል የ4.1 ሚሊዮን ዶላር (ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ) ካሳ ሊሰጠኝ ይገባል ሲል ክስ መመስረቱን ዋሽንግተን ኢንፎርመር ዘገበ፡፡
“የሚገባኝን የስራ እድገት ተከልክያለሁ ብዬ ለአለቆቼ ተቃውሞዬን በማሰማቴና መብቴን ለማስከበር በመሞከሬ በአለም ባንክ ባለስልጣናት ውሳኔ፡ ያለአግባብ ከስራ ገበታዬ ተፈናቅያለሁ” የሚለው ዮናስ፤ የተቋሙ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ በጥቁሮች ላይ የሚያደርሱትን የዘረኝነት በደልና መድልኦ በመቃወሙ ቅጣት እንደተጣለበትም ተናግሯል፡፡
ባንኩ፣ የሚገባውን የስራ መደብ ያለአግባብ ከመከልከል አልፎ ከስራ በማፈናቀልና ከቀለም ልዩነት ጋር በተያያዘ ላደረሰበት የዘረኝነት ጥቃት ቀደም ሲል ሁለት ክሶችን መስርቶ እንደነበር የገለጸው ዮናስ፤ ጉዳዩን ሲመረምር የቆየው ፍርድ ቤት ግን፣ ፍትሃዊ ባልሆነ ሁኔታ ባንኩን በነጻ እንዳሰናበተው ጠቅሶ፣ይህም ሌላ ክስ እንዲመሰርት እንዳነሳሳው ይናገራል፡፡
ፍርድ ቤቱ፤ ባንኩን ከተጠያቂነት ነጻ ቢያደርገውም፣ ክሶቹን እንደገና ለመመስረትና ፍትህ ለማግኘት እንቅስቃሴ መጀመሩን የገለጸው ዮናስ፤ ከስራ በመፈናቀሉ ሳቢያ ለደረሰበት የአእምሮ ጭንቀት እና ሳይከፈለው ለቀረው ደመወዝና ጥቅማጥቅም፣ የአለም ባንክ 4 ነጥብ 1 ሚሊዮን  ዶላር ካሳ ሊከፍለኝ ይገባል ብሏል፡፡
“ማንም ሰው አለም ባንክን የመሰለ ስመ ገናና ተቋም እንደዚህ አይነት በደል ይፈጽማል ብሎ ለማሰብ ይቸገራል፡፡ ባንኩ የስራ ልምዴን እንዲሰጠኝ ብጠይቅም ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ በማናጀርነት ማገልገሌን የሚያረጋግጠውን መረጃ ሊሰጡኝ ባለመፈለጋቸው ሌላ ስራ ለመቀጠር እንኳን አልቻልኩም” ብሏል ዮናስ፡፡
 በ1985 ዓ.ም የአለም ባንክ ባልደረባ ሆኖ መቀጠሩን የሚናገረው ዮናስ፤ ከ6 አመታት በኋላም በባንኩ ስር የሚገኘውን ኢንተርናሽናል ኮምፓሪዝን ፕሮግራም የማሻሻል ሃላፊነት ተሰጥቶት ስራውን በአግባቡ ማከናወኑንና ከ1993 እስከ 2001 ዓ.ም ፕሮግራሙን የበለጠ ለማጠናከር የሚያስችሉ የምርምር ስራዎችን በአግባቡ ሲመራ መቆየቱን ያስታውሳል፡፡ ፕሮግራሙን በየተለያዩ የእስያና የላቲን አሜሪካ አገራት በማስፋፋት ረገድ ተጠቃሽ ስራ ማከናወኑንና ለሰባት አመታት ያህልም ለፕሮግራሙ ገቢ በማሰባሰብ ስራ ላይ መሳተፉን ገልጿል፡፡
 ሆኖም የስራ ልምዱም ሆነ የትምህርት ዝግጅቱ በሚፈቅድለትና ግሎባል ማናጀር ተብሎ በሚታወቀው የባንኩ ከፍተኛ የስራ መደብ ላይ ለመስራት ሲያመለክት፣ የቅርብ አለቃውና የአለም ባንክ ዳይሬክተር የሆነ ሌላ ግለሰብ ያለአግባብ እንደከለከሉት የሚናገረው ዮናስ፤ ለዚህም እንደ ምክንያት ያቀረቡለት አውሮፓውያን በዚህ የስራ መደብ ላይ ጥቁር ሰው ተቀጥሮ ሲሰራ አይተው አያውቁም የሚል እንደነበር ገልጿል፡፡ እንዲህ ያሉት በስራው ላይ እንዳልቀጠር የፈለገው የፕሮግራሙ የውጭ ስራ አስፈጻሚ ቦርድ ለማስመሰል ነው ያለው ዮናስ፤ ቦርዱ ግን ይህ ጉዳይ እንደማይመለከተውና የሃሰት ውንጀላ መሆኑን አረጋግጧል ብሏል፡፡
“ባንኩ ትንሽ ቆይቶ ደግሞ፣ በዚህ የስራ መደብ ላይ እንዳልመደብ የተደረገው የልምድ ማነስ ስላለብኝ እንደሆነ  ተናግሯል፡፡ ይህ ግን ፍጹም የተሳሳተ መሆኑን በባንኩ ውስጥ የሚገኘው የስራ አፈጻጸም ልምዴ ያረጋግጣል፡፡ ምክትል ግሎባል ማናጀር ሆኜ በሰራሁባቸው አመታት፣ የተጣለብኝን ከፍተኛ ሃላፊነት በአግባቡ የምወጣ ትጉህ ሰራተኛ እንደነበርኩ የባንኩ ከፍተኛ አመራሮችና የቅርብ አለቆቼ መስክረውልኛል፡፡ ይሄን የሚያረጋግጡ ሰነዶች በግል ማህደሬ ውስጥ ቢኖሩም፣ ሰነዶቹ በባንኩ ሃላፊዎች በህገወጥ መንገድ ተሰርዘው በፕሮግራሙ ውስጥ አይነተኛ  ሚና እንዳልነበረኝና የግሎባል ማናጀርነት የሚጠይቀው  ብቃትና ታማኝነት እንደሌለኝ ተደርገው ተጽፈዋል” በማለት ተፈፀመብኝ ያለውን በደል ዘርዝሯል፡፡
በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡ የተጠየቁት የአለም ባንክ ቃል አቀባይ፤ ውንጀላው አግባብ አይደለም ከማለት ውጪ ዝርዝር መረጃ ለመስጠት ፍቃደኛ እንዳልሆኑ የዋሽንግተን ኢንፎርመር ዘገባ ያስረዳል፡፡ “እንዲህ አይነት ክሶች እጅግ አስቸጋሪ ናቸው፤ ነገሩ በሂደት እየተስፋፋና መነጋገሪያ እየሆነ መጥቷል፡፡ ውንጀላው ቀላል አይደለም፡፡ ሰውዬው ስር የሰደደ አመለካከት ነው የያዘው፡፡ በባንኩ አሰራሮች ላይ ያነሳቸውን ጥያቄዎችና ውንጀላዎች በቀላሉ አናያቸውም፤ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥተን እንሰራለን፡፡ ከዘረኝነት ጋር ተያይዞ የተነሳውን የሰራተኞቻችን ብዝሃነት  በተመለከተም ጠንካራ አቋም እንደያዝን እንቀጥላለን” ብለዋል የባንኩ ቃል አቀባይ፡፡
“ፍትህ እንዲሰጠኝና ባንኩም እኔን ለስቃይ በመዳረጉ ጥፋተኛነቱን አውቆ እንዲታረም ነው የምፈልገው፡፡ ያለአግባብ ተዛብቶ የተጻፈው የስራ ማስረጃዬ  እንዲስተካከልልኝ ጥያቄ ባቀርብም፣ ባንኩ ግን አሁንም ድረስ ፈቃደኛ ሊሆን አልቻለም። የተዛባውን የስራ ልምድ ማስረጃዬን  ለህዝብ ይፋ ከማውጣት እንዲታቀቡ ብጠይቃቸውም  አሻፈረን ብለዋል፡፡ ይሄም ባለኝ ትምህርትና የስራ ልምድ ሌላ ቦታ ተቀጥሬ እንዳልሰራ እንቅፋት ለመፍጠር ሆን ተብሎ በባንኩ የተሰራብኝ ደባ ነው፡፡” ብሏል ዮናስ ለዋሽንግተን ኢንፎርመር፡፡
የአለም ባንክ በአፍሪካውያንና አፍሪካ አሜሪካውያን ሰራተኞቹ ላይ በሚያሳየው ያልተገባ የዘረኝነት አመለካከት ከሰላሳ አመታት በላይ ሲተች እንደቆየ የሚናገረው ዮናስ፤ ይሄም ሆኖ ግን ባንኩ በዚህ ድርጊቱ ሳቢያ በህግ ተጠይቆ እንደማያውቅ ገልጿል፡፡ የአለም ባንክ ከተለያዩ 170 የአለም አገራት የተመረጡ 15 ሺህ ያህል ሰራተኞች የሚያስተዳድር ትልቅ ድርጅት እንደሆነ የገለጸው ዋሽንግተን ኢንፎርመር፤ ከተወነጀለበት የዘረኝነት ሃሜት ነጻ እንዳልሆነ የሚጠቁም መረጃ አያይዞ አቅርቧል፡፡ የአሜሪካ የመንግስት ተጠያቂነት ፕሮጀክትን መረጃ ጠቅሶ እንደዘገበውም፣ በ2000 ዓ.ም  በባንኩ ዋና ጽህፈት ቤት ተቀጥረው ይሰሩ ከነበሩት 3ሺ 500 ሰራተኞች መካከል ሙያዊ በሆኑ ከፍተኛ የሃላፊነት ቦታዎች ላይ የተመደቡት አራት ጥቁር አሜሪካውያን ብቻ ነበሩ፡፡
ፕሮጀክቱ በሰራው ጥናት፣ ጥቁሮች በባንኩ የአመራርነት ቦታዎች ላይ የመመደብ እድላቸው አነስተኛ መሆኑን አረጋግጧል፡፡ በዚህ ፕሮጀክትና በራሱ በአለም ባንክ የተሰሩ ጥናቶችም፣ በባንኩ ውስጥ ከቀለም ልዩነት ጋር በተያያዘ በጥቁሮች ላይ የዘረኝነት ጥቃትና መድልኦ ስር መስደዱ ተረጋግጧል፡፡ ጥቁር የባንኩ ሰራተኞች ወደከፍተኛ የአመራርነት ቦታ እንዳይመጡና እድገት እንዳያገኙ ጫና እንደሚደረግባቸውም ተጠቁሟል፡፡
የባንኩ የቀድሞ የስራ ባልደረባ ፊሊስ ሙሃመድ በአንድ ወቅት ለንባብ ያበቃችውን መረጃ በመጥቀስ ዋሽንግተን ኢንፎርመር እንደዘገበው፤ በ1952 ዓ.ም በባንኩ የአንድ ክፍል ሃላፊ የነበሩ ግለሰብ፣ ሰራተኞችን ባሳተፈ ስብሰባ ላይ የባንኩን ዘረኝነት የሚያረጋግጥ ንግግር አሰምተዋል፡፡ “ጥቁሮች ደደብ የሂሳብ ባለሙያዎችን ነው የሚያፈሩት፤ የእኛ ክፍልም የቦዘኔዎች መፈንጫ ጉራንጉር መምሰል ስለማይፈልግ ብዙ ጥቁሮችን ቀጥሮ አያሰራም። ጥቁሮች እዚያው በአፍሪካ ጉራንጉር ነው መኖር ያለባቸው” በማለት፡፡
 ዋሽንግተን ኢንፎርመር ያቀረበው ሌላው መረጃም፣ በ1990 ዓ.ም የተካሄደ አንድ የአለም ባንክ ውስጣዊ ስብሰባ ሚስጥራዊ ቃለጉባኤ፣ ጥቂት የባንኩ ማናጀሮች “ጥቁሮች የበታች ናቸው” ብለው እንደሚያስቡና ጥቁሮች ከአፍሪካ ውጭ የመስራት ችሎታቸው አናሳ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ፣ በአብዛኛው በዚያው በአህጉራቸው አካባቢ እንዲሰሩ እንደሚደረግ  አመልክቷል፡፡
ባለትዳርና የሶስት ልጆች አባት የሆነው ዮናስ ብሩ፤ የንጉሳዊው አገዛዝ አክትሞ ደርግ ወደ ስልጣን በመጣበት ጊዜ ወደ አሜሪካ መሄዱንና በተለያዩ የጉልበት ስራዎች ላይ ተሰማርቶ ለአመታት ደፋ ቀና ብሎ በመስራት ራሱን አስተምሮ፣ ከጆርጅ ማሰን ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ የዶክትሬት ዲግሪውን መቀበሉን ለዋሽንግተን ኢንፎርመር ተናግሯል፡፡

Read 5448 times