Saturday, 15 February 2014 12:57

የጥርስ ህመምና መዘዙ

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(6 votes)
  • የጥርስ ህመም ለልብ፣ ለስኳርና ለሳንባ በሽታዎች ያጋልጣል
  • በስትሮክ የመሞት ዕድልን በእጥፍ ይጨምራል
  • አብዛኛዎቹ የታሸጉ ውሃዎች የፍሎራይድ እጥረት አለባቸው

ያቺ ቆንጆ ጥርሰ በረዶ ናት
ውብ አይናማ ናት
ከዛች ቆንጆ ጥርሷ ከሚያምር
ያዘኝ ፍቅር …
እያለ ድምፃዊው የጥርስን ውበት የገለፀበትን ይህንን ዘመን ተሻጋሪ ዜማ ለዓመታት ደጋግመን ሰምተነዋል፡፡ ዜማው አፍቃሪው የወደዳትን ኰረዳ ውበትና ቁንጅና የሚያወድስበትና ፍቅሩን የሚገልፅበት ቃል አጥቶ፣ ከውበቷ ሁሉ ጐልቶ በታየው የጥርሶቿ ውበት መማረኩን የገለፀበት ውብ ዜማ ነው፡፡ ይኸው ዕውቅ ድምፃዊ የጥርስን ውበት በገለፀበት ሌላው ዘፈኑ ስንኝ ላይ፤  
ይገርማል ቁመናና ዛላ
ልዩ ነው የፀጉሯ ዘለላ
ጥርሶቿ አቀማመጣቸው
ይገርማል አቤት ንጣታቸው …
በማለት ጥርስ ምን ያህል የውበት መገለጫ፣ የውበት ማሣያ እንደሆነ ነግሮናል፡፡ ይህ የውበት መገለጫ የሆነው ጥርሳችን፣ ከሰውነታችን እጅግ ጠንካራው ክፍልና ጠቀሜታው ከፍተኛ የሆነ ተፈጥሮአዊ ስጦታችን ነው፡፡
ጤንነቱ የተጠበቀ ጥርስ ለባለቤቱ ውብ ገፅታን ከማጐናፀፉም በላይ ከሰዎች ጋር ያለ መሳቀቅ ለማውራትና እንደ ልብ ለመሳቅ ያስችላል፡፡ ያለ አፍረትና ያለ መሳቀቅ ለመሳሳምም ጤናማ ጥርስ የሚለግሰው ንፁህ የአፍ ጠረን ወሣኝነት አለው፡፡
ጥርሳችን በተለያዩ ምክንያቶች ጉዳት ሊደርስበትና ተፈጥሮአዊ ውበቱን ሊያጣ ይችላል። ለጥርስ ህመም ከሚያጋልጡ በርካታ ምክንያቶች መካከልም ጥርስን በአግባቡ አለማፅዳትና የፍሎራይድ እጥረት ዋንኞቹ እንደሆኑ የጥርስ ህክምና ስፔሻሊስቱ ዶክተር ይስሃቅ ታምሩ ይገልፃሉ፡፡ የጥርሳችንንና የድዳችንን ጤንነት ለመጠበቅ እጅግ በቀላል መንገድ ጠዋትና ማታ ጥርስን በብሩሽና በጥርስ ሳሙና ማፅዳት እንዲሁም ምግብ ከተመገብን በኋላ አፋችንን በመጉመጥመጥ በጥርሳችን ውስጥ የሚቀሩ የምግብ ትርፍራፊዎችን ማስወገድ ይኖርብናል፡፡  የጥርሳችንን ጤና ለመጠበቅ ካልቻልን በአለማችን እጅግ አደገኛ የጤና ቀውስ ከሚያስከትሉ በሽታዎች አንዱ ለሆነው የጥርስ ኢንፌክሽን ልንጋለጥ እንችላለን፡፡
ጥርሳችን ከጭንቅላታችንና ከመላው የአካል ክፍላችን ጋር ግንኙነት ያለው ሲሆን ይህ የአካላችን ክፍል ሲጐዳ (ሲታመም) ጉዳቱና ችግሩ ጭንቅላታችንን ጨምሮ በመላው የሰውነታችን ክፍሎች ላይ ችግር ሊያስከትል እንደሚችል የጥርስ ህክምና ባለሙያው ይናገራሉ፡፡
የጥርስ ኢንፌክሽን በሽታ በየትኛውም የዕድሜ ክልል ሊከሰትና ማንኛውንም ሰው ሊያጠቃ የሚችል በሽታ እንደሆነ የሚናገሩት ዶክተሩ፤ ምግብ ከተመገብን በኋላ አፋችንን በመጉመጥመጥ በጥርሳችን መሀል የሚቀሩ ትርፍራፊ ምግቦችን የማናፀዳ ከሆነ፣ ለባክቴሪያ መራቢያ ምቹ ሁኔታዎችን እንፈጥራለን፡፡ በርካታ ባክቴሪያዎች በቀላሉ በአፋችን ውስጥ ከተራቡ በኋላ ጥርሳችን እንዲቦረቦር፣ መንጋጋችን እንዲበሰብስና እንዲቆስል በማድረግ ለጥርስ ኢንፌክሽን ሊያጋልጡን ይችላሉ። እነዚህ ባክቴሪያዎች የአፋችን ውስጠኛው ክፍል እንዲቆስልና መጥፎ የአፍ ጠረን እንዲፈጠር ከማድረጋቸውም በላይ የአንገት አካባቢ ቆዳን በመብላት ተጠቂው የመተንፈሻ ቱቦ ችግር እንዲያጋጥመው ያደርጋሉ፡፡ አየር ወደታማሚው ልብና ሳንባ እንደልብ እንዳይደርስ በማገድ ልብ፣ ሣንባና አዕምሮ ላይ ችግር ይፈጥራሉ፡፡ ይህ ሁኔታም ታማሚው የአየር እጥረት እንዲያጋጥመው በማድረግ ለሞት ሊዳርገው እንደሚችል ዶክተር ይስሃቅ ይገልፃሉ፡፡
አንድ ሰው በጥርስ ኢንፌክሽን በሽታ ሲጠቃ ምንም አይነት ምልክቶችን አያሳይም፤ ችግር እንደተከሰተ በተጠቂው ሰው ላይ የሚታይ የጤና መቃወስ አይኖርም፡፡ በዚህ ምክንያትም በርካቶች ችግሩ መኖሩን እንኳን ሣያውቁ ለከፋ የጤና ጉዳት ይዳረጋሉ፡፡ በድድ ላይ የሚከሰቱ ኢንፌክሽኖችና እብጠቶችን ለመከላከል ሰውነታችን ኢንፌክሽን ተዋጊ ሴሎችን በማመንጨት እንደሚዋጋ የገለፁት ዶክተር ይስሃቅ፤ እነዚህ ሴሎች በሌሎች የሰውነታችን ክፍሎች ላይ ጉዳት ሊያስከትሉ እንደሚችሉም ተናግረዋል፡፡ በድድና በጥርስ ላይ የሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች በወቅቱ ተደርሶባቸው በቶሎ ህክምና ካላገኙ በድድና በመንጋጋ ጅማቶች ላይ አደገኛ ጉዳት ያስከትላሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በኢንፌክሽኑ የሚፈጠሩ ባክቴሪያዎች በአፋችን በኩል ወደ ውስጣዊ ሰውነታችን ይገቡና ወደ ልባችን በመምራት፣ ልብ ተፈጥሮአዊ ተግባሩን በአግባቡ እንዳያከናውን ሊያደርጉትና ጉዳት ሊያስከትሉበት ይችላሉ ብለዋል፡፡ በጥርስ ኢንፌክሽን የተጠቁ ሰዎች ከሌሎች ጤናማ ሰዎች ይልቅ በቀላሉ በልብ በሽታ ሊያዙ እንደሚችሉ የጠቆሙት ዶክተሩ፤ የድድ በሽታ፣ ስኳርና፣ የሳንባ በሽታዎችም በዚሁ ችግር ሳቢያ ሊከሰቱ የሚችሉ የጤና ችግሮች እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የችግሩ ተጠቂዎች በስትሮክ የመሞት ዕድላቸው ከሌሎች ጤናማ ሰዎች ጋር ሲነፃፀር በእጥፍ እንደሚበልጥም እንኚሁ የጤና ባለሙያ ተናግረዋል፡፡ ሌላው ለጥርስ ህመም መንስኤነት በዋነኛነት ከሚጠቀሱት ጉዳዮች መካከል አነስተኛ የፍሎራይድ ማዕድን ይዘት ያላቸውን ወይንም በቂ ፍሎራይድ ማዕድን ይዘት የሌላቸውን ውሃዎች መጠጣት ነው ያሉት ዶክተሩ፤ ሰውነታቸው በቂ የፍሎራይድ መጠን ሳያገኝ ሲቀር ወይንም የፍሎራይድ ማዕድን እጥረት በሚከሰትበት ወቅት ጥርሳችንም ሆነ ድዳችን ለከፋ የጤና ችግር ሊጋለጥ ይችላል ብለዋል፡፡ ይህም በአብዛኛው የአገራችን ክፍሎች በስፋት እንደሚታይም ዶክተሩ ጠቁመዋል፡፡ ተጣርተው በፕላስቲክና በጠርሙስ እየተሞሉ ገበያ ላይ የሚውሉ ውሃዎች በአብዛኛው በውስጣቸው የሚይዙት የፍሎራይድ ማዕድን መጠን እጅግ አነስተኛ መሆኑንና አንዳንዶቹም ምንም ፍሎራይድ ማዕድን በውስጣቸው እንደሌለ የጠቆሙት ዶክተሩ፤ ይህም ለጥርስና ለድድ ኢንፌክሽኖችና ለመንጋጋ መቦርቦር በማጋለጥ፣ የከፋ የጤና ችግር ሊያስከትል እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ህብረተሰቡ ለመጠጥነት የሚገለገልባቸውን የታሸጉ የፕላስቲክ ውሃዎች የማዕድን ይዘት የማየትና የማወቅ ልምዱ እምብዛም ነው ያሉት ዶክተር ይስሃቅ፤ ይህም ህብረተሰቡ የቀረበለትን ሁሉ ያለጥያቄና ያለዕውቀት እንዲጠቀምና ለተለያዩ የጤና ችግሮች እንዲጋለጥ እያደረገው ነው ብለዋል። እያንዳንዱ ሰው የሚመገባቸው ምግቦችና መጠጦች ምን አይነት ቫይታሚንና ማዕድኖችን በምን ያህል መጠን እንደሚይዙ ማወቅ ይገባዋል ሲሉም አክለዋል፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዘውም ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት አካላትም በተለያዩ ፋብሪካዎች እየተመረቱ ለህብረተሰቡ ጠቀሜታ የሚቀርቡ ምግቦችና መጠጦች ይዘት ላይ ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል ማድረግ ይገባዋል ብለዋል፡፡
የጥርስ ጤና ላይ ችግር በሚያጋጥምበት ወቅት በአፋጣኝ ወደ ህክምና ተቋም መሄድ ተገቢ ነው ያሉት ዶክተር ይስሃቅ፣ በየስድስት ወሩ የጥርስን ጤንነት ለማወቅ ወደ ጥርስ ህክምና ተቋማት ጎራ ማለቱ ጠቀሜታው ሰፊ ነው ይላሉ፡፡
በተለያዩ ፋብሪካዎች ተመርተው በተለያ መጠኖች እየታሸጉ ለገበያ የሚቀርቡ ውሃዎች የኢትዮጵያ ጥራትና ደረጃዎች (የተስማሚነት ምዘና ድርጅት) ዕውቅና የሌላቸው መሆኑን ድርጅቱ በትግራይ ክልል ውስጥ እየተመረተ ለተጠቃሚው ከሚደርስ አንድ የታሸገ ውሃ ውጪ ሌሎቹን እንደማያውቃቸው ቀደም ሲል መግለፁ የሚታወስ ነው፡፡

Read 12679 times