Saturday, 15 February 2014 13:20

ድምፃዊ ብዙአየሁ ደምሴ - ከካናዳ

Written by 
Rate this item
(8 votes)

“በሰው ስራ ታውቆ የራስን መስራት ፈተና አለው”

ከጥቂት ዓመታት በፊት በዝነኛው ድምፃዊ ሙሉቀን መለሰ ሥራዎች ከአድማጮች ጋር የተዋወቀውና ተወዳጅነትን ያተረፈው አርቲስት ብዙአየሁ ደምሴ፤ በቅርቡ “ሳላይሽ” የተሰኘ የራሱን የመጀመርያ አልበም ለጆሮ አብቅቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየው ገበያው አልበሙ ከወጣ ጊዜ አንስቶ ድምፃዊውን ለማግኘት ስትታትር ቆይታ ባለፈው ረቡዕ ምሽት ተሳክቶላታል፡፡ ድምፃዊውን አሁን ከሚኖርበት ካናዳ በስልክ አግኝታው በአዲሱ አልበሙና በሙያው እንዲሁም በህይወቱ ዙሪያ እንደሚከተለው አነጋግራዋለች፡፡

ደህና አደርክ ልበል፣ ደህና ዋልክ? እኛ ጋ ከቀኑ አስር ሰዓት ነው...
ደህና አደርክ ነው የሚባለው፤ እኛ ጋ ከጠዋቱ 1 ሰዓት ነው፡፡ ግን አንቺ እንዴት ዋልሽ..?
በጣም ደህና ነኝ፡፡ አንተስ እንዴት አደርክ..ለነገሩ ድምፅህም የጠዋት ድምፅ ነው…
አዎ! ከእንቅልፌ እየተነሳሁ ነው፤ ጠዋት ስለሆነ ነው ድምፄ የጎረነነብሽ…እግዚአብሄር ይመስገን በጣም ደህና ነኝ፡፡ አገር ሰላም ነው? ሁሉ አማን? እኔ ሰላም ነኝ
ቤተሰብህን ጠቅልለህ ነው እንዴ ካናዳ የገባኸው..?
ቤተሰቦቼ ኢትዮጵያ ናቸው፤ ልጆቼም ባለቤቴም፡፡
በዚያው ቀልጠህ ቀረህ እኮ! ለመሆኑ አካሄድህ ለስራ ነው ለኑሮ?
ለነገሩ አሁን ሁሉ ነገር ስላለቀ መምጣት እችላለሁ፡፡ ለተወሰኑ ጊዜያት ለስራ ነበር የሄድኩት።
አዲሱ ‹‹ሳላይሽ›› አልበምህ እንዴት ነው? ተቀባይነት አገኘ? እስካሁን ምን ያህል ቅጂዎች ተሸጡ?
በትክክል ይሄን ያህል ኮፒ ተሸጧል ማለት መረጃው የለኝም፡፡ ነገር ግን ሙዚቃዬን ካሳተመልኝ የናሆም ሪከርድስ ባለቤት ጋር በየቀኑ እንገናኛለን፡፡ እንደ አሳታሚ ሳይሆን እንደጓደኞች ነን፡፡ እናም ባለቤቱ፤ “ብዙ አልበም ሰርቻለሁ፤ በዚህ ፍጥነት የተደመጠ ብዙ አልገጠመኝም”፤ ብሎኛል፡፡ እንዲህ በመሆኑም በጣም ተደስቻለሁ፡፡ የካናዳን ነገር ደግሞ ከምነግርሽ በላይ ነው፡፡ ሙዚቃው እንዴት እንደሚደመጥ አልነግርሽም፡፡ በቃ ያስደነግጣል .. ይሄን ያህል እደመጣለሁ እንዴ? ብዬ በእጅጉ ተደንቄአለሁ፡፡ አሳታሚዬ ናሆም ሪከርድስ ደግሞ አሜሪካ ነው ያለው፡፡ እሱ እንደነገረኝ እዚያም እጅግ በጣም ጥሩ ነው፤ ኢትዮጵያ ይደመጣል የሚባለው ያህል ሳይሆን አይቀርም ከፍተኛ ተ    ቀባይነት አግኝቷል፡፡
እስከዛሬ እንግዲህ በሰው ዘፈን ነበር የምትታወቀው፡፡ ከሰው ዘፈን ወደ ራስ ሥራ የመሸጋገሩ ሁኔታስ ምን ይመስላል? መቼም ፈታኝ እንደሚሆን እገምታለሁ …
አዎ፤ ከሰው ዘፈን ወጥተሽ የራስሽን ኦርጂናል ስራ ስትሰሪ በጣም ከባድ ነው፡፡ ምክንያቱም የራስ ዘፈን ሲሆን ራስሽን ሆነሽ ነው የምርቀርቢው። በተለይ በሰው ስራ ታውቀሽ ቆይተሽ የራስሽን ስትሰሪ ትንሽ ፈተና አለው፡፡
በአዲሱ አልበምህ ላይ በድምጽህም ሆነ በአዘፋፈን ዘይቤህ የሙሉቀን መለሰ ተፅዕኖ ጎልቶ እንደሚታይብህ ይነገራል፡፡ ይህን አስተያየት ትቀበለዋለህ?
አንዳንድ ጊዜ የምትወጅው ነገር የግድ ይስብሻል። ጥሩ ነገር ማን ይጠላል ብለሽ ነው… (ሳቅ)
የመጀመሪያ አልበምህ ሙሉ በሙሉ የሙሉቀን መለሰ ነበረ፡፡ ለአንዱ ዘፈን እንደውም የቪዲዮ ክሊፕ ሁሉ ሰርተህለታል፡፡ በዚህም ከሙሉቀን ጋር ተጋጭተህ ነበር፡፡ በአዲሱ አልበምህ ደግሞ አንድ የሙሉቀን መለሰ ዘፈንን ተጫውተሃል፡፡ አሁንስ አስፈቅደኸው ነው?
አዲስ የሰራሁት አይደለም፤ ከመጀመሪያ አልበም የተረፈ ነው፡፡ እንደውም መጀመሪያ ላይ ማካተት አልፈለግሁም ነበር፡፡ በኋላ የመጣ  ሃሳብ ነው፡፡ እሱም ቢሆን ግን ለኤሌክትራ ባለቤት እንዲሁም ለግጥምና ዜማ ደራሲዎቹ  አስፈላጊው ክፍያ ተፈፅሟል፡፡ ‹‹አትከብደኝም እስዋ›› የሚለውን ነው በአዲሱ አልበም ውስጥ ያካተትኩት፡፡
በነገርሽ ላይ አሜሪካ ሳለሁ ከጋሽ ሙሉቀን ጋር በጣም እንገናኝ ነበር፤ ካናዳ ከመጣሁ ነው የተጠፋፋነው፡፡ እና ለዚህ የሙሉቀን ዘፈን ብቻ የወጣው ብር በጣም ብዙ ነው…የናሆም ሪከርድስ ባለቤት አቶ ኤልያስ ነው የከፈለው፡፡
አዲሱ አልበምህ መለቀቁን ተከትሎ ከተለያዩ አገራት የኮንሰርት ጥያቄዎች አልቀረቡልህም?
አሁን በተጨባጭ ብዙ ስራዎች፣ ብዙ ኮንሰርቶች እየመጡልኝ ነው፡፡ አልበሙ በየቤቱ ይግባ እንጂ ሥራው ችግር የለውም፤ ይመጣል፤ ሰው ውስጥ እስኪዋሃድ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ከፋሲካ በኋላ የኮንሰርት ጉዞዬን እጀምራለሁ፡፡ እስከዛ ግን ሁለት ነጠላ ዜማዎች እለቃለሁ፡፡ በተለይ አንዱ ነጠላ ዜማ በበዓል መዳረሻ ላይ ነው የሚሆነው፤ ያለቀ ስራ ነው፡፡
‹‹ሳላይሽ›› በሚለው አልበምህ ከህይወትህ ጋር የሳሰረ ዘፈን አካተሃል?
አዎ አለ፡፡ ‹‹የህልሜ ንግስት›› የሚለውን ለባለቤቴ ነው የዘፈንኩት፡፡ ከእግዚአብሄር በታች አጠገቤ ሆና ትረዳኝ የነበረች እሱዋ ነች፡፡ ‹‹ንገሪኝ›› የሚለውን ደግሞ ለእናቴ ነው የዘፈንኩት፡፡
አሁን ካናዳ ውስጥ በምን ስራ ነው የምትተዳደረው?
ሙዚቃ ነው የምሰራው፡፡ ከሙዚቃ ውጪ ምንም ነገር አልሰራም፡፡ ራሴን በሙዚቃው ዘርፍ ለማሳደግ ጥናቶች እያደረግሁ ነው፡፡ መተዳደሪያዬ ግን ሙዚቃ ነው፡፡
ለአዳዲሶቹ ዘፈኖችህ ቪዲዮ ክሊፕ ለመስራት አላሰብክም?
‹‹ሳላይሽ›› እና ‹‹ማመኔ›› ለሚሉት ዘፈኖች እዚህ ክሊፕ ሰርቼ እያለቀ ነው፡፡ በቅርቡ አድናቂዎቼ እጅ ይገባል፡፡
ቴዲ አፍሮ በስራህ እንደሚያደንቅህና ዝምድና እንዳላችሁ ሰምቻለሁ፡፡ ስለ አዲሱ አልበምህ አስተያየት ሰጠህ?
አዎ ዝምድና ነገር አለን፡፡ ዘፈኖቼን ብዙ የሰማ አልመሰለኝም፡፡ እስካሁን ምንም አይነት አስተያየት አልደረሰኝም፡፡
ካናዳ ለአርቲስቶች እንዴት ናት? ትመቻለች?
ውይ አትመችም፡፡ ከባድ ነው፤ እኔ እድለኛ ስለሆንኩ ነው፡፡ እዚህ ያለን አርቲስቶች የተወሰንን ነን፡፡ ሄኖክ አበበ፣ ፋንታሁን ሸዋንቆጨው፣ ይርዳው ጤናው፣ እና ሌሎችምሰ አሉ፡፡ ካናዳን እንደማረፊያ ነው የሚጠቀሙባት፤ የተለያዩ አገራት እየሄዱ ኮንሰርት እየሰሩ ይመጣሉ፡፡ ባለፈው ከአስቴር አወቀ ጋር ‹‹እንደ ወፍ›› በሚለው ዘፈን እየዞርኩ ኮንሰርት እንዳቀርብ አስበው ነበር፡፡ ነገር ግን ይኼንን አልበሜን ለመስራት አራት ዓመት ነው የፈጀብኝ፡፡ ትኩረቴ ሁሉ እሱላይ ነበር፡፡ አልበሜን ከዳር ሳላደርስ የትም አልንቀሳቀስም ብዬ ነው የቀረው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ኮንሰርት ለማቅረብ ሃሳብ የለህም? መቼ እንጠብቅ?
ኢትዮጵያ ላይ በቅርቡ አንድ ነገር ለማድረግ አስበናል፡፡ እስከዛው ለአድናቂዎቼ እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ እጅግ እንደምወዳቸው መልዕክት አስተላልፊልኝ፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ነገር ስላስተካከለልኝ አመሰግናለሁ፡፡ ባለቤቴ፣ ልጆቼ፣ አባቴን ጨምሮ አብረውኝ የነበሩትን ሁሉ አመሰግናለሁ፡፡ ለዚህ አልበም በስኬት መጠናቀቅ ከመጀመሪያ እስከመጨረሻ አብረውኝ ለሰሩና ከጐኔ ላልጠፉት አማኑኤል ይልማና አቀናባሪ ወንድሜነህ ምስጋናዬ ይድረሳቸው፡፡ የናሆም ሪከርድስ ባለቤት አቶ ኤልያስንም በእጅጉ አመሰግነዋለሁ፡፡

Read 7604 times