Tuesday, 04 March 2014 11:51

ደደቢት ሴፋክሴዬንን በሜዳው ይፋለማል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በዓለም 107ኛ፤ በአፍሪካ 17ኛ፤ በምስራቅ አፍሪካ 2ኛ ነው


16 ክለቦች በሚሳተፉበት የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ እና ነገ በአንደኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታዎች በመላው አህጉሪቱ ሲካሄዱ የምስራቅ አፍሪካዎቹ ከተሞች አዲስ አበባ፤ ዳሬሰላም እና ናይሮቢ ትልልቅ ግጥሚያዎችን  ያስተናግዳሉ፡፡ የአምናው የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ደደቢት በነገው እለት የቱኒዚያውን ክለብ ሲኤስ ሴፋክሴዬን በአዲስ አበባ ስታድዬም የሚፋለም ይሆናል፡፡ የቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ሴፋክሴዬን ከሳምንት በፊት በአፍሪካ ክለቦች ሱፕር ካፕ በግብፁ ክለብ አልሃሊ 3ለ2 ተሸንፎ ዋንጫ አምልጦታል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን የአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ ዋንጫን ያሸነፈው ሲኤስ ሴፋክሲዬን በሱፕር ካፑ የደረሰበትን ሽንፈት በነገው የአዲስ አበባ ጨዋታ ለማካካስ ትኩረት ማድረጉን የቱኒዚያ ጋዜጦች ዘግበዋል፡፡ ደደቢት በአፍሪካ ደረጃ  ብዙም ልምድ ባይኖረውም በደጋፊው ፊት ከባድ ተፎካካሪ ሆኖ በመጫወት በከፍተኛ የግብ ልዩነት ለማሸነፍ ከቻለ የማለፍ እድሉን ሊያሰፋ ይችላል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታዎች በዛሬው እለት ናይሮቢ ላይ የኬንያው ክለብ ጎሮማሃያ ለሁለት ጊዜያት የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫዎችን ያሸነፈውን የቱኒዚያውን ኤስፔራንስ ሲገጥም፤ ዳሬሰላም ላይ ደግሞ የታንዛኒያው ክለብ ያንግ አፍሪካንስ የአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ከነበረውና ከሳምንት በፊት የሱፕርካፕ ዋንጫ ያገኘውን የግብፁን ክለብ አልሃሊን ያስተናግዳል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተመሰረተ ከ70 ዓመታት በላይ ያስቆጠረው የኢትዮጵያ ክለቦች ከፍተኛ ውድድር ፕሪሚዬር ሊግ  ባለፈው የውድድር ዘመን በፉክክር ደረጃው  ከዓለም 107ኛ፤ ከአፍሪካ 17ኛ እንዲሁም ከምስራቅ አፍሪካ 2ኛ ማግኘቱን የእግር ኳስ ስታትስቲክስ እና ታሪክ ዓለም አቀፍ ፌደሬሽን (IFFHS) አመለከተ፡፡ ተቀማጭነቱን በስዊዘርላንዷ ከተማ ሉዛን ውስጥ ያደረገው የእግር ኳስ ስታትስቲክስ እና ታሪክ ዓለም አቀፍ ፌደሬሽን (IFFHS)  ለዓለም የእግር ኳስ ሊጎች ደረጃ የሚያወጣው በአገር ውስጥ የሊግ እና የጥሎ ማለፍ ውድድሮች በመመዘን፤ በአህጉራዊ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ የየአገሩ ክለቦች ያላቸውን ፉክክር  ደረጃ እና ውጤት በማስላት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከዓለም የክለብ ውድድሮች 107ኛ ደረጃን  ያገኘው 157 ነጥብ በማስመዝገብ ነው፡፡ በምስራቅ አፍሪካ በክለቦቿ የሊግ ውድድር አንደኛ የሆነችው 230 ነጥብ በማስመዝገብ ከዓለም 91ኛ ደረጃ የወሰደችው ሱዳን ስትሆን፤ የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከያዘው ሁለተኛ ደረጃ በመቀጠል፤ የኬንያ ፕሪሚዬር ሊግ  በ123 ነጥብ ከዓለም 114ኛ፤ የታንዛኒያ  ፕሪሚዬር ሊግ በ114.5 ነጥብ ከዓለም 118ኛ፤ የብሩንዲ ፕሪሚዬር ሊግ በ114 ነጥብ ከዓለም 119ኛ፤ የኡጋንዳ ፕሪሚዬር ሊግ በ114 ነጥብ ከዓለም 120ኛ እንዲሁም የሩዋንዳ ፕሪሚዬር ሊግ በ108 ነጥብ ከዓለም 125ኛ ደረጃ በማግኘት ተከታታይ ደረጃ አላቸው፡፡ የእግር ኳስ ስታትስቲክስ እና ታሪክ ዓለም አቀፍ ፌደሬሽን (IFFHS)  የዓለም አንደኛ ምርጥ ሊግ ብሎ የሰየመው 1155 ነጥብ ያስመዘገበውን የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ሲሆን፤ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ1128 ነጥብ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ1058 ነጥብ፤ የጣሊያን ሴሪ ኤ በ927 ነጥብ፤ የብራዚል ሴሪኤ በ896 ነጥብ፤ የአርጀንቲና ፕሪሚዬራ ዲቪዥን በ868 ነጥብ፤ የፈረንሳይ ሊግ 1 በ796 ነጥብ፤ የሩስያ ፕሪሚዬር ሊግ በ739.5 ነጥብ፤ የኮሎምቢያ ፕሪሚዬር ሊግ በ724.5 ነጥብ እንዲሁም የሮማንያ ፕሪሚዬር ሊግ በ722.5 ነጥብ ከ2 እስከ 10 ያለውን ደረጃ አግኝተዋል፡፡ በአፍሪካ በምርጥ የፉክክር ደረጃው አንደኛ የተባለው 469.5 ነጥብ በማስመዝገብ በዓለም 31ኛ ደረጃ የወሰደው የቱኒዚያ ሊግ ነው፡፡  ግብፅ በ361.5 ነጥብ ከዓለም 46ኛ፤ ሞሮኮ በ361 ነጥብ ከዓለም 47ኛ፤ ናይጄርያ በ332.5 ነጥብ ከዓለም 53ኛ፤ ማሊ በ322 ነጥብ ነጥብ ከዓለም 56ኛ፤ ደቡብ አፍሪካ በ316.5 በዓለም 61ኛ፤ አልጄርያ በ315.5 ነጥብ ከዓለም 62ኛ፤ አንጎላ በ314.5 ነጥብ ከዓለም 64ኛ እንዲሁም ካሜሮን በ295 ነጥብ ከዓለም 70ኛ በመመዝገብ በአፍሪካ ምርጥ ሊጎች የደረጃ ሰንጠረዥ ከ2 እስከ 10 ተከታትለው ተቀምጠዋል፡፡ ጋና፤ ኮትዲቯር፤ ኮንጎ ዲ ሪፖብሊክ፤ ሱዳን፤ ዛምቢያ፤ ዚምባቡዌ፤ ኮንጎ ኪንሻሳ፤ ኢትዮጵያ፤ በርኪናፋሶ፤ ቦትስዋና እና ኬንያ ከ11 እስከ 20 ደረጃ ያገኙ የአፍሪካ ሊጎች ሆነዋል፡፡

Read 1353 times