Tuesday, 04 March 2014 11:53

ገንዘቤና መሃመድ የኢትዮጵያን ቡድን ይመራሉ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ከሳምንት በኋላ በፖላንዷ ከተማ ስፖት በሚካሄደው 11ኛው የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮና የሚሳተፈውን የኢትዮጵያ ቡድን ገንዘቤ ዲባባ እና መሃመድ አማን እንደሚመሩት ታወቀ፡፡ በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በወንዶች 800 ሜ፣ 1500 ሜ እና 3000 ሜ እንዲሁም በሴቶች  1500 ሜ እና 3000 ሜ ውድድሮች ኢትዮጵያ 11 አትሌቶችን ታሳትፋለች፡፡ አትሌት ገንዘቤ ዲባባና አትሌት መሃመድ አማን በዓለም በቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ለወርቅ ሜዳልያ ድሎች ከፍተኛ ግምት የተሰጣቸው ሲሆን አዳዲስ ሪከርዶችን እንደሚያስመዘግቡ ተጠብቀዋል፡፡ ገንዘቤ ዲባባ በዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ከ2 ዓመት በፊት በ1500 ሜ ያገኘችውን የወርቅ ሜዳልያ ክብር የምታስጠብቅበት ወቅታዊ ብቃት ቢኖራትም በ3ሺ ሜ ተሳታፊ ለመሆን እንደወሰነች ያመለከተው የአለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ዘገባ፤ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የርቀቱን የዓለም ሪከርድ ለሁለተኛ ጊዜ በመስበር የወርቅ ሜዳልያውን ልትወስድ እንደምትችል ግምት ሰጥቷታል፡፡ ባለፈው 1 ወር ጊዜ ውስጥ በ1500ሜና በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች እንዲሁም በ2 ማይል ሩጫ ሶስት የዓለም ሪከርዶችን የጨበጠችው ገንዘቤ በስዊድን ስቶክ ሆልም የ3ሺ ሜትር የዓለም ሪከርድን 8 ደቂቃ ከ16.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ማስመዝገቧ ይታወሳል፡፡ በሌላ በኩል በ800 ሜትር በትራክ እና በቤት ውስጥ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የወቅቱ ኮከብ  አትሌት የሆነው መሃመድ አማን በርቀቱ የወርቅ ሜዳልያ ክብሩን ለማስጠበቅ እንደሚወዳደር ተገልጿል፡፡  መሃመድ አማን በ800 ሜትር ዘንድሮ ያስመዘገበው 1 ደቂቃ ከ44.52 ሴኮንዶች የሆነ ጊዜ የአፍሪካ ሪኮርድ እንደሆነ ያመለከተው የአይኤኤኤፍ ዘገባ ምናልባትም የርቀቱን የዓለም ሪከርድ ሊያስመዘግብ እንደሚችል ጠቁሟል፡፡ የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ከ2 ዓመት በፊት በቱርክ ኢስታንቡል በተካሄደ ጊዜ በ1500 ሜትር የነሐስ ሜዳልያ ያገኘው መኮንን ገብረመድህንና ዘንድሮ በ3ሺ ሜትር  ውጤታማነት አንደኛ ደረጃ የተሰጠው  ሃጎስ ገብረህይወት ለወርቅ ሜዳልያ የተጠበቁ ሌሎቹ የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በተጨማሪም በወንዶች ምድብ አማን ዎቴ በ1500ሜትር፤ የኔው አላምረው እና ደጀን ገብረመስቀል በ3ሺ ሜትር እንደሚሳተፉ ሲገለጽ፤ በሴቶች ምድብ ደግሞ በ1500 ሜትር አክሱማይትና ኤምባዬ ጉዳይ ፀጋዬ እንዲሁም በ3ሺ ሜትር አልማዝ አያና ህይወት አያሌው ይወዳደራሉ፡፡ በሻምፒዮናው ከ1 እስከ 6 ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች የገንዘብ ሽልማት የሚሰጥ ለ1ኛ 40ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 20ሺ ዶላር እንዲሁም ለ3ኛ 10ሺ ዶላር ይሰጣል፡፡ ለአዲስ የዓለም ክብረወሰን ደግሞ  50ሺ ዶላር ቦነስ እንደሚበረከት ታውቋል፡፡
በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪክ ኢትዮጵያ 19 የወርቅ፤ 5 የብርና 11 የነሐስ በድምሩ 35 ሜዳልያዎችን  በመሰብሰብ ከዓለም አገራት አራተኛ ደረጃ ይዛለች፡፡ በሻምፒዮናው ታሪክ ከምንግዜም ውጤታማ አትሌቶች ተርታ  የሚጠቀሱት  ደግሞ ኃይሌ ገብረስላሴ እና መሰረት ደፋር ናቸው፡፡ ታላቁ አትሌት ሃይሌ ገብረስላሴ በ3ሺ ሜትር 3 የወርቅ ሜዳልያዎችን እንዲሁም በ1500 1 የወርቅ ሜዳልያ ያስመዘገበ ሲሆን በ1997 የ3ሺ ሜትርን ሪከርድ 7 ደቂቃ ከ34.71 ሴኮንዶች እንዲሁም በ1999 እኤአ የ1500ሜ ሪከርድን በ3 ደቂቃ ከ33.77 ሰኮንዶች እንደያዘ ነው፡፡ አትሌት መሰረት ደፋር በበኩሏ በ3ሺ ሜትር 4 የወርቅ፤ 1 የብር እና 1 የነሐስ ሜዳልያዎችን በመሰብሰባቸው ነው፡፡


Read 2519 times