Saturday, 22 March 2014 12:02

የደቡብ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት ከኃላፊነታቸው ተነሱ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(12 votes)

      12 ዳኞች በስነ-ምግባር ጉድለት ከኃላፊነት ተነስተዋል

    ለበርካታ ዓመታት የደቡብ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ታረቀኝ አበራ አይዶ ከኃላፊነታቸው የተነሱ ሲሆን ምክትላቸው የነበሩት አቶ ሙሉጌታ አጎ፤ የጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት ሆነው ተሹመዋል፡፡ በክልሉ ከወረዳ እስከ ጠቅላይ ፍ/ቤት ሲያገለግሉ የነበሩ 12 ዳኞች፤ በስነ-ምግባር ጉድለት ከሃላፊነታቸው እንደተነሱ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አቶ ታረቀኝ ለበርካታ ዓመታት ጠቅላይ ፍ/ቤቱን በመሩበት ወቅት ባሳዩት የሥራ ክፍተትና የስነ-ምግባር ጉድለት ከኃላፊነታቸው እንደተነሱ ምንጮቻችን ቢጠቁሙም፣ የክልሉ የጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉጌታ አጎ ሃሰት ነው ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ “የጠቅላይ ፍ/ቤቱ ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ ታረቀኝ፤ ሶስተኛ ዲግሪያቸውን ለመስራት ወደ ኔዘርላንድ ለመሄድ ባመለከቱት መሰረት፣ተፈቅዶላቸው መሄዳቸውን ነው የማውቀው” ብለዋል፡፡
ከክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ጀምሮ በተለያዩ ዞኖችና ወረዳዎች በዳኝነት ሙያ ሲያገለግሉ የነበሩ 12 ዳኞች በስነ-ምግባር ጉድለት ከኃላፊነት መነሳታቸውን በተመለከተ የጠየቅናቸው አቶ ሙሉጌታ አጎ፤ ዳኞቹ ባሳዩት የስራ ክፍተትና የስነ-ምግባር ጉድለት በዳኞች አስተዳደር ጉባኤ ተወስኖባቸው ከሃላፊነት እንደተነሱ አስረድተዋል፡፡
ቀደም ሲል “ቡታጅራ ላይ በድንጋይና በዱላ ተደብድበው የሞቱት ኢ/ር ጀሚል ሀሰን ቤተሰቦች፤ አቶ ታረቀኝ አበራ ባስቻሉት የይግባኝ ችሎት፣“የገዳዮቹን ፍርድ ያለአግባብ ቀንሰዋል” በሚል ቅሬታ ማቅረባቸውን መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን ጉዳዩ እንደገና በሰበር ሰሚ ችሎት ታይቶ፣ በወንጀለኞቹ ላይ ከፍተኛ ቅጣት ተወስኖባቸዋል፡፡  

Read 3954 times Last modified on Saturday, 22 March 2014 16:20