Saturday, 22 March 2014 13:04

ለቂሊንጦ ማረሚያ ቤት መፃህፍት ማሰባሰብ ተጀመረ

Written by 
Rate this item
(7 votes)

       ከሁለት ዓመት በፊት የተጀመረው ለማረሚያ ቤቶች የሚውል መፃሕፍት ማሰባሰብ ዛሬ ይጀመራል፡፡ ለቀጣዮቹ 30 ቀናት በሚቆየው የመፃሕፍት ማሰባሰብ ሥራ መጽሐፍ መለገስ የሚፈልጉ ፈቃደኞች በተመረጡ ቦታዎች እንዲያስቀምጡ በጎ ፈቃደኛዋ ጥሪ አድርጋለ ች፡፡ ዋቢ ሸበሌ ሆቴል፣ ብሄራዊ ቴአትር ጀርባ የሚገኘው ጃፋር መጽሐፍ መደብር፣ ሜጋ መጽሐፍት መደብር ቢሮ እና ፒያሳ እናት ህንፃ ፊት ለፊት የሚገኘው አብዲ መጸሐፍ መደብር መጽሐፎቹን ለማስቀመጥ የተመረጡ ቦታዎች እንደሆኑ ነርስ ሊንዳ በቀለ ገልፃለች። በ2004 ዓ.ም ብሄራዊ ቴአትር መግቢያው መጽሐፍ የሆነ ፕሮግራም አዘጋጅታ ወደ ሶስት ሺህ ያህል መጽሐፍትን በመሰብሰብ ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንዳስገባች የገለፀችው በጎ ፈቃደኛዋ፤ በ2005 ዓ.ም ከኅብረተሰቡ ገንዘብ በማሰባሰብ ጋሞ አካባቢ ለሚገኙ የገጠር ት/ ቤቶች የመማሪያ መጽሐፍትን በቅናሽ በመግዛት ማስረከቧን ተናግራለች፡፡ ዘንድሮም በጎ ፈቃደኞች የሚለግሷቸውን መጸሐፍት ለቂሊንጦ ማረሚያ ቤት እንደምታስረክብ ገልፃ፤ ሁሉም ሰው ካለው መጽሐፍ ላይ እንዲለግስ ጥሪ አቅርባለች፡፡ በጎ ፈቃደኛዋ በየዓመቱ የምታካሂደውን የመጽሐፍ ማሰባሰብ ሥራ “መጽሐፍት ለሁሉም በሁሉም ስፍራ” በሚል መርህ እንደምታከናውንም ጨምራ ገልፃለች፡፡

Read 2046 times