Monday, 14 April 2014 09:11

ኢትዮጵያና ግብጽ ቦክስ ሊገጥሙ ነው

Written by 
Rate this item
(2 votes)

የከባድ ሚዛን ቦክሰኞቹ ኢትዮጵያዊው ሳሚ ረታ እና ግብጻዊው አህመድ ሰኢድ፣ በሁለቱ አገራት መካከል ሰላማዊ ግንኙነትን የማጠናከር አላማ ይዞ በሚዘጋጀውና በመጪው ግንቦት ወር መጨረሻ አዲስ አበባ ውስጥ በሚካሄደው የቦክስ ግጥሚያ አገራቸውን ወክለው እንደሚፋለሙ ተገለፀ፡፡
ኢትዮጵያዊው የከባድ ሚዛን ቦክሰኛ ሳሚ ረታ ባለፈው ሳምንት ለአናዶሉ ኤጀንሲ እንደተናገረው፣ ሁለቱ ቦክሰኞች ሰላማዊውን ፍልሚያ ለማካሄድ ተፈራርመው ቀን የቆረጡ ሲሆን  የአለም አቀፉ የቦክስ ፌዴሬሽንም ለውድድሩ እውቅና ሰጥቷል፡፡ ውድድሩን ያዘጋጀው ተቀማጭነቱ በአዲስ አበባ የሆነው ‘አፍሪካ ስፖርትስ ፕሮሞሽን’ የተባለ ድርጅት ሲሆን  የውድድሩ አላማም በሁለቱ አገራት መካከል ሰላማዊ ግንኙነትን ማጠናከር ነው፡፡ ውድድሩ፣ ‘አፍሪካውያን አንድ ህዝቦች ናቸው’ የሚል መልዕክት የሚያስተላልፍ ይሆናል ተብሏል፡፡ “ግጥሚያው የሁለቱን አገራት አንድነት የምናሳይበትንና ‘አለመተማመን ገደል ግባ!’ ብለን በጋራ የምናውጅበትን ዕድል ይፈጥራል” ብሏል ሳሚ ረታ፡፡ የአለም አቀፉ የቦክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚደንት ኦኔስሞ ኤ ንጎዊ በበኩላቸው፣ የውድድሩ መሰረታዊ አላማ በአፍሪካ አህጉር ሰላም እንዲሰፍን ማድረግ መሆኑን ጠቁመው፣ “በአፍሪካውያን  መካከል ህብረት መፍጠር” የሚለውን ይህን ታላቅ ሃሳብ ይዞ ለተነሳው ለሳሚ ረታ ያላቸውን አድናቆት ገልጸዋል፡፡
“ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ግድብ ለመስራት ውሳኔ ማሳለፏ አስደስቶኛል፡፡ አባይ ለሁሉም የሚበቃ የፈጣሪ ስጦታ ነው፡፡ ሁሉም አገራት በሰላማዊ ሁኔታ አብረው መኖር የሚችሉበትን እንዲሁም የፈጣሪን ስጦታ በትብብር መንፈስ የሚጋሩበትን መንገድ እንዲፈልጉ እንመክራለን” ብለዋል ንጎዊ፡፡
የቦክስ ግጥሚያው በናሽናል ኤርዌይስ ስፖንሰርነት በዲኤስ ቲቪ ሱፐር ስፖርት ቻናል በቀጥታ እንደሚሰራጭ የገለጸው ሳሚ፣ ግብጻዊው ተፋላሚው አህመድ ሰኢድም፣ በውድድሩ ለመሳተፍ በሙሉ ፈቃደኝነት ተስማምቶ ፊርማውን እንደማኖሩ፣ ቀኑን አክብሮ እንደሚመጣና እንደሚፋለሙም በእርግጠኛነት ተናግሯል፡፡
የውድድሩ ስፖንሰር የናሽናል ኤርዌይስ ባለቤት አቶ አበራ ለሚ በበኩላቸው፣ ኩባንያቸው የውድድሩን ሃሳብ ታላቅነት በመረዳትና በኢትዮጵያና በግብጽ መካከል ያለውን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በማጠናከር ረገድ የሚጫወተውን ሚና በማጤን፣ ግጥሚያውን ስፖንሰር ማድረጉን ለአናዶሉ ኤጀንሲ ተናግረዋል፡፡
የ32 አመቱ የከባድ ሚዛን ቦክሰኛ ሳሚ ረታ፣ ከዚህ በፊት ካደረጋቸው 21 የቦክስ ግጥሚያዎች፣ በ18ቱ ማሸነፉን ለኤጀንሲው ገልጿል፡፡

Read 5069 times